1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ኤርትራ ወደ ኢትዮጵያ ልዑካን እንደምትልክ አስታወቀች 

ረቡዕ፣ ሰኔ 13 2010

የኤርትራው ፕሬዝደንት ኢሳያስ አፈወርቂ ኢትዮጵያ ላቀረበችው የሰላም ጥሪ ሁኔታዎችን የሚያጣራ የልዑካን ቡድን ወደ ኢትዮጵያ ለመላክ መዘጋጀታቸው አስታቁ። ልዑካኑ የሚሄዱት ለሰላም ጥረቱ አዎንታዊ አስተዋፅኦ ለማድረግ መሆኑም ተገልጿል።

https://p.dw.com/p/2zuZl
Eritrea Präsident Isaias Afwerki
ምስል Eritrea Minister of Information/Y.G. Meskel

የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ይህን የተናገሩት ዛሬ በኤርትራ እየተከበረ በሚገኘዉ በ 20ኛዉ የሰማዕታት መታሰቢያ ዝግጅት ላይ ባደረጉት ንግግር ነዉ። አክለውም ከኢትዮጵያ በኩል ባለፉት ቀናት የተሰሙት አዎንታዊ ምልክቶች የኅብረተሰቡ ግልፅ ምርጫ መሆኑን እንደሚያመላክትም ገልጸዋል። በኬንያ የኤርትራ አምባሳደር በየነ ርዕሶም በበኩላቸው በሁለቱ ሃገራት መካከል አዲስ የሰላም እና የእርቅ ምዕራፍ መከፈቱን መግለፃቸውን አሶሲየትድ ፕረስ ዘግቧል። የኤርትራዉ የማስታወቂያ ሚኒስትር አቶ የማነ ገብረመስቀልም በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል የሚካሄድ የትብብር ሥራ የሁለቱን ሃገራት የሁለትዮሽ ግንኙነት ብቻ ሳይሆን በአፍሪቃዉ ቀንድ አካባቢ ያለዉንም እድገት እንደሚጠናክር በትዊተር መልዕክታቸው ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያና ኤርትራ መካከል በነበረዉ ዉዝግብም የሁለቱ ሃገራት ሕዝብ ሁለት ትዉልዶች የግማሽ ምዕተ ዓመት ዕድልን አጥተዋልም ብለዋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አሕመድ ኤርትራ ለሰጠችዉ አዎንታዊ አፀፋ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂን ማመስገናቸዉን የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፍፁም አረጋ በትዊተር መልክታቸዉ ይፋ አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ለኤርትራ ልዑካንም መልካም አቀባበል ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውን ማስታወቃቸውንም አቶ ፍፁም ጠቅሰዋል።   

21.01.2013 Karte Eritrea Asmara eng


አዜብ ታደሰ


ሸዋዬ ለገሠ