1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ግጭት እና ተቃዉሞ በጋምቤላ

Merga Yonas Bulaሰኞ፣ ሚያዝያ 17 2008

ባለፈዉ ሐሙስ በጋምቤላ ክልል በጄዊ የስድተኞች መጠለያ ካምፕ አከባቢ ንብረትነቱ /ACF/ የተባለ ግብረ ሰናይ ድርጅት የሆነ አንድ ተሽከርካሪ ባደረሰው አደጋ ሁለት የስደተኞች ልጆች ከሞቱ በኋላ ስደተኞቹ 21 የአካባቢውን ነዋሪዎች ሲገድሉ፣ ከ10 በላይ መቁሰለቸዉን ዘገባዎች ያሳያሉ።

https://p.dw.com/p/1IcRc
UNHCR Flüchtlingslage in Gambella Äthiopien
ምስል DW/Y. Gebreegziabher

[No title]

የጋምቤላ ክልላዊ መንግሥት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጋትሏክ ቱት ኩዃት ግጭቱ መከሰቱን አረጋግጠው አደጋዉን አድርሰዋል ተብለው የተጠረጠሩት 30 ሰዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸዉንም ባወጡት መግለጫ አስታውቀዋል ። ይሁን እንጅ በጋምቤላ ከተማ የስደተኞቹን ርምጃ በመቃወም ለተቃውሞ አደባባይ የወጡት ከፀጥታ ኃይሎች ጋር መጋጨታቸዉ አለመረጋጋቱን እንዳባባሰ ይሰማል። ስለ ግጭቱ የጠየቅናቸው የፌዴራል እና አርብቶ አደር ልማት ጉዳዮች ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ አበበ ወርቁ ጉዳዩን በተመለከተ የተጠናከረ መረጃ እንደሌላቸዉ ይናገራሉ።

ዶቼቬለ ስለ ግጭቱ ከአካባቢው ነዋሪዎች መረጃዎችን ለማግኘት ያደረገው ጥረት አልተሳካም ። ሆኖም መቀመጫውን ብሪታኒያ ያደረገው የAnywaa Survival Organizaion የተባለዉ የጋምቤላ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪ ድርጅት መሪ አቶ ኝካዉ ኦቻላ በተቃዋሚዎችና እና በጸጥታ ሃይሎች መካከል ስለተፈጠረው ግጭት የሚያውቁትን ለዶቼቬለ ተናግረዋል። የዚህ ሁሉ መንስኤ ያሁኑ መንግስት ስልጣን ከያዘ አንስቶ ያለዉ የመልካም አስተዳደር ብልሹነት ነዉ ሲሉ አቶ ኝካዉ ኦቻላ ያስረዳሉ ። በጋምቤላ ክልል የአኙዋክ የኑዌር እና የሌሎች ብሄረሰቦችን እሮሮዎች መንግስት ማዳመጥ አልቻለምም ይላሉ።

Karte Äthiopien Südsudan Gambella DEU

በሌላ በኩል ይህ ግጭት ከመከሰቱ ከአንድ ሳምንት በፊት <<የታጠቁ ኃይሎች>> ከደቡብ ሱዳን በኩል ሰርጎ በመግባት በጋምቤላ ክልል 208 መግደላቸዉ፣ ከ80 በላይ በማቁሰል 102 ህፃናትን ደግሞ አፍነዉ መዉሰደቸዉ ይታወሳል።ጥቃት የደረሰው በኑዌር ዞን ሶስት ወረደዎች ላይ ሲሆን ወደ 2000 የሚሆኑ ከብቶችንም እንደዘረፉ ቤቶችም እንደተቃጠሉ በፌዴራል እና አርብቶ አደር ልማት ጉዳዮች ሚኒስትር የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ አበበ ወርቁ ለዶቼ ቬሌ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ መከለከያ ሰራዊት እነዚህን <<ታጣቂዎች>> ለመያዝና እና የታገቱትን ለማስመለስ ርምጃዎችን እየወሰደ መሆኑንም አቶ አበበ አብራርተዋል።

ይህ ጉዳይ በተመለከተ በዶቼ ቬሌ የፌስቡክ ደረ ገፅ ላይ በተደረገዉ ዉይይት የኢትዮጲያ መንግስት ጋምቤላ ዉስጥ የተከሰተዉን ግጭት ለማብረድ ከፍተኛ ሚና መጫወት እንዳለበት አስታያየታቸዉን ሰጥተዋል።

መርጋ ዮናስ

ኂሩት መለሰ