1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለምክር ቤት አባላት ምላሽ ሰጥተዋል

ሰኞ፣ ታኅሣሥ 16 2010

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ የተወካዮች ምክር ቤት አባላት ባቀረቡት ጥያቄ መሰረት ዛሬ ከሰዓት በምክር ቤት ተገኝተው ነበር፡፡ የበርካቶችን ህይወት የቀጠፈው የሀገሪቱ የፖለቲካ ቀውስ ያሳሰባቸው የምክር ቤት አባላት ላቀረቧቸው ጥያቄዎችም በዝግ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡  

https://p.dw.com/p/2pw2B
Äthiopien | Parlament
ምስል DW/Y. G. Egziabher

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለምክር ቤት አባላት ምላሽ ሰጥተዋል

የዛሬው የጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ የምክር ቤት ቆይታ ያልተለመዱ ነገሮች የታዩበት ነው፡፡ ምክር ቤቱ በተለምዶ መደበኛ ስብሰባውን ከሚያደርግባቸው ማክሰኞ እና ሐሙስ ቀናት ሰኞ ዕለት መካሄዱ ብቻ ሳይሆን ለጋዜጠኞች እና ታዛቢዎች ዝግ መደረጉ አንዱ ነው፡፡ ጥያቄ እና መልሱ የተጠራው ደግሞ በገዢው ፓርቲ የምክር ቤት አባላት መሆኑ ደግሞ ሌላው ነው፡፡

ከቀኑ ስምንት ሰዓት ተኩል ገደማ የተጀመረው የዛሬው ስብሰባ ሶስት ሰዓት ገደማ እንደፈጀ የምክር ቤቱ ሰራተኞች ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል፡፡ ስብሰባው ዝግ የተደረገው ለጋዜጠኞች ብቻ ሳይሆን ለምክር ቤቱ ሰራተኞች ጭምር እንደሆነ ምንጮች ገልጸዋል፡፡ የምክር ቤቱ የቀረጻ ሰራተኞችም ወደ ስብሰባው አዳራሽ አለመግባታቸውን ተናግረዋል፡፡ ስለዛሬው ስብሰባ አጀንዳ የተጠየቀው የምክር ቤቱ የመረጃ እና ኮሚዩኒኬሽን ክፍል ሰራተኛ “ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከአባላት ጋር የሚያደርጉት ውይይት ከመሆኑ በስተቀር አጀንዳውን አናውቅም” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

Äthiopien | Parlament
ምስል DW/Y. G. Egziabher

በ2008 ዓ.ም ተሻሽሎ የጸደቀው የተወካዮች ምክር ቤት የአሰራርና የአባላት የሥነ-ምግባር ደንብ ስብሰባዎች በዝግ ሊካሄዱ እንደሚችሉ ደንግጓል፡፡ ስብሰባው በዝግ ይካሄድ የሚለው ጥያቄ ከምክር ቤት አባላት አሊያም በህግ አስፈጻሚው አካል ሊቀርብ እንደሚችልም አስቀምጧል፡፡ አንድ ሶስተኛ የምክር ቤት አባላት አሊያም የህግ አስፈጻሚው አካል ለሚያቀርቡት ይህን መሰል ጥያቄ ግን ከግማሽ በላይ አባላት ድጋፋቸውን መስጠት እንደሚገባቸው ይገልጻል፡፡

በዚህ ሁኔታ ከምክር ቤት አባላት ጋር የተገናኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ከሁለት ወር በፊት ጥቅምት 16ም በወቅታዊ የሀገሪቱ ጉዳዮች ላይ ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተው ነበር፡፡ በወቅቱ ከቀረቡላቸው ጥያቄዎች መካከል “በሀገሪቱ አንዳንድ አካባቢዎች ሰላም መደፍረሱ ተጨባጭ ስጋቶች አስከትሏል፡፡ የእነዚህ ነገሮች ምንጭ ምንድነው? ለምንስ ቶሎ መፍታት አልተቻለም፡፡ መንግስት እፈታለሁ ቢልም በተግባር አልታየም” የሚል ነበር፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዛሬ ምክር ቤት ፊት እንዲቀርቡ ምክንያት የሆነውም ይሄው በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች እየታየው ያለው ግጭት እንደሆነ አባላቱ ባለፈው ሳምንት ለዶይቼ ቬለ ገልጸው ነበር፡፡ ከኦሮምያ ክልል ጉጂ ዞን የናጋሌን አካባቢ በመወከል የምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ ታሪኩ ደምሴ ቀደም ሲል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምክር ቤት ተገኝተው በተመሳሳይ ጉዳይ ላይ የተወያዩ ቢሆንም “ያን ጊዜ ሁኔታዎች አልባሱም ነበር” ሲሉ መናገራቸው ይታወሳል፡፡ “ከዚህ በፊትም፣ ከአንድ ወር በፊት ይመስለኛል፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፓርላማ ቀርበዉ ለተነሱት ጥያቄዎች መልስ ሰጥተዉ ነበር። ግን የፖለቲካዉ ሁኔታ ከዚህ ደረጃ አልደረሰም ነበር። በወቅቱ ችግር ቢኖርም እንደ አሁኑ ከበድ ያለ እና የከረረ አልነበረም” ብለዋል፡፡

በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን የቡሌ ሆራ ተወካይ የሆኑት አቶ ቦነያ ኡዴሳ የምክር ቤት አባላት ጠቅላይ ሚኒስትሩን ለምን እንደጠሯቸው እንዲህ አስረድተው ነበር፡፡ «በአሁኑ ሰዓት እየተሰራ ያለዉን፣ እየተጣሰ ያለዉን የሰብዓዊ መብት ሊያስቆም የሚችለዉ ወይም የማስቆምም ግዴታ በሕገ መንግስቱ የተሰጠው የኢሕአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ነው። የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴዉን የሚመሩት ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ናቸዉ። አሁን በአገሪቱ ከሕገመንግስት ዉጭ በሰዉ ልጅ ላይ እየተፈፀመ ያለዉን የሰብዓዊ መብት ጥሰት ማስቆም ስላለባቸዉ ፓርላማዉ ከእሳቸዉ ጋር ሊወያይ ይፈልጋል። እኛም እንደ ፓርላማ አባላት መጠየቅ የምንፈልገዉ የሰዉ ግድያ ለምን አልቆመም? በመንግስት በኩል ይህን ለማስቆም እስካሁን ምን እየተሰራ ነዉ? ይህን ለማስቆም ምን መደረግ አለበት፣ ለምን አልቆመም፣ ለምን አላስቆማችሁም? የሚሉ ጥያቄዎች ናቸዉ» ሲሉ በዋናነት የሚያነሷቸውን ጥያቄዎች ባለፈው ሳምንት ዘረዝረው ነበር።

Äthiopien Parlament Hailemariam Desalegn
ምስል DW/Y. G. Egziabher

በተወካዮች ምክር ቤት የአሰራርና የአባላት የሥነ-ምግባር ደንብ መሰረት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሚያዝላቸው መርኃ ግብር መሰረት፣ በዓመት ሁለት ጊዜ የመንግስትን አጠቃላይ የስራ እንቅስቃሴ አስመልክቶ ዘገባ እንዲያቀርቡ ይጠበቃል። ሆኖም ጠቅላይ ሚኒስትሩ መቅረብ የሚገባው ጉዳይ አለ ብለው ካመኑ በማንኛውም ጊዜ ለምክር ቤቱ ዘገባ ማቅረብ እንደሚችሉ ደንቡ ይደነግጋል። ከዚህ በተጨማሪ መንግስታዊ አካል አንገብጋቢ በሆኑ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ለምክር ቤቱ ማብራሪያ መስጠቱ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ እና ከአባላት ተደጋጋሚ ጥያቄ የሚነሳ ከሆነ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሊጠሩ ይችላሉ ይላል።

ስለዛሬው ስብሰባ ከምክር ቤቱ አባላት ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ አልተሳካም፡፡

ተስፋለም ወልደየስ

ነጋሽ መሐመድ