1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ማሕደረ-ዜና፤ ዘመቻ-ሙሴ 30ኛ ዓመት

ሰኞ፣ ኅዳር 22 2007

ኢትዮጵያም -በአብዮትና ፀረ-አብዮት ግብግብ ትናወጥ ነበር።የሶማሊያ ጦርም ገሚስ ኢትዮጵያን ለመያዝ ምሥራቅና ደቡባዊ ኢትዮጵያን ተቆጣጠረ።የአብዮቱ ትርምስ፤ የኢትዮ-ሶማሊያ ጦርነት፤ የዩናይትድ ስቴት መንግሥት ፀረ-ኢትዮጵያ አቋም መያዝ፤ ለቤገን ዕቅድና ቃላቸዉን ገቢር ለማድረግ ጥሩ አጋጣሚ ነበር።

https://p.dw.com/p/1Dxnq
ምስል Getty Images

አንድ ነገር እንዲደረግ ተወሰነ።ሞሳድ፤ ሲ አይ ኤና የሱዳኑ የሥለላ ድርጅት (SSS) ዉሳኔዉን ገቢር ለማድረግ ይጣደፉ ያዙ።ሕዳር 21 1984 (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳዉያኑ አቆጣጠር ነዉ) የመጀመሪያዎቹን ቤተ እስራኤላዉያንን ያሳፈረዉ አዉሮፕላን ከሱዳን በብራስልስ-ቤልጅግ አድርጎ እስራኤል ገባ።ዘመቻ ሙሴ ተጀመረ።ባለፈዉ ሳምንት 30 ዓመቱ።የዘመቻዉ ምክንያት፤ ሒደትና ዉጤት ያፍታ ዝግጅታችን ትኩረት ነዉ አብራቸሁን ቆዩ።

እስራኤል እንደ ሐገር ከተመሠረተች ከ1948 ጀምሮ የተፈራረቁት የሐገሪቱ መሪዎች ከመመሥረቷ በፊት እንደነበረዉ ሁሉ በመላዉ ዓለም የተበተነዉን የሁዳዊ ወደ ቅድስቲቱ ምድር ሲያሰባስቡ ነበር።ቤተ-እስራኤሎችን ግን ብዙም ያስታወሳቸዉ አልነበረም።ቤተ እስራኤላዉኑ ግን ያቺን ምድር ለዘመነ-ዘመናት እዳለሙ፤ እንደተመኟት ነዉ።እየሩሳሌምን እደናፈቁ-ትዉልደ ትዉልድ አሳልፈዋል-ሁለት ሺሕ ዘመን።

ጋዜጠኛ ራሐሚም አልአዛር።እሱ በርግጥ ከብዙዎቹ ቀድሞ እስራኤልን አያት-1972።ያኔዉ ታዳጊ ወጣት እስራኤል ተማረ-ኖረባትም።በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ ቤተ-እስራኤላዉን ስድስተኛዉ የእስራኤል ጠቅላይ ሚንስትር ሜናሔም ቤገን የዚያን ቀን የተናገሩትን ሊሰሙ ቀርቶ ቤገን የሚባል ፖለቲከኛ ሥለመኖሩ የሚያዉቁት እንኳ ጥቂት ናቸዉ።

እስከ ቤገን ድረስ የተፈራረቁት አምስት የእስራኤል ጠቅላይ ሚንስርቶች አዉሮጳ፤ ሰሜንና ደቡብ አሜሪካ፤በበርካታ አረብ ሐገራትና ሌላም ሥፍራ የሚኖሩ የሁዲ ወገኖቻቸዉን ከያሉበት ወደ እስራኤል አስወስደዋል።ቤግን-ከሌሎቹ ለየት ባሉት ላይ አተኮሩ።ቤተ-እስራኤሎች።የእስራኤልና የኢትዮጵያ ሐይማኖታዊ፤ ፖለቲካዊና ማሕበራዊ ሁነቶችም ለቤገን ትኩረት ጥሩ መደላድል ሆነዉ ነበር።

Karte Äthiopien englisch

ሐላኺክ (የራባዮች ጉባኤ) ኢትዮጵያዉያኑ የሁዲዎች የሚከተሉት እምነት የዩሁዲ ሐይማኖት አካል መሆኑን አፀደቀ።1977።የሁዲዎች ወደ እስራኤል እንዲመለሱ የሚደነግገዉ የእስራኤል ሕግ ቤተ-እስራኤላዉያንንም እንዲያክትት የሐገሪቱ ባለሥልጣናት ወሰኑ።መጋቢት 14 1977።በሰወስተኛ ወሩ ቤገን የጠቅላይ ሚንስትርነቱን ሥልጣን ያዙ።ሰኔ-1977።ቤተ-እስራኤላዉያንን ወደ እስራኤል ለማስገባት እንደሚጥሩ ቃል ገቡም።

ከኢትዮጵያ በተለያዩ አጋጣሚዎች ወጥተዉ እስራኤልና አሜሪካ የሚኖሩ ቤተ-እስራኤላዉያንና ተባባሪዎቻቸዉ ቁጥራቸዉ ትንሽ ቢሆንም ወላጅ፤ ወዳጅ ዘመዶቻቸዉ ወደ ቅድስቲቱ ምድር እንዲመጡላቸዉ የሚያደርጉት ግፊትም ተጠናከረ።እሱ አንዱ ነበር።

ኢትዮጵያም -በአብዮትና ፀረ-አብዮት ግብግብ ትናወጥ ነበር።የሶማሊያ ጦርም ገሚስ ኢትዮጵያን ለመያዝ ምሥራቅና ደቡባዊ ኢትዮጵያን ተቆጣጠረ።የአብዮቱ ትርምስ፤ የኢትዮ-ሶማሊያ ጦርነት፤ የዩናይትድ ስቴት መንግሥት ፀረ-ኢትዮጵያ አቋም መያዝ፤ ለቤገን ዕቅድና ቃላቸዉን ገቢር ለማድረግ ጥሩ አጋጣሚ ነበር።

ተዘጋ።ቤገን ግን ተስፋ አልቆረጡም።ሰዉዬዉ ተስፋ ቆርጠዉ አያዉቁም።ሊኩድ የተሰኘዉን አክራሪ የፖለቲካ ፓርቲያቸዉን ከተቃዋሚ ፓርቲ ነት ለመንግሥትነት ለማብቃት 29 አመታት ሳይታክቱ ታግለዋል።የተዘጋዉን ለመክፈትም ይሰረስሩ ገቢ።ሐላፊነቱንም ለእስራኤሉ የሥለላ ድርጅት ሞሳድ ሰጡ።1979።

በአብዛኛዉ ምዕራብ ጎንደር የሚኖሩት ቤተ-እስራኤላዉያን ሥለነሱ-ለነሱና በነሱ ሰበብ ቴል አቪቭ፤ ዋሽግተን፣ ኒዮርክና ካርቱም ላይ የሚቀለጣጠፈዉን በግልፅ የሚያዉቁበት አጋጣሚ አልነበረም።እነ ጆናታን ሼፋ ግን አላረፉም።

Menachem Begin
ምስል AP

«ሞሳድ ሱዳን ዉስጥ ማስኮብለያ ጣቢያዉን አሰራ።» አሉ ኋላ ጆናታን ለአንድ ፊልም አዘጋጅ።ሞሳድ፤ሲ አይ ኤ፤የሱዳኑ የስለላ ድርጅት SSS የቤግንን ትዕዛዝ ገቢር ለማድረግ ደፋ ቀና ሲሉ ኢትዮጵያ በሌላ ነዉጥ ተመታች።ድርቅ እና ረሐብ።በረሐቡ ላይ የሞሳድ ስዉር ሰበካና ቅስቀሳ የታከለለት ቤተ-እስራኤላዊ ወደ ሱዳን ይጎርፍ ያዘ።

«ጆናታን ደወለልኝ እና ስማ፤ ለልዩ ተልዕኮ አፈልግሐለሁ አለኝ።አሁን የምፈልግሕ እንደከዚሕ ቀደሙ ለግድያ አይደለም።በጣም ሰብአዊ ለሆነ ተልዕኮ ነዉ እያለ ቀጠለ፤ ሱዳን ዉስጥ ማስመለጪያ ጣቢያ እንድትመሠርት እፈልጋለሁ።አለኝ» አሉ ቤተ እስራኤላዉያኑን ወደ እስራኤል ለማጓዝ ሱዳን ዉስጥ የድብቅ በተዘጋጀዉ ጣቢያ አማካሪ የነበሩት ኢማኑኤል አሎን-ለአንድ ፊልም አዘጋጅ።

ቤተ-እስራኤላዉያኑ ሱዳን ለመድረስ ብዙ ሺ ኪሎ ሜትር መንግድ በእግር ጭምር መጓዝ ነበረባቸዉ።በሽፍታ ይዘረፋሉ፤ ይደበደባሉ፤ ሌሎች መንግድ ላይ ደክመዉ ይወድቃሉ።ይሞታሉም።ሱዳን ከገቡ በሕዋላም በረሐብ፤በወባና በሌሎች በሽታዎች ከአንድ ሺሕ አራት መቶ በላይ ሞተዋል።ዕቅዱም ተጣደፈ።ጉር አርየሕ የሁዳ (የይሁዳ ደቦል) የተሰኘዉ ዘመቻ ከፍፃሜዉ መጀመሪያ ደረሰ።ሥሙ ግን አሜሪካዉያን የሁዲዎች ባደረጉት ግፊት ተቀየረ-ዘመቻ ሙሴ በሚለዉ። የመጀመሪያዉ አዉሮፕላን-በድብቅ ከተዘጋጀለት የሱዳን አዉሮፕላን ማረፊያ 200 መቶ ቤተ እስራኤላዉያንን አሳፍሮ ወደ ብራስልስ-ቤልጅግ በረረ ከዚያ ወደ እስራኤል።ሕዳር 21 1984።ሁለተኛዉ ቀጠለ።ሰወስተኛዉ አሰለሰ።

ዘመቻዉ ጥር 5 1985 እስከተቋረጠበት ጊዜ ድረስ በተቋጠረዉ አንድ ወር ተኩል ጊዜ ዉስጥ በተደረጉ 30 በረራዎች-ስምንት ሺሕ ያሕል ቤተ-እስራኤሎች እስራኤል ገብተዋል።ከዚያ በሕዋልም በዘመቻ ሰለሞንና በሌላ መንግድም በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ ቤተ-እስራኤላዉያን ከሚመኙት ምድር ደርሰዋል።ነጋሽ መሐመድ ነኝ ቸር ያሰማን።

ነጋሽ መሐመድ

ተክሌ የኋላ