«ዶሮ እና እህል ጠባቂ ልሆን ነበር»የክብረ ወሰን ባለቤት ታምሩ ዘገየ
ዓርብ፣ ግንቦት 16 2005«ስወለድ አያቴ ስሜን ፍቃዱ ነበር ያለኝ። የቄስ ትምህርት ቤት ስገባ ነው ታምሩ የሚለው ስም የወጣልኝ» ይላል ወጣቱ። እንደሱ እምነት ለዚህ ተዓምር ያበቃው አካል ጉዳተኛ ሆኖ መፈጠሩ ነው።
አካል ጉዳተኛ ሆኖ ስለተወለደ ብዙ መከራዎችን አሳልፏል። በተለይ 15 ዓመት እስኪሞላው በመሬት ላይ እየተንፏቀቀ ነበር ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ የሚንቀሳቀሰው።
ይህ ብቻ አልነበረም ታምሩ ብዙ መገለል ስለደረሰበት እና እሱ እንደሚለው ዶሮ እና እህል ጠባቂ እንዳይሆን በእድሜው ከፍ ሲል ወደ ላሊበላ ጉዞ ጀመረ። አላማው ወደ ጎጃም ሄዶ የቄስ ት/ቤት ለመግባት ነው። ላሊበላ እንደደረሰም ለጉብኝት የመጡ አንድ አሜሪካዊ ዶክተር ጋ ይገናኛል። ኋላም ወደ አዲስ አበባ ወስደው የቀዶ ጥገና ህክምና እንዳደረጉለት ይናገራል። ህክምናው ስኬታማ ነበር። ታምሩ ዛሬ ያለምርኩዝ ቆሞ መሄድ ይችላል። ይሁንና በቀዶ ጥገና ህክምና ሊድን ይችላል ብለው ያላሰቡት እናቱ -ታምሩ እንደሚለው ፤በሱ ላይ ብዙም ተስፋ አልነበራቸውም ።አካል ጉዳተኛ ሆኖ የተወለደውን ልጅ አሜን ብለው የተቀበሉት እና ከሌሎች በተለየ አመለካከት የቀረቡት የታምሩ አያት እንደነበሩ ገልፆልናል።
ታድያ ወጣቱ ችግሩን ወደ ተሰጥኦ ቀይሮ እጆቹን እንደ እግር መጠቀም ጀመረ። ዛሬ በዚህ ችሎታው እግሩን ወደ ላይ ሰቅሎ በአንድ ደቂቃ ውስጥ 76ሜትር በመርኩዝ በመሄድ ክብረ ወሰን ለመያዝ ችሏል።
ታምሩ ስለ ከባድ የልጅነት ጊዜው ፣ስለ አሁን ስኬቱ እና የወደፊት አላማው አጫውቶናል። ከድምፅ ዘገባው ያገኙታል።
ልደት አበበ
ሸዋዬ ለገሰ