1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ጨው ጥቅሙና መዘዙ፣

ረቡዕ፣ ሐምሌ 24 2005

«ጨው ሲበዛ ያቅራል ፤ በርበሬ ሲበዛ ይመራል» ይባላል፣ ለሰውና እንስሳ ጠቀሚ ከሆኑ ማዕድናት መካከል አንዱ ጨው ነው፤ የዓለም የጤና ጥበቃ ድርጅት(WHO) እንደሚመክረው ከሆነ እያንዳንዱ ሰው በየቀኑ መጠኑ ፣ከ 5 ግራም የማይበልጥ ጨው መመገብ

https://p.dw.com/p/19HvJ
ምስል Christian Thiele

ይኖርበታል። ከዚህም ጋር ተያይዞ፤ ፖታሲየም በቀን 3,5 ግራም ጠቃሚ ነው ተብሎ እንደተመሠከረለት በዚህ በጀርመን ፤ ለህሙማን ጠቀሚ ምክርም ሆነ ትምህርት ያካፍላል ተብሎ የሚታመንበት ፣ የቤት ሀኪም(ሃውስ አርትዝት)የተሰኘው መጽሔት አስገንዝቦአል።

ጨው ይጠቅማል ብለን ስናወሳ፣ ምን ዓይነት የትኛውን ጨው ማለታችን እንደሆነ በቅድሚያ ግልጽ ማድረግ ሳይኖርብን አይቀርም።

Totes Meer Israel
ምስል Fotolia

ለምግብ ማጣፈጫ ሰዎች የሚጠቀሙበት የተለመደው ማዕድን ጨው ፣ በሥነ-ቅመማ ስሙ «ሶዲዮም ክሎራይድ» (NaCl)የተሰኘው ነው። ጨው፤ ሳይጣራ እንዲሁ የባህሩን ከውሃ ጋር የተቀላቀለውን በማቅረብ ባልተጣራ መልኩ ወይም አጣርቶ ማቅረብ ይቻላል። ለጤንነት ይበልጥ ተፋላጊ የሆነውና ሃኪሞች በሚያሳስቡት መሠረት በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚዘጋጀው ፣ አዮዲን (አዮዳይን)የተሰኘው ሌላ ማዕድን የተቀላቀለበት ነው። ለአንስሳትና ሰዎች ህልውና እጅግ ጠቃሚ መሆኑ የሚነገርለት ጨው፤ ሲበዛ ለተጠቀሱት ክፍሎች ባቻ ሳይሆን ለዕጽዋትም ጎጂነቱ ከቶውንም አያጠራጥርም። የተመጠነ ጨው፤ ምግብን አጣፍቶ ለሰውነት ለአጥንትም ሆነ ለደም የሚጠቅም መሆኑ ብቻ ሳይሆን ምግብ ሳይበላሽ ለረጅም ጊዜ ተጠብቆ እንዲቆይ ለማድረግም ፍቱንነቱ የሚያጠራጥር አይደለም።

ጨው ፣ በዓለም ህዝብ ታሪክ፣ ለምግብ ማጣፈጫነት የረጅም ዘመናት ታሪክ ነው ያለው። ሰው በቅድሚያ በሠፈረባቸውና ሥልጣኔ ባሥፋፋባቸው የዓለም ክፍሎች ብቻ ሳይሆን፤ በማዕከላዊው አውሮፓ በምትገኘው ጀርመን እንኳ፤ የ 3,100 ዓመታት ታሪክ ያለው መሆኑ ነው የተገለጠው። የጀርመን ዛኽሰን አንሃልት ፌደራል ክፍለ ሀገር፣ በቁፋሮ የጥንት የሥልጣኔ አሻራዎችን የሚያስሱ ጠበብት ባልደረባ የሆኑት ሃራልድ ሜለር ፤ ሐምሌ 9 ቀን 2005 ጥንታዊውን የጨው ማዕድን ማውጫ ቦታ ለተመልካቾች በማሳየት እንደገለጡት ከሆነ፣ በሃለ ከተማና አካባቢዋ ይኖር የነበረው ህዝብ ፤ «ነጩ ወርቅ » የሚል ተቀጥላ ስም አግኝቶ በነበረው ጨው ሳቢያ ፣ ለሺ ዓመታት በተሻለ የኤኮኖሚ ደረጃ ላይ ለመገኘት በቅቷል።

በኢትዮጵያ፣ በተለይ በአፋር በረሃ በዳሉልና አካባቢው የሚገኘው ጨው ፣ እየተጠረበ ፣ አሞሌ ጨው በመባል የታወቀው ጡብ መሰል ጥሬ ጨው፤ በነጋዴዎች አማካኝነት ለደጋው አገር ህዝብ ፣ ከዚያም አልፎ ራቅ ወዳሉ አካባቢዎች እየተሸጠ፤ ለተጠቃሚዎቹ ተፈላጊ ምርት ፤ ለሻጮቹም ዋና ወረትም ሆነ ንብረት ሆኖ እስከዛሬ ድረስ የንግድ ልውውጡ እንደቀጠለ ነው። ይኸው የጨው ንግድ የ 30 ሺ ዓመታት ያህል ታሪክ እንዳለውም ነው የሚነገረው። የሰሃራ ምድረ በዳ በር ፤ የምሁራንም ዋና ማዕከል የነበረችው ቲምቡክቱ፣ የ 12ኛው ክፍለ ዘመን ነጋዴዎች፤ የጨውን ዋጋ ፣ ከመጽሐፍትና ወርቅ አሳንሰውት አያውቁም ነበር።

በጥንታውያን ግብጾች፤ ሜሶፖታማውያን፤ ቻይናውያን ግሪኮችና ሮማውያን ጨው፤ በተጨባጭነት ለምግብ ማጣፈጫ ብቻ ሳይሆን፤ በጥንታዊ እምነትና ልማድ፤እንዲሆም የተለያየ ሃይማኖች ልዩ ሥፍራ ሲሰጠው ኖሯል።

Symbolbild Salzstreuer und Pfeffermühle
ምስል Fotolia/macroart

በጥንት ዕብራውያንና ግሪካውያን ዘንድ፤ መስዋዕት ሲቀርብ ፤ በሮማውያን አብያተ መቅደስም ፤ መስዋእቱ በጨው ታሽቶ ነበረ የሚቀርበው። በክርስትና ሃይማኖት፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ፤ ደቀመዛሙትቱን፤ «እናንት የዓለም ጨው ናችሁ» ነው ያላቸው። ጨው ፣ ከመበላሸት ፤ኃጢአት ከሆነው ንቅዘት የሚከላከል ፤ የሚያጸዳ ኃይል እንዳለው ሆኖ ነው የሚታየው የሚተረጎመው ማለት ነው። በዘመነ ሐዲስ -ኪዳንም ፤ ጨው በምሳሌና በምልክት፣ የዕውቀት፣ ከንቅዘት ነጻ የመሆን ፤ እንዲሁም በእግዚአብሔርና በሰው ልጅ መካከል ያለ ዘለዓለማዊነትና ሥምረት ተምሳሌት ሆኖ ነው የተወሰደው።

መጽሐፍ ቅዱስ ፤ በአጠቃላይ ፣ ከ 30 በላይ ጨውን የሚመለከቱ ጉዳዮችን አሥፍሯል። እ ጎ አ በ 1933 ዓ ም፤ የቲቤቱ ዳላይ ላማ ሲሞቱ፣ቀጥ ብሎ እንዲቆም በተደረገ ከጨው በተሠራ አልጋ ውስጥ ነበረ የተቀበሩት። በተለያዩ የአውሮፓ ሃገራት ፣ በዛሬው ዘመንም ቢሆን የቆየ ልማድ እንዲጠበቅ በሚል ጭምር የሞተ ሰው ከመቀበሩ በፊት፣ ሬሣ- ሣጥኑ ውስጥ አንድ እፍኝ ጨው ይበተናል። ጨው፤ ከኃጢአት ነጻ የመሆን ፣ የዘለዓለማዊነት፣ ዲያብሎስንም ማበረሪያ ምልክት ሆኖ ነው የተወሰደው።

አስማተኞችና ርኩሳን መናፍስት እንዳያበላሹት በሚል ልማዳዊ እምነት እስኮትላንዳውያን በሚጠምቁት ቢራ ላይ ጨው ይጨምሩ ነበር። ለነገሩ የሚጠመቅ ቢራ ሳይበላሽ ረዘም ላለ ጊዜ እንዲቆይ ፤ ጨው አስተዋጽዖ እንደሚኖረው ፤ የሥነ ቅመማው ሳይንስ የሚያረጋግጠው ነው።

በመግቢያችን ላይ በጨረፍታ እንዳነሳነው፣ ለምግብነት የሚውል ጨው አዮዲን ማዕድን ሊኖረው ይገባል። አለበለዚያ ፣ ከአንገት ዕጢዎች (ታይሮይድ ግላንድ )የተባለው በማበጥ ወደ እንቅርት ይለወጣል። ኢትዮጵያ ፣ በያመቱ ከ 313,000 እስከ 399,000 ቶን ጨው እንደምትጠቀም ይታሰባል። በአዮዲን እጥረት በሚከሠት የጤና መቃወስ ሳቢያ ፣ አንዳንድ የዜና ምንጮች እንደሚጠቁሙት፤ በእርግዝና ወቅት፤ 50 ሺ ያህል ሰዎች ናቸው ህይወታቸው የሚያልፈው። በተለይ ህዝብ በርከት ብሎ በሚኖርባቸው በአገሪቱ ደጋማ አካባቢዎችም ሆኑ አምባዎች፤ የአዮዲንና አንዳንድ ጠቃሚ ማዕድናት እጥረት መኖሩ የታወቀ ነው።

Salz wird in den Salinen von Janubio abgebaut
ምስል Fotolia

በአሁኑ ዘመን ጨውን መጠን ባለፈ መልኩ፣ በተለያየ መንገድ ሰዎች እንደሚመገቡትና ይህም የደም ግፊትን ከፍ እንዲል በማድረግ በጤንነት ላይ ሳንክ እየፈጠረ ስለመሆኑ፣ የጤና ሳይንስ ባለሙያዎች ከማስመገንዘብ የቦዘኑበት ጊዜ የለም። ጨው፣ ድንገተኛ የልብ ድካምና ተመሳሳይ ህመም እንደሚያስከትል፣ ብርቲቱ የደም ግፊትም እንደሚያስከትል ነው የሚነገርለት። ከሞላ ጎደል የደም ግፊታቸው ከመደበኛው ትንሽም ቢሆን ከፍ የሚልባቸው ሰዎች የሚመገቡትን የጨው መጠን በአጅጉ መቀነስ ይኖርባቸዋል።

በምዕራቡ ዓለም ፤ በአሁኑ ጊዜ፤ ግለሰቦች ብቻ ሳይሆኑ፤ የምግብና መጠጥ አዘጋጂ ኩባንያዎች ወይም ታላላቅ የምግብ መደብሮች፣ በየጊዜው የሚቀርበውን ጤና-ነክ መመሪያ ልብ በማለት ፣ የሶዲዬም ፍጆታ መጠን እጅግ ዝቅ እንዲል እርምጃዎችን እስከመውሰድ መድረሳቸው ይነገርላቸዋ። ጨው በይበልጥ የሶዲየም ይዘት ተቀንሶ ፣ የፖታሲዮም ፍጆታ እንዲጨምርም ነው ምክር የሚሰጠው። ፖታሲየም ፤ በመሠረቱ፤ የባቄላ ዝርዮች ከሆኑ ጥራጥሬዎች፤ ከአተር፣ ከለውዝ ዓይነቶች ከ«እስፒናች»፤ ሙዝ ፓፓያና ቴምር ጭምር ይገኛል።

በብዙ አዳጊ አገሮች፤ እጅግ ተፈላጊ ከሆነው ኢምንት የምግብ ዓይነት ይበልጥ እጥረት የሚያጋጥመው ፣ የ «ቪታሚን ኤ»፣ አዮዲንና የብረት ማዕድናት ናቸው።

ጨው በሰውነት ውስጥ እንዴት እንደሚከማች፤ በልዩ ተልእኮ የተረጋገጠበት ሁኔታ አስገራሚም ተብሏል።

Äthiopien Wüste Danakil
ምስል picture-alliance/dpa

እ ጎ አ በ 1997 ዓ ም፣ ወደ ኅዋ ተጉዘው በነበሩት ጀርመናዊው ጠፈርተኛ ራይንሆልድ ኤባልድ ላይ የተከሠተው እንደ አንድ ማስረጃ ይጠቀሳል። አንዳች የስበት ኀይል በሌለበት ሰውም እንደ ላባ በሚንሣፈፍበት ኅዋ፣ በሰውነት ውስጥ የምግብ ዓይነቶች የሚያሳዩት ለውጥ ምን ይመስላል? ኤባልድ፤ ለ 2 ሳምንት ወደ ኅዋ በበረራ ላይ ሳሉና እንደተመለሱም፤ የሚመገቡትን በዝርዝር መጻፍ ነበረባቸው።

«በበረራው ወቅት፣ በአመጋገቤ፤ በምጠጣውም ጥብቅ ቁጥጥር ነበረ ያደረግሁና የመዘገብሁ። ታዲያ አስገራሚ ሁኔታ ነበረ የተከሠተው። እወስደው የነበረ ው የጨው መጠን ፤ መሬት ላይ ከሚወሰደው ወይም በህክምና መጽሔት ከምናውቀው የተለየ ነበር።»

ጠፈርተኛው የተመገቡት ፤ የጠጡትና የዕዳሪአቸውም ይዞታ በሚገባ ይመረመር ፣ ይመዘን ነበረና አስገራሚ ሆኖ የተገኘው፤ በኅዋው የበረራ ወቅት ብዙ ጨው ሰውነት ውስጥ መጠራቀሙ ነው። አንድ ጤነኛ ሰው፤ ሰውነቱ ውስጥ፣ በ 6 ሊትር ፈሳሽ ነገር ውስጥ ሊኖረው የሚገባ የጨው መጠን ነበረውና!

ተመራማሪዎቹ፣ ጨው በአጠቃላይ በኩላሊት በኩል ተጣርቶ ከሽንት ጋር መወገድ እንደሚኖርበት ቢታወቅም፤ የሰው አካላት ተግባራቸውን ፣ ሁሌ በተለመደው መልክ ብቻ እንደማያከናውኑ ነበረ ተመራማሪዎቹ የተገነዘቡት። ጨው በሰውነት ውስጥ የፈሳሽ ነጥረ ነገርን ዝውውር ማስተካከል ብቻ ሳይሆን፤ ደም ግፊት ላይ ተጽእኖ አለው። በሌላም በኩል፤ በአጥንት ግንባታም መሟሸሽም ረገድ አስተዋጽዖ ያደርጋል። በሽታን የመከላከል ሚናም አለው።ግራም ነፈሰ ቀኝ፤ ይህ ጠቃሚ ማዕድን፣ በሚያስፈልግ መጠኑ እንጂ ከሚገባው በላይ የሚወሰድ ከሆነ ከጥቅሙ ጉዳቱ ስለሚያመዝን ጥንቃቄ ያሻል።

ተክሌ የኋላ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ