ግብፅ - የተከፋፈለው ህዝብ
ግብፅ ውስጥ ከሥልጣን ከተወገዱት ፕሬዚደንት ከሞሐመድ ሙርሢ በኋላ በሀገሪቱ መረጋጋት አይታይም። በደጋፊዎችና ተቃዋሚዎች መካከልም ዕርቅ አልወረደም። በደረሰው ግጭት እስካሁን በርካታ ሰዎች ህይወታቸውን አጥተዋል።
ከመንፈንቅለ መንግስቱ በፊት
በሰኔዎቹ መጨረሻ ነበር በፕሬዚደንት ሞሐመድ ሙርሢ ላይ ከፍተኛ የተቃውሞ ሰልፍ መካሄድ የተጀመረው። የተቃውሞው አንቀሳቃሽ ታማሩድ (አመፅ አብዮት)ትችትም በፈላጭ ቆራጭነት የአስተዳደር ስልት፣ በሀገሪቱ የከረረ እስልምና እንዲስፋፋ እና የኢኮኖሚውም ባፋጣኝ ሁኔታ እንዲዳከም አድርገዋል በሚል ነው።
የተባባሰው አመፅ
ሙርሢ ፣ ከሥልጣን እንዲወርዱ የሚያሳስብ ጠንካራ የተቃውሞ ሰልፍ አጋጥሞአቸው ከሰነበቱ በኋላ ፣ አማፂያን ሰኔ 24 2005 ዓም ካይሮ የሚገኘውን የሙስሊም ወንድማማች ማኅበር መቀመጫን አወደሙ። ክፍሎቹንም እንዳልነበር አደረጉ። በሙርሢ ደጋፊዎች እና ተቃዋሚዎች መካከል የተነሳው ብጥብጥ አሁንም እንደቀጠለ ነው።
ጥያቄው
የግብፅ መከላከያ ሚንስትር እና የጦር ሐይሎች ጠቅላይ አዛዥ ጄኔራል አብዱል ፈታሕ አል-ሲሲ ሰኔ 24 2005 ዓም ሙርሢ እና የሙስሊም ወንድማማቾች በሀገሪቷ የተነሳውን አመፅ በሚቀጥሉት 48 ሰዓታት እንዲያቆሙ ነበር የጠየቁት። ሙርሢ ግን ስልጣን እንደማይለቁ አስታወቁ። ሙስሊም ፖለቲከኞች እና አድናቂዎቻቸውም የግብፅ ህዝብ የኃይሉን አመራር እንዲደግፍ አሳሰቡ።
ከስልጣን ውገዳ
ጦር ኃይሉ የሰጠው 2ኛ የማስጠንቀቂያ የጊዜ ገደብ ካለፈም በኋላ ፕሬዚዳንት ሙርሢ ከስልጣን ለመውረድ ፍቃደኛ አልነበሩም። ሰኔ 26 2005 ዓም ምሽትም የግብፅ ጦር ኃይል ፕሬዚዳት ሙርሢን ከሥልጣን ማስወገዱ ተሰማ። ሙርሢም በቁጥጥር ስር ዋሉ። አከራካሪው ህገ መንግስትም ተከፈተ። የሙርሢ ደጋፊዎች በካይሮ ጎዳናዎች ተቃውሟቸውን ሲያሰሙ፤ ተቃዋሚዎቹ በደስታ ፈነደቁ። በቀጣዩ ብጥብጥም በርካታ ሰዎች ተገደሉ በመቶ የሚቆጠሩም ቆሰሉ።
አዲስ አመራር በመንገድ ላይ
ፕሬዝዳት ሙርሢን ከስልጣን ከተወገዱ በኋላም የግብፅ ሕገ-መንግሥታዊ ፍርድ ቤት ዋና ዳኛ አድሊ መንሱር በጊዚያዊ ፕሬዝዳትነት ተሾሙ። ህገ መንግስቱም ማሻሻያ እንዲደረግበት እና ህዝቡን የሚወክል ተደርጎ እንዲቀርብ ተጠየቀ። መንሱርም የሙርሢ ደጋፊዎች እንዲተባበሩ ቢጠይቁም የሙስሊም ወንድማማቾች ይህንን በጥብቅ አወገዙ።
የግብፅ ህዝብ ክፍፍል
ሙርሢ ከሥልጣን ከወረዱ ቀናት በኋላም አመፁ አልተቋጨም። በደጋፊዎች እና ተቃዋሚዎች መካከል ካይሮ ላይ ደም ተፋሰሰ። በካይሮ ብቻም ሳይሆን በአሌክሳንድሪያ፣ ስዌዝ እና አል አሪሽም ሁለቱ ቡድኖች ተጋጩ።
የጦር ኃይሉና ገለልተኛነት
የግብፅ የጦር ኃይል ከተወሰነ ወቅት በቀር ጣልቃ ከመግባት ተቆጠቦ ነው የቆየው።ይሁንና በርካታ የሙስሊም ወንድማማቾች ባለስልጣናት በቁጥጥር ስር ውለዋል።ይህም አመፁን አባብሳችኋል በሚል ነው። የሙስሊም ወንድማማጮች ግን ሙርሢ መልሰው ስልጣን እስኪረከቡ ድረስ አመፃቸውን እንደሚቀጥሉ አሳስበዋል።
የጨለመ ተስፋ
ባለፈው ቅዳሜ (29 ሰኔ 2005ዓም) ከካይሮ የመጣው ዜና የሰላም ኖብል ተሸላሚ ሞሀመድ ኤል ባራዳይ ስልጣኑን ይረከባሉ የሚል ነበር። ሆኖም ዜናው ከጥቂት ሰዓታት በኋላ መልሶ ውድቅ ሆነ። የዚህም ምክንያት የሙስሊሙ ኑር ፓርቲ አመፅ እንደሚያስነሳ በመሰማቱ ነው። ኤል ባራዳይ በተለይ በምዕራብ ሀገራት ዲሞክራሲ እንዲሰፍን ይጥራሉ ብለው ተስፋ ይጥሉባቸዋል።