1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

አዲስ አበባ፤ በተመድ የዩናይትድ ስቴትስ አምባሳደር ኒኪ ሄይሌ ኢትዮጵያ ገብተዋል፤

ሰኞ፣ ጥቅምት 13 2010

በተመድ የዩናይትድ ስቴትስ አምባሳደር ኒኪ ሄይሊ በዛሬዉ ዕለት ለጉብኝት አዲስ አበባ ገቡ። የአምባሳደር ሄይሊ ጉብኝት በፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ሥር ከአፍሪቃ ክፍለ ዓለም ጋር በቀጣይ የሚኖር እቅድ ምንነትን ግልፅ ሊያደርግ እንደሚችል ሮይተርስ ከአዲስ አበባ በላከዉ ዘገባ ጠቁሟል።

https://p.dw.com/p/2mMjX
Äthiopien Nikki Haley in Addis Abeba
ምስል DW/Getachew Tedla

የአምባሳደር ኒኪ ሔይሌ ጉብኝት

ባለፈዉ ሳምንት አምባሳደሯ ኒዉዮርክ ላይ ጉብኝታቸዉን አስመልክተዉ፤ ፕሬዝደንቱ ወደአፍሪቃ የሚልኳቸዉ በፕሬዝደንት ጆርጅ ደብሊዮ ቡሽ አስተዳደር የተጀመረዉን ለመደገፍ ነዉ ማለታቸዉንም ዘገባዉ ጠቅሷል። አምባሳደሯ በኢትዮጵያ፣ ደቡብ ሱዳን እና ዴሞክራቲክ ሪፑብሊክ ኮንጎ በሚያደርጉት ጉብኝት የመንግሥታቱ ድርጅትን እንቅስቃሴ በጥንቃቄ እንደሚመለከቱ በጽሑፍ አመልክተዋል። ፕሬዝደንት ትራምፕ በበኩላቸዉ በደቡብ ሱዳን እና ኮንጎ ዉስጥ ሰላም የሚሰፍንበትን መንገድ እንዲያመቻቹ እንደሚልኳቸዉም ማመልከታቸዉን ዘገባዉ አስታዉሷል። 

አምባሳደሯ የደቡብ ሱዳን እና የዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ መንግሥታትን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የገንዘብ ድጋፍ አጠቃቀም እንደሚመረምሩ በሀተታቸው ገልጠዋል። "የተባበሩት መንግሥታት በሁለቱ አገራት ለሰላም ማስከበር ተልዕኮ ከ2 ቢሊዮን ዶላር በላይ ወጪ ያደርጋል" ያሉት ሄይሌ የምንሰጠው ገንዘብ ለችግረኞች እንዳይደርስ የሚገታ ከሆነ አንቀጥልበትም ሲሉ አስጠንቅቀዋል። 
"ዩናይትድ ስቴትስ በጦርነት በታመሱት አገሮች ሰብዓዊ፣ ኤኮኖሚያዊ እና ሥልታዊ ጥቅም አላት" ሲሉም ጽፈዋል። ሄይሊ በደቡብ ሱዳን ቀጥሏል ያሉትን ኹከት እና የዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን ማባሪያ ያጣ ቀውስ ጠቅሰው በርካታ የአፍሪቃ አገሮች ፈተናዎች ውስጥ መሆናቸውን ጠቁመዋል። 
ጌታቸው ተድላ ኃይለጊዮርጊስ 
እሸቴ በቀለ
አርያም ተክሌ