1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
ሳይንስ

ሀዋሳ ዩኒቨርስቲ ለአራት ምሁራን የፕሮፌሰር ማዕረግ ሰጥቷል

ረቡዕ፣ ነሐሴ 17 2009

ባለፈው ሳምንት የአዲስ አበባ እና የሀዋሳ ዩኒቨርስቲዎች ለ10 ምሁራን የፕሮፌሰርነት ማዕረግ ሰጥተዋል፡፡ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ዩኒቨርስቲዎች ውስጥ ያሉ ፕሮፌሰሮች ግን ጥቂት መሆናቸውን የሚጠቆሙት የዘርፉ ባለሙያዎች በአንድ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ሊኖር ይገባል ከሚባለው ቁጥር ጋር ሲነጻጸር ከፍተኛ ክፍተት እንደሚስተዋል ይጠቁማሉ፡፡

https://p.dw.com/p/2iisS
Symbolbild Literatur Bücherstapel
ምስል Fotolia/silver-john

የሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ እና የፕሮፌሰርነት ማዕረግ አሰጣጥ

በአንጋፋው አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ እና በሐዋሳ ዩኒቨርስቲ መካከል 50 ዓመት ገደማ ልዩነት አለ፡፡ ሰላሳ ሶስት ተማሪዎች ተቀብሎ ማስተማር የጀመረው አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ አሁን 50 ሺህ ተማሪዎች ትምህርት የሚገበዩበት ተቋም ሆኗል፡፡ ከተቋቋሙ 40 ዓመት የሞላቸውን ኮሌጆች ጭምር በውስጡ ያቀፈው ሀዋሳ ዩኒቨርስቲ በበኩሉ 40 ሺህ ገደማ ተማሪዎች እያስተናገደ ነው፡፡ ሁለቱም ዩኒቨርስቲዎች ከዓመት ዓመት የሚሰጧቸውን የትምህርት ዘርፎች እያስፋፉ፣ የቅበላ አቅማቸውንም እያሳደጉ ቢመጡም የሚጋሩት መሰረታዊ ችግር አለ፡፡ 

ሁለቱም አንድ ከፍተኛ የትምህርት ተቋም ሊኖረው የሚገባውን ያህል የዶክትሬት ዲግሪ የያዙና እና የፕሮፌሰርነት ማዕረግ ላይ የደረሱ በርካታ ምሁራን የላቸውም፡፡ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ካሉት መምህራን መካከል የሙሉ ፕሮፌሰሮች ቁጥር ከሶስት በመቶ እንደማይበልጥ ሰሞኑን የወጣ አንድ መረጃ ይጠቁማል፡፡ በሐዋሳ ዩኒቨርስቲ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ሙሉ የፕሮፌሰርነት ማዕረግ ያላቸው ምሁራን ዘጠኝ ብቻ ነበር፡፡ 

Äthiopien Universität Adis Ababa
ምስል picture alliance/robertharding/M. Runkel

ለመሆኑ በአንድ ዩኒቨርስቲ ውስጥ ካሉ ምሁራን መሀል ምን ያህሉ ሁለተኛ ዲግሪ፣ ምን ያህሉ የዶክትሬት ዲግሪ ማዕረግ ሊኖራቸው ይገባል? ፕሮፌሰሮች? በሀዋሳ ዩኒቨርስቲ የፖሊሲ እና ልማት ተቋም ዳይሬክተር እና በስነ-ትምህርት ዘርፍ የተመረቁት ፕሮፌሰር ተስፋዬ ሰመላ ምላሽ አላቸው፡፡   

“ፕሮፌሰር ሳይሆን ፒ.ኤች.ዲ (ዶክትሬት) ዲግሪ ከ20 እሰከ 30 በመቶ መሆን አለበት፡፡ ቢያንስ 30 በመቶ መሆን አለበት ነው፡፡ ያ ማለት 30 በመቶ ፒ.ኤች.ዲ፣ 40 በመቶው ሁለተኛ ዲግሪ ያለው መሆን አለበት፡፡ ምክንያቱም አስተማሪ የሚባለው እኛ ጋር (መምህር ነው የሚባለው) የሁለተኛ ዲግሪ ያለው ማለት ነው፡፡ የመጀመሪያ ዲግሪ ያላቸው በቴክኒካል ረዳትነት ወይም በቤተ ሙከራ ውስጥ እና ረዳት መምህራን ናቸው፡፡ ዋናውን መምህር የሚረዱ ናቸው” ይላሉ ፕሮፌሰር ተስፋዬ፡፡ 

በንደፈ-ሀሳብ ደረጃ ይህ ቢቀመጥም በተግባር ያለው ግን ተቃራኒው እንደሆነ በዩኒቨርስቲው የሚያስተምሩ መምህራን ይናገራሉ፡፡ በሐዋሳ የኒቨርስቲ ያሉ ፕሮፌሰሮች በአጠቃላይ ካሉት መምህራን ጋር ሲነጻጸሩ አንድ በመቶ ብቻ እንደሚሆኑ ይገልጻሉ፡፡ ዩኒቨርስቲው ይህን ለመቀየር ያሰበ እርምጃ ባለፈው ሳምንት ወስዷል፡፡ በምርምር ስራዎቻቸው እና ባበረከቱት አስተዋጽኦ የላቀ ውጤት አስመዘግበዋል ላላቸው አራት አንጋፋ ምሁራን የሙሉ ፕሮፌሰርነት ማዕረግ እንዳጎናጸፈ ይፋ አድርጓል፡፡ 

ከሀዋሳ ዩኒቨርስቲ መግለጫ ሁለት ቀን ቀደም ብሎ በሀገሪቱ የመጀመሪያ የሆነው የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የስራ አመራር ቦርድ ለስድስት ምሁራን የፕሮፌሰርነት ማዕረግ ማጽደቁን አስታውቆ ነበር፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ለምሁራኑ ማዕረጉን የሰጠው በየትምህርት ጉባኤዎች ተፈትሾ እና በሴኔት ይሁንታ አግኝቶ እንደሆነ ገልጿል፡፡ የሐዋሳ ዩኒቨርስቲም ተመሳሳይ ሂደት መከተሉን የዩኒቨርስቲው የአካዳሚክ ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ፍስሀ ጌታቸው ይናገራሉ፡፡ 

“የፕሮፌሰርነት ማዕረግ ቅድሚያ የሚጀምረው ከትምህርት ክፍል ነው፡፡ ትምህርት ክፍሉ የራሱ መማክርት (council) አለው፡፡ [ምሀራኑ] ከመማክርቱ የድጋፍ አስተያየት ማግኘት ይጠበቅባቸዋል፡፡ የትምህርት ክፍሉ የድጋፍ አስተያየት ከሰጠላቸው በኋላ በኮሌጆቻቸው አካዳሚክ ኮሚሽኖች ተመርምሮ ድጋሚ የድጋፍ አስተያየት ማግኘት ያስፈልጋል፡፡ በኋላም በሴኔት ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው፣ በሴኔት እንዲሁም በዩኒቨርስቲው ቦርድ የመጨረሻውን ውሳኔ የሚያገኝ ረጅም ሂደት ያለው፣ በመምህራኑ ብቃት ላይ የተመረኮዘ የአካዳሚክ ማዕረግ ነው” ይላሉ ምክትል ፕሬዝዳንቱ፡፡

Symbolbild Literatur Bücherstapel
ምስል Fotolia/silver-john

ለፕሮፌሰር ማዕረግ የታጩ መምህራን የሚመዘኑባቸው አራት መስፈርቶች እንዳሉ የሚናገሩት ዶ/ር ፍስሀ እንደሚከተለው ይዘረዝሯቸዋል፡፡ 

“የመጀመሪያው መስፈርት ተባባሪ ፕሮፌሰር (associate professor) ሆነው ያገለገሉበት ዓመት ነው፡፡ በዩኒቨርስቲያችን ውስጥ ተባባሪ ሆነው በትንሹ ሊያገለግሉ የሚገባው የዓመት ብዛት አራት ነው፡፡ በብቃት አራቱን ዓመት የፈፀሙ፣ በተማሪዎች፣ በመምህራን፣ በስራ ጓዶቻቸው፣ በትምህርት ክፍል መሪዎች፣ በዲኖች ግምገማ እርሱን የጨረሱ መሆን አለባቸው፡፡ ለፕሮፌሰርነት ግምገማ ግን ከዚያም በላይ ብቃታቸው በተረጋገጠ ጆርናሎች ላይ ያሳተሙት ሳይንሳዊ ጽሁፍ ጽሁፍ ብዛት ይታያል፡፡ እነዚህ የምርምር ጽሁፎች በዓለም አቀፍ ደረጃ በታወቁ ባለሙያዎች በድጋሚ ይገመገማሉ፡፡ በሶስተኛ ደረጃ ደግሞ በዩኒቨርስቲው ውስጥ ከማስተማር ስራ በተጨማሪ የሰሩት ሌሎች ስራዎችም እንደታሳቢ ይታያሉ፡፡ አራተኛ እና የመጨረሻው ከዩኒቨርስቲ ውጭ ለህብረተሰቡ ምን ስራ ሰርተዋል የሚለው ነው፡፡ እነዚህ ነገሮች በሙሉ ተካትተው ወደ ቁጥር በዩኒቨርስቲው ደንብ መሰረት ደግሞ ይቀየራሉ፡፡ በድምር ውጤታቸው ከ80 በመቶ በላይ ያገኙ ወደ ፕሮፌሰርነት ማዕረግ እንዲያድጉ ይደረጋል” ሲሉ ያስረዳሉ ዶ/ር ፍስሀ፡፡  

በዚህ አይነት በርከት ያሉ ማጣሪያዎች ባሉት ሂደት ውስጥ አልፈው ባለፈው ሳምንት የፕሮፌሰርነት ማዕረግ ካገኙት አራት የሀዋሳ  ዩኒቨርስቲ ምሁራን መካከል አንዱ ዶ/ር ካሳሁን አስማረ ናቸው፡፡ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በ1989 ዓ.ም በእንስሳት ህክምና የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ያገኙት ዶ/ር ካሳሁን ላለፈው 20 ዓመት በዘርፉ በማስተማር እና በምርምር ላይ ቆይተዋል፡፡ የዛሬ አራት ዓመት ከኖርዌይ የእንስሳት ህክምና ሳይንስ ተቋም ፒ.ኤች.ዲያቸውን አግኝተዋል፡፡ 

በሀዋሳ ዩኒቨርስቲ የእንስሳት ህክምና ትምህርት ክፍል የበሽታ ስርጸት (epidemiology) መምህር የሆኑት ዶ/ር ካሳሁን ወደ 40 የሚጠጉ የምርምር ጽሁፎችን በታወቁ የሳይንስ መጽሔቶች (ጆርናሎች) ላይ አሳትመዋል፡፡ የፕሮፌሰር እጥረት በሚታይበት ዩኒቨርስቲያቸው ውስጥ ማዕረጉን ለማግኘት ረጅም ጊዜ ወስዶባቸው እንደው ጠይቄያቸው ነበር፡፡ ለበርካታ ዓመታት በየዩኒቨርስቲው ሲያስተምሩ የቆዩ ምሁራን ይህን ማዕረግ ማግኘት ያልቻሉበትን ዋነኛ ምክንያቶች ከራሳቸው ጋር እያነጻጸሩ ያስረዳሉ፡፡ 

“ምርምር መሰጠት ይፈልጋል፡፡ በማተማር ተቋም ውስጥ ለረጅም ጊዜ መኖርህ አይመስለኝም ትልቁ ነገር፡፡ በዚያ ጊዜ ውስጥ ምን ያህል በምርምር ስራ ላይ አተኩረሃል? ምን ያህልስ እነዚያን የምርምር ውጤቶች ለሳይንስ ማህበረሰቡ አስተዋውቀሃል? የሚሉት ይመስለኛል፡፡ አንዳንድ ሰዎች በአጭር ጊዜ ብዙ ነገሮች ይሰራሉ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ረጅም ጊዜ ይፈልጋሉ፡፡ ስለዚህ እኔ የማየው በዚህ ምርምር ላይ ትኩረት የመሆን ጉዳይ በርካታ ምክንያቶች ይኖሩታል፡፡ ለምሳሌ በሳይንስ አካባቢ ያሉ ምርምሮች ገንዘብ ይፈልጋሉ፡፡ ገንዘብ ደግሞ እንደፈለግኸው አታገኝም፡፡ ፋሲሊቲዎች ይፈልጋሉ፡፡ እነዚያ ፋሲሊቲዎች አይኖሩም፡፡ ለምሳሌ እኔ እንደ ዕድል ሆኖ ኖርዌይ ካስተማሩኝ መምህራን ጋር፣ ሀገር ቤት ደግሞ ብሔራዊ የእንስሳት ህክምና ኢንስቲትዩት ካሉ ተመራማሪዎች ጋር ጥሩ ግኝኑነት እና የምርምር ቡድን ስላለን ለእኛ ከገንዘብ ውጭ ያለ ተግዳሮት አልነበረም፡፡ እና በዚህ የተነሳ የምርምር ወረቀቶችን በተሻለ ፍጥነት መጻፍ ችለናል፡፡ የምርምር ስራዎችን ማቀላጠፍ ችለናል፡፡ እኔ እድለኛ ነኝ ብዬ አስባለሁ፡፡  እዚህ ማዕረግ ላይ ለመድረስ በጣም ብዙ ጊዜ ሰርተዋል፡፡ በጣም ብዙ ጊዜ ደክመዋል፡፡ እና ከእነሱ አንጻር ሲታይ የእኔ ረጅም ነው ብዬ መናገር ትንሽ ይከብደኛል” ይላሉ ዶ/ር ካሳሁን፡፡

Äthiopien Mekelle University in Mek'ele - Tiermiedizin
ምስል DW/Y. Geberegziabeher

የሙሉ ፕሮፌሰርነት ማዕረግን ለማግኘት በኢትዮጵያ ዩኒቨርስቲዎች ያሉ መምህራን ለዓመታት ከመጠበቃቸው አንጻር ሲታይ በእርግጥም ዶ/ር ካሳሁን እድለኛ ናቸው ያስብላል፡፡ ሀዋሳ ዩኒቨርስቲው ሙሉ የፕሮፌሰርነት ማዕረግ የሰጣቸው ለትምህርት ክፍላቸው ባመለከቱ አንድ ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ ለ27 ዓመት በተለያዩ ደረጃዎች በማስተማር ስራ ላይ የቆዩት እና ከስድስት ዓመት በፊት በዚያው በሀዋሳ ዩኒቨርስቲ የፕሮፌሰርነት ማዕረግ ያገኙት ፕሮፌሰር ተስፋዬ ግን ክብሩን ለማግኘት ዓመታት መጠበቃቸውን ይናገራሉ፡፡ የፕሮፌሰሮች እጥረት እያለ ለምን መምህራንን ዓመታት ማስጠበቅ አስፈለገ ስንል የሀዋሳ ዩኒቨርስቲ የአካዳሚክ ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ፍስሀን ጠይቀናቸው ነበር፡፡ ተከታዩን ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ 

“የፕሮፌሰር [ማዕረግን] ለመስጠት የሚታይበት አግባብ በርካታ ነው፡፡ ብዙ ሰዎች የሚያዩት፣ ብዙ ሰዎች አጽድቀውት የሚያልፍ ነው፡፡ ሲጀምር ከትምህርት ክፍሉ መማክርት ነው፡፡ ከሚያስተምርበት ትምህርት ቤት ተቀባይነት አግኝቶ ወደ ኮሌጁ አካዳሚክ ኮሚሽን፣ ወደ ሴኔት ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ፣ ወደ ሴኔት፣ እንዲሁም ወደ ቦርድ ሲሄድ ሂደቱ ረዘም ሊል ይችላል፡፡ የረዘመበት የምዘና ሂደቱ ሰፊ ስለሆነ ነው፡፡ ብቃትን ማረጋገጥ አስፈላጊ ስለሆነ ነው፡፡ በውጪ ሁሉ ባለሙያዎች፣ ከኢትዮጵያ ውጪ ባሉ ፕሮፌሰሮች የምርምር ጽሁፎቻቸው ይገመገማል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ከእኛ ቁጥጥር ውጭ ነው፡፡ ውጪ ያለ ፕሮፌሰር ጽሁፎቹን ገምግሞ ለመላክ እስከ አንድ ወር ሊፈጅበት ይችላል፡፡ በፍጥነት የሚያልቅ ነገር አይደለም፡፡ ነገር ግን ከዓመት በላይ ከሆነ ዘገየ ማለት ይቻላል፡፡ ዓመት አካባቢ መደበኛ ይመስለኛል፡፡ እንደ ሀዋሳ ዩኒቨርስቲ አሰራር በአማካይ ዓመት ነው [የሚወስደው]፡፡ አሁን በጀመርነው ስርዓት ከአሁን በኋላ በፍጥነት ለመስራት፣ ይሄንን የሚፈጀውን ጊዜ እንቀንሳለን ብለን ነው የምናስበው፡፡ በእርግጥም ደግሞ እንቀንሰዋለን፡፡” 

“ፕሮፌሰሮች ዩኒቨርስቲያችን ውስጥ እጅግ በጣም ያስፈልጋሉ፡፡ ዩኒቨርሲቲያችን በአሀኑ ጊዜ ከ200 በላይ ፒ.ኤች.ዲ ያላቸው ሰራተኞች አሉት፡፡ እነዚህ መምህራን በሚሰሩት የምርምር ውጤት ቀስ እያሉ ወደ ፕሮፌሰር ደረጃ የሚያድጉ ነው የሚሆነው፡፡ ፕሮፌሰር ሲሆኑ ሲሆኑ ደግሞ በዩኒቨርስቲያችን ውስጥ ያሉትን የፒ.ኤች.ዲ ተማሪዎች የማማከር፣ የመደገፍ፣ የምርምር ስራዎቻቸውን ሁሉ የማገዝ የፕሮፌሰሮቻችን ዋና ኃላፊነት ነው የሚሆነው፡፡ ዩኒቨርስቲያችን ወደ ምርምር ዩኒቨርስቲ ቀስ እያለ እየተሸጋገረ ስለሆነ ወደፊት በርካታ ፕሮፌሰሮች እንፈልጋለን፡፡”

ምሁራን የፕሮፌሰርነትን ማዕረግ ከተጎናጸፉ በኋላ ለተቋሞቻቸው እና ለህብረሰተቡ ማበርከት ስለሚጠበቅባቸው ጉዳዮች ፕሮፌሰር ተስፋዬ በዝርዝር ያስረዳሉ፡፡ 

Symbolbild Weiterbildung Beruf
ምስል Fotolia/Africa Studio

“አንደኛ ችግር ፈቺ የሆኑ ምርምሮችን መካሄድ መቻል ነው፡፡ ማካሄድ ብቻ ሳይሆን በስራቸው ያሉ ለምሳሌ በዶክትሬት ዲግሪ ደረጃ የሚሰለጥኑ ተማሪዎችን ይዞ ማሰልጠን አለበት፡፡ ሰዎችን ማፍራት አለበት፡፡ የዚያን ብቃት መላበስ አለበት፡፡ በፒ.ኤች.ዲ ደረጃ ተማሪዎችን፣ ያማክራል፣ ያስመርቃል፣ ጥራቱን በጠበቀ መልኩ አሰልጥኖ የምርምር ብቃታቸውን በሙያው ያለ አስፈላጊ ክህሎቶችን ጨብጠው እንዲወጡ እና ወዲት ብቻቸውን ራሳቸውን ችለው የሚመራመሩ ዜጎችን ማፍራት አለበት፡፡ አንድ ሰው ፕሮፌሰር ሲሆን እነዚህን ማድረግ አለበት፡፡ እርሱ ስለሰራ እና ስለሆነ ነገር ስላሳተመ ብቻ ፕሮፌሰር የሚሆን ከሆነ ትርጉም አልባ ነው የሚሆነው፡፡ ትርጉም የሚኖረው እርሱ የሚያፈራው ሰው መኖር አለበት፡፡ ራሱን መተካት አለበት፡፡ ራሱን ሲተካ እንደውም ከእርሱ በተሻለ መንገድ ነው ምክንያቱም ሳይንሱም እያደገ ስለሚሄድ አዳዲስ ብቃቶችን እየተላበሰ፣ ራሱም እየተማረ፣ እነርሱን እያስተማረ፣ ለእነርሱ ደግሞ ሰፊ የመማር እና የመመራመር ዕድል ሰጥቶ ጥሩ የሆኑ ተመራማሪዎችን ማፍራት አለበት፡፡ ለእኔ ያ ነው ፕሮፌሰር ማለት” ሲሉ ይደመድማሉ ፕሮፌሰር ተስፋዬ፡፡ 

 

ተስፋለም ወልደየስ

ነጋሽ መሐመድ