1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ግብፅ እና የመጀመሪያው ዙር ምክር ቤታዊ ምርጫ

ማክሰኞ፣ ጥቅምት 9 2008

በግብፅ ባለፈው እሁድ የተጀመረው እና ለሁለት ቀን እንዲቀጥል የተወሰነው የመጀመሪያው ዙር ምክር ቤታዊ ምርጫ ትናንት ሲካሄድ ዋለ። በዚሁ በሁለት ዙር በሚካሄደው ምክር ቤታዊ ምርጫ ላይ ድምፁን እንዲሰጥ የተጠራው መራጭ ሕዝብ ቁጥር 27 ሚልዮን ነው። ሁለተኛው ዙር ከአራት ሳምንታት በኋላ ይደረጋል።

https://p.dw.com/p/1Gr6a
Ägypten Parlamentswahlen
ምስል Reuters/M. Abd El Ghany

[No title]

በግብፅ ምክር ቤታዊ ምርጫ ትናንትም ለሁለተኛ ቀን ተካሂዶዋል። የአስመራጩ ኮሚሽን ባለስልጣናት እንዳመለከቱት፣ ባለፈው እሁድ በተጀመረው ምርጫ ላይ ድምፁን ለመስጠት የወጣው መራጭ ሕዝብ ቁጥር ያን ያህል አልነበረም። አሌግዛንድሪያን በመሳሰሉ ትላልቅ ከተሞች በመጀመሪያ ቀን ምርጫ ላይ የተሳተፈው ሕዝብ ቁጥር በገጠሩ አካባቢ ከታየው ይበልጥ ነበር። ሁለተኛው ዙር ምክር ቤታዊ ምርጫ የፊታችን እአአ ህዳር 22 እና 23 ይቀጥላል።

ምርጫው ባለፉት ሁለት ቀናት በሃገሪቱ ካሉት 27 የምርጫ ወረዳዎች መካከል በ14 ቱ የተካሄደ ሲሆን፣ ድምፅ የመስጠት መብት ያለው ሕዝብ ቁጥር 27 ሚሊዮን መሆኑን የአስመራጩ ኮሚሽን አስታውቋል። 596 መንበሮች ላሉት ምክር ቤት 448 ነፃ ፣ 120 በፓርቲ ስር የተደራጁ እጩዎች በቀጥታ በሕዝብ ይመረጣሉ፣ የተቀሩት 28 ደግሞ በፕሬዚደንቱ ነው የሚመረጡት። እአአ ከ2012 ዓም ወዲህ ግብፅ ካለ ምክር ቤት ነው የቆየችው፣ የሃገሪቱ ላዕላይ ሕገ መንግሥታዊ ፍርድ ቤት እአአ በ2011 የተመረጠውን እና በብዛት ፅንፈኞች ይገኙበት የነበረውን ምክር ቤት መበተኑ የሚታወስ ሲሆን፣ ከዚያን ጊዜ አንስቶ ፕሬዚደንት አብደል ፋታህ አል ሲሲ ሥልጣኑን በጠቅላላ ይዘዋል። አዲሱ የግብፅ ምክር ቤትበጎርጎሪዮሳዊው 2015 ዓም መጨረሻ ይቋቋማል ተብሎ ይጠበቃል።

Ägypten Parlamentswahl 2015
ምስል picture-alliance/dpa/K. Elfiqi

ግብፃውያን ባለፈው እሁድ በጀመሩት ምክር ቤታዊ ምርጫ የሥርዓት ዴሞክራሲ ሂደት ለማንቀሳቀስ የሚያስችለውን የመጨረሻ ርምጃ ወስደዋል። ይህን የሚሉት የግብፅ አመራር አባላት፣ በተለይም፣ ለመጀመሪያ ጊዜ በዴሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጡትን የቀድሞ ፕሬዚደንት መሀመድ ሙርሲን ከስልጣን ያስወገዱት የቀድሞ ጀነራል እና የአሁኑ ፕሬዚደንት አብደል ፋታህ አል ሲሲ ናቸው። ይሁንና፣ የተቃዋሚው ቡድን ሀሳቡን እንዳይገልጽ በታፈነበት እና የቀድሞውን አምባገነን ፕሬዚደንት ሆስኒ ሙባራክ አገዛዝ ዘመንን ለመመለስ በተመቻቸ የምርጫሕግ የሚመረጠው አዲሱ ምክር ቤት አሁን በሚታየው የሃገሪቱ ፕሬዚደንት አብደል ፋታህ አል ሲሲ ፈላጭ ቆራጩ አገዛዝ ላይ አንዳችም ለውጥ የማያመጣ ነው የሚሆነው በሚል ሃያስያን ትችት ሰንዝረዋል። ፅንፈኛው መሀመድ ሙርሲ ለራሳቸው ተጨማሪ ስልጣን በመስጠት፣ ዳኞችን ማስፈራራት፣ የፕሬስ ነፃነትን ባፈኑት እና እስላማዊውን ሕግ መከተል በጀመሩበት ጊዜ አብደል ፋታህ አል ሲሲ ጣልቃ በመግባት ይህንኑ ሂደት እአአ ሰኔ 24፣ 2013 ዓም ማስቆማቸው ይታወሳል።

Ägypten Mohamed Mursi Ex-Präsident
ምስል Reuters/A. Waguih

« ግብፅ ወደ አደገኛው ማለትም፣ የእምነት ልዩነቶችን፣ የርስበርስ ጦርነት እና የመንግሥት ተቋማት መዋቅሮችን መንኮታኮትን ወደሚያስከትል ውስጣዊ ውዝግብ ማጥ ውስጥ ስትወድቅ አንዳችም ርምጃ ሳንወስድ ዝም ብለን አንመለከትም። »

በዚሁ ርምጃቸው የብዙኃኑን ድጋፍ ካገኙት አል ሲሲ ጋር ፍጥጫ ላይ መግባት ማንንም እንደማይበጅ በምክር ቤታዊው ምርጫ ከሚሳተፉት አንዱ የሆነው የነፃ ግብፃውያን ፓርቲ ቃል አቀባይ ሸባግ ዋጉዊ በመግለጽ፣ በፕሬዚደንቱ እና በምክር ቤቱ መካከል የሆነ የስልጣን መጋራት ስምምነት ሊኖር እንደሚችል ግምታቸውን ሰጥተዋል።

ምክር ቤታዊው ምርጫ አስመራጩ ኮሚሽን ከጠበቀው ያነሰ ሆኖ መገኘቱን አስታውቋል። ለዚህም ፕሬዚደንት አል ሲሲ የሚከተሉት የማያፈናፍን ፖለቲካ ምክንያት መሆኑን የዩኤስ አሜሪካውያኑ «ብሩኪንግስ ኢንስቲቲውሽን ዋሽንግተን » የሚባለው የፖለቲካ ጥናት ተቋም ተንታኝ ኤች ኤ ሄሌየር ለዶይቸ ቬለ አስረድተዋል።

« ከግብፅ ሕዝብ መካከል ብዙውን ከፊል የሚሸፍነው ወገን ይህንን ፖለቲካዊ ሂደት ሕጋዊ አድርጎ አይመለከተውም። በሌላ በኩል ደግሞ ብዙ ሰዎች ፕሬዚደንቱን መደገፍ የሚያስደስታቸው ይመስለኛል። እነዚህ ሰዎች በሃገሪቱ ፖለቲካዊ ሂደት ውስጥ የማሳተፍ ያን ያህል ፍላጎት የላቸውም። »

ሁለተኛው ዙር ምርጫ የፊታችን እአአ ህዳር 22 እና 23 በተቀሩት 13 የምርጫ ወረዳዎች የሚካሄደው የምክር ቤታዊው ምርጫ አጠቃላይ ውጤት የፊታችን ታህሳስ ይፋ እንደሚደረግ ይጠበቃል።

አርያም ተክሌ

አዜብ ታደሰ