1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያውያን የውይይት እና የትብብር መድረክ

ማክሰኞ፣ ኅዳር 25 2011

ስብስቡ ያካተታቸው አባላት አደረጃጀትም ሆነ ተግባር ቢለያይም የጋራ ችግር በአንድ ላይ አሰባስቧቸው በጋራ መንቀሳቀስ መጀመራቸውን አቶ አፈወርቅ ያስረዳሉ። ከመድረኩ መሥራቾች ውስጥ ከ20 በላይ የሚሆኑ የፖለቲካ ድርጅቶች እና  የሲቪክ ማህበራት መሪዎች ይገኙበታል።

https://p.dw.com/p/39Spo
Äthiopien Dialog und Kooperation Forum Deutschland
ምስል Afework Teferra

በጀርመን የኢትዮጵያውያን የውይይት እና የትብብር መድረክ

በውጭ ያሉ ኢትዮጵያውያን በየሚኖሩበት አገር ከተማም ሆነ አካባቢ ለተለያዩ ዓላማዎች በተመሰረቱ ማህበራት እና ድርጅቶች  ተሰባስበው ይንቀሳቀሳሉ። በጀርመንም በኢትዮጵያውያን የተመሠረቱ ልዩ ልዩ ማህበራት እና ድርጅቶች ይገኛሉ። ከመካከላቸው ዛሬ በአውሮጳ እና ጀርመን ዝግጅታችን የምናስተዋውቃችሁ «በጀርመን የኢትዮጵያውያን የውይይት እና የትብብር መድረክ« አንዱ ነው። የኢትዮጵያውያን የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች የሲቪክ ማህበራት የቤተ እምነቶች እና የግለሰቦች ስብስብ ፣ብለው በአጭሩ ይገልጹታል መሪዎቹ፤ ከተመሰረተ 5 ዓመታት ያስቆጠረውን በጀርመን የኢትዮጵያውያን የውይይት እና የትብብር መድረክ። ማህበራዊ እና ፖለቲካዊ ሥራዎች ለመሥራት የተቋቋመው የዚህ መድረክ ሰብሳቢ አቶ አፈወርቅ ተፈራ እንደሚሉት በመድረኩ የተሰባሰቡት በጋራ በሚያስተሳስሩዋቸው ጉዳዮች ላይ አብረው የመሥራት ፍላጎት ያላቸው ድርጅቶች እና ግለሰቦች ናቸው። በጋራ እንዲሰሩ ካደረጓቸው ምክንያቶች መካከልም ባለፉት ጊዜያት በኢትዮጵያ ይፈጸሙ የነበሩ የመብት ጥሰቶች እና የህግ የበላይነት አለመከበር ይጠቀሳሉ። ስብስቡ ያካተታቸው አባላት አደረጃጀትም ሆነ ተግባር ቢለያይም ይህ የጋራ ችግር በአንድ ላይ አሰባስቧቸው በጋራ መንቀሳቀስ መጀመራቸውን አቶ አፈወርቅ ያስረዳሉ።ለመድረኩ ለአባልነት የተቀመጡ መስፈርቶችም አሉ።  ከመድረኩ መሥራቾች ውስጥ ከ20 በላይ የሚሆኑ የፖለቲካ ድርጅቶች እና  የሲቪክ ማህበራት መሪዎች ይገኙበታል። ከተለያዩ የጀርመን ከተሞች የተሰባሰቡ የቤተ እምነት ተጠሪዎች እና ገልለተኛ አቋም ያላቸውን ግለሰቦችን ጨምሮ በአጠቃላይ ቁጥራቸው ከ30 በላይ የሚሆኑ ተወካዮች አንድ ዓመት ከወሰደ ንግግር በኋላ ነበር መድረኩን ለመመሥረት የበቁት።ያኔ ሃላፊነቱን ወስዶ ምስረታውን ሲያስተባብር የነበረው «በራይንማይን የኢትዮጵያውያን ኮሚኒቲ በፍራንክፈርት ማህበር ነበር። የመድረኩ አባል የሆነው የዚህ ማህበር ሊቀመንበር አቶ በጋሻው ጉርሙ መድረኩ እንዲመሰረት መነሻ የነበሩትን ሃሳቦች ያስታውሳሉ ። አቶ በጋሻው እንዳስረዱት የፖለቲካ ትግሉ የፈጠረው ውጥረት፣ ሊመሰረት የታሰበው መድረክ የመሳካት አለመሳካቱ ጥርጣሬ እና ተስፋ የመቁረጥ ስሜት እንዲሁም ማህበሩ የሚያተኩርበት ኢትዮጵያዊነት ላይ ገደብ መደረግ አለመድረጉ የማህበሩን ምስረታ የፈተኑ ዋና ዋና ጉዳዮች ነበሩ። የመድረኩ መመስረት በመዳከም ላይ የነበሩ እርሳቸው የሚመሩትን «በራይንማይን የኢትዮጵያውያን ኮሚኒቲ በፍራንክፈርት »የመሳሰሉ ማህበራት እንዲጠናከሩ ረድቷል እንደ አቶ በጋሻው ። መድረኩ መመሥረቱ መረጃዎችን የመለዋወጥ እድል ፈጥሮ በተናጠል ይካሄዱ የነበሩ እንቅስቃሴዎች ወደ አንድ እንዲመጡም አድርጓል። በነዚህ የጋራ እንቅስቃሴዎቻቸውም ውጤት ተገኝቷል ይላሉ አቶ በጋሻው።
ካለፉት 7 ወራት አንስቶ በኢትዮጵያ የሚካሄደው ለውጥ ፣ የተሰባሰቡበትን መድረክ ዓላማ እውን እያደረገ በመሆኑ በሚገኙበት በጀርመን ለለውጡ እና ለዋነኛዎቹ ተዋናዮች ድጋፋቸውን በተለያዩ መንገድ እየሰጡ መሆናቸውን ይናገራሉ። ከ7 ወራት በፊት ይካሄዱ የነበሩ የተቃውሞ ሰልፎች አሁን በድጋፍ ሰልፎች ተቀይረዋል። ከዚሁ ጎን ለጎንም ለወገን ችግር ለመድረስ ፣ እንደ ከዚህ ቀደሙ ኢትዮጵያዊው የአቅሙን እንዲረዳ በማስተባበርም እርዳታዎችን የማሰባሰብ ሥራዎችን ያካሂዳሉ አቶ አፈወርቅ ገልጸዋል። በጀርመን የኢትዮጵያውያን የውይይት እና የትብብር መድረክ በኢትዮጵያ የለውጥ እንቅስቃሴ ከተጀመረ በኋላ ለበለጠ ሥራ የሚያነሳሱ ሁኔታዎች ተፈጥረዋል የሚል እምነት አለው። ይህን ተስፋ ሰጭ አጋጣሚ በመጠቀምም የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት እንቅስቃሴዎቹን ለማጠናከር ማቀዱን የመድረኩ ሰብሳቢ አቶ አፈወርቅ ተፈራ እና የመድረኩ መሥራች እና አባል አቶ በጋሻው ጉርሙ ተናግረዋል።  ምንም እንኳን መድረኩ ሲታገልለት የነበረ ለውጥ በኢትዮጵያ እየተካሄደ ቢሆንም በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች በሚከሰቱ ግጭቶች የሚደርሱ ጥፋቶችን በመቃወም ድምጹን ማሰማቱም አልቀረም።

Äthiopien Dialog und Kooperation Forum Deutschland
ምስል Afework Teferra
Äthiopien Dialog und Kooperation Forum Deutschland
ምስል Afework Teferra
Äthiopien Dialog und Kooperation Forum Deutschland
ምስል Afework Teferra

ኂሩት መለሰ

ሸዋዬ ለገሠ