1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኔታንያሁ የኬንያ ጉብኝት

ማክሰኞ፣ ሰኔ 28 2008

አፍሪቃ አሸባሪነትን ለመዋጋት በምታደርገዉ ትግል እስራኤል ርዳታዋን እንደምትለግስ ተገለፀ። ትናንት በዩጋንዳ ጉብኝት የጀመሩት የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቢኒያሚን ኔታንያሁ ዛሬ በመቀጠል ኬንያ ገብተዋል።

https://p.dw.com/p/1JIwR
Kenia, Benjamin Netanjahu und Uhuru Kenyatta
የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቢኒያሚን ኔታንያሁና ከፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ፤ ናይሮቢ ንያ ላይምስል Reuters

[No title]

ኔታንያሁ ዛሬ ናይሮቢ ኬንያ ላይ ከፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ጋር በሰጡት የሁለትዮች ጋዜጣዊ መግለጫ « ከአሸባሪዎች ጋር ድንገተኛ ጦርነት አለ » የሠዎችን ሕይወት ለመታደግ ቀድመን ርምጃ እንወስዳለን ሲሉ ኧሸባብ፤ ቦኮሃራም፤ እንዲሁም ራሱን «እስላማዊ መንግስት» ሲል የሚጠራዉ አሸባሪ ቡድን ሁሉ አፍሪቃ ዉስጥ እንዳለ ተናግረዋል። ጥቃትን ለመከላከል የደሕንነት መረጃዎችን ከኬንያዉያን ጓደኞቻችንና ከሌሎች አፍሪቃዉያን ጋር እንለዋወጣለን ሲሉም ተናግረዋል። አገራቸዉ ከእስራኤል ጋር የደሕንነት መረጃን በመለዋወጥ የረጅም ጊዜ ታሪክ እንዳላት የገለፁት የኬንያዉ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ በበኩላቸዉ በጎርጎረሳዊዉ 1976 ዓ,ም የጀርመንና የፍልስጤም አሸባሪዎች የያዝዋቸዉን ከ 100 በላይ ታጋቾች ለማስለቀ በተደረገዉ ጥረት ኬንያ ለእስራኤል ርዳታ መስጠትዋን አስታዉሰዋል።

የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ የአራት ቀን አፍሪቃ ጉብኝታቸዉን በዚህ ሳምንት ሰኞ በዩጋንዳ መጀመራቸዉ ይታወቃe። ከሠላሳ ዓመት ወዲህ አንድ የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር አፍሪቃን ሲጎበኝ ኔታንያሁ የመጀመሪያዉ ናቸዉ። ኔታንያሁ ከዩጋንዳና ከኬንያ ሌላ፤ ርዋንዳን እና ኢትዮጵያንም ይጎበኛሉ ።

Afrikanische Flüchtlinge demonstrieren in Israel
የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቢኒያሚን ኔታንያሁ ከዩጋንዳዉ ፕሬዚዳንት ዩዌሪ ሙሴቪ ጋር በዩጋንዳ አዉሮፕላን ማረፍያምስል Reuters/Presidential Press Unit

የኔታንያሁ የአፍሪቃ ጉብኝት ዋነኛ ዓላማ አዳዲስ የንግድ አጋሮች ፍለጋ መሆኑ ተዘግቧል ። ጉብኝታቸው እሥራኤል ፣የሰኞ 40 ዓመት በፍልስጤማውያን እና ጀርመናውያን አሸባሪዎች ተጠልፎ ኤንቴቤ ዩጋንዳ ያረፈዉ አዉሮፕላን ዉስጥ የነበሩትን ዜጎችዋን ካስለቀቀችበት ዘመቻ መታሰብያ ቀን ጋር ተገጣጥሟል ።በዚህ ተልዕኮ ኔታንያሁ ወንድማቸዉን አጥተዋል።
በዛሬ አርባ ዓመቱ የእስራኤል ኤንቴቤ ዩጋንዳ ተልዕኮ ከ30 በላይ ሰዎች ሞተዋል፤ 77 እስራኤላዉያንን ማስለቀቅ ተችሏል። እንድያም ሆኖ የአሁኑ የጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ የአፍሪቃ ጉብኝት ግልፅ ፖለቲካዊና ኤኮኖሚያዊ አጀንዳን የያዘ ነዉ። ኔታንያሁ በቅርቡ ለእስራኤል ምክር ቤት አባላትና በእስራኤል ለአፍሪቃ ሃገራት አምባሳደሮች «እስራኤል ወደ አፍሪቃ ትመጣለች፤ አፍሪቃም ወደ እስራኤል ትሄዳለች» ብለው ነበር።

የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር በአሁኑንጉብኝታቸው ሃገራቸዉ በ1960 ዎቹ ከአፍሪቃ ጋር ከነበራት ግንኙነት ጋር ማስተሳሰር ይፈልጋሉ። የ 1960ዎቹ የእስራኤል አፍሪቃ መልካም ግንኙነት ከጎርጎረሳዉያኑ 1973 ዓ,ም በኋላ ግብፅ በተለያዩ አፍሪቃ ሃገሮች ላይ ተፅእኖ በማድረጓ ቁርኝቱ ማብቃቱ የሚታወቅ ነዉ ። በ 1973 ዓም ግብፅና ሶርያ እስራኤልን በመቃወም ዮም ኩፑር በመባል የሚታወቀዉን ጦርነት ማካሄዳቸዉ ይታወቃል። እንድያም ሆኖ በእስራኤልና በአፍሪቃ መካከል የነበረዉ የቀዘቀዘ ግንኙነት በ1980ዎቹ ዳግም ያንሰራራ ቢመስልም፤ አንድ የእስራኤል መሪ በክፍለ ዓለሙ ጉብኝት ካደረገ ወደ 30 ዓመት ይጠጋል ።እስራኤል ከአፍሪቃ ጋር ግንኙነት መሻትዋ ግልፅ የሆነ መሠረታዊ ጥያቄ እንዳለዉ ይታይበታል። ሃገሪቱ አዲስ የወዳጅነት ግንኙነትን እየፈለገች ነዉ። ለምሳሌ እንደ ፈረንሳይ የመሳሰሉት ተፅእኖ ፈጣሪ የአዉሮጳ ሃገራት በጋዛ ሰርጥ የእስራኤልን ከበባና የምዕራብ ዩርዳኖስ የጀመረችዉን የሰፈራ መረሃ-ግብር ይቃወማሉ። በኬንያና ዩጋንዳ የቀድሞ የእስራኤል አምባሳደር አርዬ ኦዴድ እንደሚሉት በዚህም ምክንያት ሃገራቸው ከአፍሪቃ ሃገራት ርዳታን ትሻለች።


«እኛ እናንተን ልንረዳ የምንፈልገዉ በሰብዓዊ ምክንያቶች ብቻ ሳይሆን በፖለቲካ ጉዳዮች ጭምርም ነዉ። ከአዉሮጳ ኅብረት ጋር ያለን ግንኙነት ውጥረት የሰፈነበት በመሆኑ፤ ከአፍሪቃ ሃገራት የበለጠ ድጋፍ ለማግኘት እንመኛለን። በአሁኑ ወቅት ከሰሃራ በታች ካሉ 45 የአፍሪቃ ሃገራት ውስጥ ከ40ው ጋር እስራኤል ዲፕሎማስያዊ ግንኙነት አላት። እነዚህ ሃገራት እንዲረዱንና በንቃት እንዲንቀሳቀሱ እንፈልጋለን።»
ኦዴድ፤ በአዉሮጳ ኅብረትና በአፍሪቃ ኅብረት እስራኤልን በመቃወም በርካታ ዉሳኔዎች በመኖራቸዉ ይህን የፖለቲካ አካሄድ በአፍሪቃ አገራት እገዛ መቀየር እንፈልጋለን ሲሉ ተናግረዋል።
ታድይ ይህን የኦዴድን ምኞት ነዉ የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ በአሁኑ የአፍሪቃ ጉብኝታቸዉ ማግኘት የሚፈልጉት። የጋናዉ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሃና ቴሃ ባለፈዉ ሚያዝያ ወር እስራኤልን ሲጎበኙ ኔታንያሁ የነገሩዋቸዉም ይህንኑ ነዉ። በዩኤስ አሜሪካ «ጀምስታዉን ፋዉንዴሽን» የአፍሪቃ ጉዳዩች ምሁር ያኮብ ዜን ከዶይቼ ቬለ ጋር ባደረጉት ቃለ-ምልልስ እንደተናገሩት ግን እስራኤል በፖለቲካ ጉዳዮች የአፍሪቃ ሃገራትን እምብዛም መርዳት አትችልም።


« እስራኤል ለአፍሪቃ ሃገራት በፖለቲካው ረገድ ብዙ ልታደርግላቸው የምትችለው ነገር የለም ። እነርሱም እንደዚሁ ። ምጣኔ ኃብትን በተመለከተ ግን እስራኤል መርዳት ትችላለች»
እስራኤል በመከላከያና በቴክኖሎጂ ረገድ ርዳታ ማድረግ ትችላለች ሲሉ ያኮብ ዜን አክለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ዛሬ በጀመሩት የአፍሪቃ ጉብኝት ሻንጣቸዉ ዉስጥ የሸከፉት ይህንኑ ነዉ። ይኸዉም በግብርና እና በጤና ረገድ የልማት ርዳታና ለሃገር ዉስጥ ደህንነት ስልጠናን ወደ 12 ሚሊዮን ዩሮ መድበዋል ። በምዕራብ አፍሪቃ ጽንፈኛዉ ቡድን ቦኮ ሃራምንና፤ በአፍሪቃዉ ቀንድ የኧሸባብ ደፈጣ ተዋጊ ቡድን ለመዉጋት እንዲሁም በሰሜናዊ ሊቢያ ሃገሪትዋ እንዳትንኮታኮት ትግል እየተካሄደበት ባለበት ባሁኑ ወቅት፤ ኬንያና ኢትዮጵያ የእስራኤልን የመከላከልና የደህንነት ጥበቃ ክህሎት የማወቅ ብሎም የስለላ መረጃዎች የመለዋወጥ ትልቅ ፍላጎት አላቸዉ።

« በርካታ የእስልምና ሃይማኖት ተከታይ ያሉባት ናይጀርያን ጨምሮ ኬንያ፤ ኢትዮጵያና ዩጋንዳ በፀረ ሽብሩ ትግል የእስራኤልን እርዳታ ጠይቀዋል። ምክንያቱም እስራኤል የዚህ ባለሞያዎች ስላሏት እና በደህንነት ቴክኖሎጂና በደህንነት መረጃዎች በኩልም ሃገራቱን ልትረዳ ስለምትችል ነው ። »
ለዚህ የእስራኤል ርዳታ የአፍሪቃ መንግስታትም እስራኤልን ለመደገፍ ተዘጋጅተዋል። እንደ ፋይናንሻል ታይምስ ዘገባ፤ በእስራኤል የሚገኙ ወደ 40 ሺህ የሚሆኑ ኤርትራዉያንና ሱዳናዉያን ስደተኞችን የአፍሪቃ ሃገራት ለመቀበል ዝግጁ ናቸዉ። እስራኤል በአፍሪቃዉያን ስደተኞች አያያዝ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ትችት ይቀርብባታል ።ለረጅም ጊዜያት በግብጽ በኩል አቋርጠዉ እስራኤል ይገቡ የነበሩ አፍሪቃዉያን ስደተኞች በአሁኑ ወቅት በአጥር ተገድበዋል።

Uganda Entebbe Israels Premierminister Netanjahu und Präsident Museveni
ምስል Reuters

እስራኤል የሚገኙ ስደተኞች በሕጋዊ መንገድ ሥራ መስራት አይችሉም። የቀድሞዉ የእስራኤል አምባሳደር አርዬ ኦዴድ እንደሚሉት ኤርትራዉያን ስደተኞችን ወደ ሃገራቸዉ እንዲመለሱ አናስገድድም፤ ለእስራኤል ግን ሌላ ችግር ሆነዋል። ምክንያቱም በሃገሪቱ 150 ሺህ ፍልስጤማዉያን በሃገሪቱ ዉስጥ በስራ ላይ ተሰማርተዉ ስለሚገኙ እስራኤል ሌላ የሠራተኛ ኃይል ባለመፈለግዋ ነዉ ሲሉ ተናግረዋል። ይህ በእስራኤል የሚታየዉ የአፍሪቃዉያን የስደተኞች ችግር ግን በአሁኑ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ የአፍሪቃ ሃገራት ጉብኝት ይነሳል ብለው አያምኑም። እንዲያም ሆኖ እንደ ሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎች ሩዋንዳና ዩጋንዳ በእስራኤል የሚገኙትን አፍሪቃዉያን ስደተኞች ለመቀበል የተዘጋጁ ሃገሮች ናቸዉ። ለእነዚህ ሃገሮች ደግሞ እስራኤል የጦር መሳርያና የመከላከያ ምሁራንን ለመስጠት ቃል ሳትገባ አልቀረችም።

ካትሪን ማታይ/አዜብ ታደሰ

ሂሩት መለሰ