1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
ውዝግቦችአፍሪቃ

እረብሻ ያደፈረሰው የደን ሃጉ የኤርትራውያን ፌስቲቫል

ሰኞ፣ የካቲት 11 2016

በኔዘርላንዷ የደን ሃግ ከተማ ባሳለፍነው ሳምንት መጨረሻ የተካሄደው የኤርትራውያን ፌስቲቫል በእረብሻ መደርፍረሱ መነጋገሪያ ሆኗል። የኤርትራ መንግሥት ደጋፊዎች እና ተቃዋሚዎች በተጋጩበት በትናንትናው ዕለት ስድስት የኔዘርላንድ ፖሊሶች መጎዳታቸውን እና ከባድ የንብረት ጉዳት መድረሱን የሀገሪቱ ፖሊስ አስታውቋል።

https://p.dw.com/p/4cZmH
ኔዘርላንድ፤ ደንሃግ ከተማ
በኔዘርላንድ ደንሃግ ከተማ በኤርትራውያን ፌስቲቫል ላይ የተነሳውን ብጥብጥ ተከትሎ ከደረሰው ጉዳት በከፊል፤ ምስል ANP/picture alliance

እረብሻ ያደፈረሰው የደን ሃጉ የኤርትራውያን ፌስቲቫል

በኔዘርላንዷ የደን ሃግ ከተማ ባሳለፍነው ሳምንት መጨረሻ የተካሄደው የኤርትራውያን ፌስቲቫል በእረብሻ መደርፍረሱ መነጋገሪያ ሆኗል። የኤርትራ መንግሥት ደጋፊዎች እና ተቃዋሚዎች በተጋጩበት በትናንትናው ዕለት ስድስት የኔዘርላንድ ፖሊሶች መጎዳታቸውን እና ከባድ የንብረት ጉዳት መድረሱን የሀገሪቱ ፖሊስ አስታውቋል። ድግሱ በተዘጋጀባት ከተማ ትናንት ምሽቱን በተፈጠረው ብጥብጥ ፖሊሶች እና የአደጋ ጊዜ ፈጥኖ ደራሽ ሠራተኞች ላይ ሳይቀር በድንጋይ እና ርችት መወርወሩም ተገልጿል። ሁለት የፖሊስ መኪኖች ሙሉ በሙሉ ሲቃጠሉ፤ ሌሎች ተሽከርካሪዎችም ከባድ ጉዳት እንደደረሰባቸው ነው ዘገባዎች ያመለከቱት። የኤርትራመንግሥት ደጋፊዎች መሆናቸው የተገለጸው የበአሉ አዘጋጆች ድግስ ያዘጋጁበት ማዕከልም ጉዳት እንደደረሰበት የጀርመን የዜና ወኪል ዲፒኤ በዘገባው ጠቅሷል። የድግሱ ታዳሚዎች በሙቀት እና ጭስ መጎዳታቸውንም ገልጿል። ብጥብጡን ለመበተን የኔዘርላንድ አድማ በታኝ ፖሊሶች አስለቃሽ ጭስ መጠቀሙንም አመልክቷል። ከብጥብጡ ጋር በተገናኘ ዕድሜያቸው ከ13 እስከ 36 ዓመት የሚደርስ 13  ወንዶች መታሰራቸውን ፖሊስ አስታውቋል። ድርጊቱ በኔዘርላንድ መገናኛ ብዙሃን ከፍተኛ መነጋገሪያ ከመሆኑም በላይ የስደተኞች ጥላቻ ያላቸው ፓርቲዎች ጉዳዩ የእነሱን አቋም ትክክለኛነት ማሳያ እንዳደረጉት እየታየ ነው። በአንጻሩ ድርጊቱ ለስደተኞች ድጋፍ የሚሰጠውን ኅብረተሰብ ክፉኛ እንዳሳዘነም የብራስልሱ ዘጋቢያችን ገልጾልናል።

ገበያው ንጉሤ

ሸዋዬ ለገሠ

ኂሩት መለሰ