1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

መፍትሄ ያጣዉ የየመን ቀዉስ

ረቡዕ፣ ሚያዝያ 12 2008

በየመን ፕሬዚዳንት አብድ ራቦ ማንሱር ሃዲና በሁቲ አማፅያን ደጋፊዎች መካከል የተደረሰዉ የተኩስ አቁም ስምምነት ከሞላ ጎደል ለአንድ ሳምንት ፀንቶ ቆይቶአል። ባለፈዉ ሰኞ በተመ አደራዳሪነት የየመን አማፅያንና ዓለም አቀፍ እዉቅና ባገኘዉ መንግሥት መካከል ኩዌት ዉስጥ ሊደረግ የታቀደዉ የሰላም ድርድር ቀጠሮ ላልተወሰነ ጊዜ ተላልፎአል።

https://p.dw.com/p/1IZHY
Jemen Stammestreffen Unterstützer der Huthi Rebellen
ምስል picture-alliance/Photoshot/H. Ali

[No title]

ባለፈዉ ሰኞ በተመ አደራዳሪነት የየመን አማፅያንና ዓለም አቀፍ እዉቅና ባገኘዉ መንግሥት መካከል ኩዌት ዉስጥ ሊደረግ የታቀደዉ የሰላም ድርድርም መዘግየቱ ከተሰማ በኋላ በእርስ በርስ ጦርነት ለምትናጠዋ ለየመን ቀዉስ መፍትሄ የማግኘቱ ተስፋ የራቀ ሳይሆን እንደማይቀር ነዉ የሚነገረዉ።ወጣት፤ ጎልማሳ፤ በእድሜ ገፋ ያሉ በሽዎች የሚቆጠሩ ወንድ የሁቲ አማፅያን የተቃዉሞ ሰልፈኞች መዲና ሰንዓ ጎዳና ላይ ተሰብስበዋል። ሰልፈኞቹ ባህላዊዉን ሽርጥ አገልድመዋል፤ አንዳንዶች ደግሞ ባህላዊዉን አጠር ያለ ጎራዴ መሰል ነገር ወገባቸዉ ላይ ታጥቀዋል። አንዳንዶች ሰፊ የየመን ባንዲራ አንግበዋል ሌሎች በትልቅ ሰሌዳ ላይ የፃፉትን መፈክር ከግራ ወደቀኝ ያወዛዉዛሉ፤ በማይክሮፎን መፈክር ያሰማሉ።
ከአንድ ዓመት ከመፈንቅ ጀምሮ መዲና ሰነዓ በሁቲ አማፅያን እጅ ስር መዉደቅዋ ይታወቃል። ሌሎች አንዳንድ የየመን ከተሞች በአማፅያኑ እጅ ስር መሆናቸዉ ቢታወቅም ገሚሱ ዳግም በመንግሥት ቁጥጥሩ ስር አዉሎአቸዋል። አስር የአረብ ሃገራት የተጣመሩበት በሳዉዲ የሚመራዉ መራሹ የአየር ኃይል ደካማዉን የየመን መንግሥት በመደገፍ አማፅያኑ ወደ ሰሜናዊ የሃገሪቱ ክፍል እንዳይገቡ በመከላከል ላይ ነዉ። በየመን ፕሬዚዳንት አብድ ራቦ ማንሱር ሃዲና በሽዓ አማፅያን ደጋፊዎች መካከል የተደረሰዉ የተኩስ አቁም ስምምነት ግድፈት ቢኖረዉም ከአንድ ሳምንት ጀምሮ ዉሉ እንደፀና ይታወቃል። 9000 የመናዉያን ህይወታቸዉን ያጡበት ከየመኑ የ 13 ወራት ጦርነት በኋላ የየመን ተቀናቃኝ ወገኖች በሃገሪቱ ሰላም ለማስፈን ጥረት እያደረጉ ነዉ። የሁቲ አማፅያን ደጋፊ ሃሳን ዛይድ ያህያ እደሚሉት ከሆነ ግን ከሰላም ጥረቱ ምንም አይጠበቅም።
«ለዓለምና ለየመን ህዝብ የምናስተላልፈዉ መልዕክት የመንን ደግፉ እያልን ነዉ። የተኩስ አቁም ስምምነቱን እናከብራለን ። እነሱ ያፈርሳሉ።»
ሃሳን ዛይድ ያህያ « እነሱ» ያሉት የየመን ፕሬዚዳንት አብዶር ራቦ ማንሱር ሃዲን የሚደግፉትን የሳዉዲ ጥምር ኃይልን ማለታቸዉ ነዉ። ባለፈዉ የጎርጎሳዉያኑ 2015 መጋቢት ወር ፕሬዚዳንት አብዶር ራቦ ማንሱር ሃዲ የመንን ለቀዉ መሰደዳቸዉ ይታወቃል። ሃዲ በተሰደዱበት በሳዉዲ ዓረብያ ዉስጥ ቁጭ ብለዉ በየመን ክርነ ጠንካራ፤ ተሰሚነት ያለዉ ፖለቲከኛ ለመሆን ሞክረዋል። ፕሪዚዳንቱ በቅርቡ ባደረጉት የካቢኒ ለዉጥ ጠላቶቻቸዉን የሁቲ አማፅያንንና የኢራን ደጋፊዎቻቸዉን መቆጣጠር ይፈልጋሉ። የሁቲ አማፅያንን ከአየር የሚወጋዉ ሳዉዲ መራሹ ጦር በክዊት ለሚደረገዉ ድርድር ጥሩ ፍላጎት እንዳለዉ በዩኤስ አሜሪካ የየመን አንባሳደር አህመድ ኣዋድ ቢን ሙራክ ይገልጻሉ።
«ዴፕሎማቱ መሪት ላይ የሚታየዉ እዉነታ ተቀይሮአል ብለዋል። ሁቲ አማፅያንን በመዉጋት በቅርቡ ከተካሄደዉና ድል ከተገኘበት ወታደራዊ ርምጃ በኋላ የመንግሥት ልዑካኑ በድርድሩ የተደረጉትን ስምምነቶች ለማክበር ዝግጁ ናቸዉ።»
አሁን ወደ ድርድር የተመጣበት ምክንያት ምናልባት ለሳዉዲ መራሹ ጥምር ጦር፤ የየመኑ ጦርነት ብዙ ወጭን እያስከፈለዉ ይሆናል። በሳዉዲ የሚደገፈዉ የየመን ጦር ሰራዊት ከወራት በፊት ኤደን ከተማ እና በከፊል ታኢዝ ከተማን አስመልሰዋል። እንድያም ሆኖ ሰሜናዊ የሃገሪቱ ክፍል የተቆጣጠሩትን የሁቲ አማፅያን ማስለቀቅ ቀላል የሚሆን አይሆንም። በሌላ በኩል አማፅያኑም ቢሆኑ በጦርነት ብዙ ልምድ ያላቸዉ መሆኑ የማይታበል ሃቅ ነዉ። ባለፉት ወራት ሰሜናዊ የመንን የተቆጣጠሩት አማፅያን ደቡባዊዉን የየመን ክፍል ሲያጠቁ ተስተዉሎአል። ከዚህ ባሻገር ኧል-ቃይዳ በደቡባዊ የየመን ክፍል በሃገሪቱ ግዙፍ የተባለዉንና 600 ኪሎ ሜትር የሚሸፍነዉን ወደብ ተቆጣጥሮ ይገኛል።

Shiiten Jemen Houthis
ምስል picture-alliance/AP Photo/H.Mohammed
Jemen Luftangriffe in Sanaa
ምስል picture-alliance/AP Photo/Y. Arhab

የሁቲ አማፅያንና ተቀናቃኞቹ እየተዋጉ ባለበት ወቅት ኧል-ቃይዳ በደቡባዊ የመን ይዞታዉን ሊያስፋፋ ችሎአል። በክዌት የሚደረገዉ የሰላም ድርድር ስኬታማ ይሁን አይሁን የሚወሰነዉ የሁለቱ የየመን ተቀናቃኝ ቡድኖች ፍላጎት ላይ ብቻ ሳይሆን በሳዉዲ አረብያና በኢራን መንግሥታት ፍላጎትም ጭምር ነዉ እዉነታዉ። ሁለቱ መንግስታት አንዱ አንዱን በመደገፍ የየመን የርስ በርስ ጦርነት የዉክልና ጦርነት ማድረጋቸዉ እሙን ነዉ። ለሁቲ አማፅያን ቀረቤታ ያላቸዉ ሁለት የሚዲያ ባለስልጣናት እንደተናገሩት፤ በሳዉዲ አረቢያ የሚመራዉ ጦር የሚያደርገዉን የአየር ድብደባ ሙሉ በሙሉ እስካልቆመ ድረስ ለድርድር ክዌት ላይ ለሰላም ድርድር መቀመጡ ፋይዳ የለዉም ሲሉ መናገራቸዉ ሰኞ እለት ተገልፆአል።


አነ አልሜሊንግ / አዜብ ታደሰ

ነጋሽ መሐመድ