1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

Merga Yonas Bula
ሐሙስ፣ መስከረም 18 2010

በአዲስ አበባ ከተማ የዉሃ አገልግሎትን ጨምሮ የመብራትና የኔትዎርክ መቆራረጥ አሁንም አነጋጋሪ እንደሆነ ይገኛል። የአዲስ አበባ የዉሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ተመን ለመጨመር ባቀደበት ወቅት ጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ጣልቃ ገብተው ተፈፃሚ እንዳይሆን ትዕዛዝ መስጠታቸዉን የአገር ዉስጥ ዘገባዎች ያመለክታሉ። 

https://p.dw.com/p/2ktNV
Stadtansicht von Addis Abeba Hauptstadt von Aethiopien
ምስል Imago/photothek

Water Supply Shortage in Addis Ababa - MP3-Stereo

ከሶስት ሚሊዮን በላይ ሕዝብ እንዳላት የሚነገርላት አዲስ አበባ በዉሃ መቆራረጥ ክፉኛ እንደሚትቸገር ይነገራል። የአዲስ አበባ ክፍለ-ከተሞችም ፈረቃ በማዉጣት የማህበረሰቡ ክፍል ዉሃ እንዲያገኙ በማድረግ ላይ እንደሆኑ ለመረዳት ተችሎዋል። ዶይቼ ቬሌ ያነጋገራቸዉ የከተማዋ ነዋሪዎች ዉሃ ማታ ላይ ብቻ እንደሚያገኙና አንዳንዴም ለአራት ቀን እንደሚጠፋ ገልጸዋል።

በየካ ክፍለ ከተማ ወረዳ 9፣10፣11 ላይ የዉሃ ሥርጭት ኃላፊ አቶ ግርማ ይስማዉ የተጠቀሱት ወረዳዎች ዳገታማ በመሆናቸውና የዉሃ ስርጭቱ አነስተኛ በመሆኑ ውኃ በፈረቃ እንደሚከፋፈል  ይናገራሉ። ያለ ፈረቃ የዉሃ ስርጭቱን በሙሉ ለወረዳዎቹ ቢለቀቅ ዉሃዉ ለሁሉም አይዳረስምም ሲሉ አቶ ግርማ ተናግረዋል።

Screenshot facebook.com/aawsags zu Trinkwasser-Rationierung in Äthiopien
ምስል facebook.com/aawsags

ይህ ባለበት ሁኔታ የአዲስ አበባ ዉሃና ፍሳሽ ባለሥልጣን ለከተማዋ ነዋሪዎች የሚቀርበዉን የዉሃ አግልግሎት ላይ ተመን ለመጨመር ጥናት እንዳደረገና ጥናቱም በባለስልጣኑ አመራር ቦርድ ተቀባይነት ማግኘቱ የአገር ዉስጥ ዘገባዎች ጠቁመዋል። በዘገባዉም እንደ ምክንያት የተጠቀሰዉ ባለስልጣኑ ለሚያከናዉናቸዉ ፕሮጀክቶች የገንዝብ እጥረት ስላለበት በዉሃ አገልግሎቱ ላይ ተመን በመጨመር ፕሮጀክቶቹን ለማንቀሳቀስ መፈለጉ ነው።

በዉሃ ላይ ተመን ይጨመራል መባሉን ሰምቻለሁ የሚሉት አቶ ግርማ ግን ተፈጻሚነቱ በዚህ  ቀን ይሆናል ተብሎ እንዳልተነገራቸው አስታውቀዋል።  አሁን ያለዉ የውሃ ተመን መጠን «የሞተ ሂሳብ» ነዉ የሚሉት አቶ ግርማ ለመስመር ጥገናና ለሌሎች ስራዎች የሚመደበው ወጭ ከፍተኛ ነዉም ብለዋል።

በአዲስ አበባ ከተማ የዉሃ ፍላጎትና አቅርቦት አለመመጣጠኑ አቶ ግርማን ጨምሮ ሌሎች የከተማዋ ነዋሪዎችን እያሳሰበ ይገኛል። ኮሬንቲ ለአንድ ሰዓት እንኳን ከተቋረጠ ውሃም ለግማሽ ቀን ያህል ስለሚቋረጥ ችግሩ ከፍተኛ ነው ይላሉ አቶ ግርማ።

ይህን በዉሃ እጥረት ሰበብ ህብረተሰቡ የሚያሰማውን ብሶት በትዊተር ገጹ ላይ የሚያሰፈረዉ ጦማሪ አጥናፍ ብራሃኔ የኮሬንቲ፣ የኔትዎርክ እንዲሁም ሌሎች አገልግሎቶች መቆራረጥ «በጣም እየተለመደ መጥቷል» ይላል። አጥናፍ የዉሃ እጥረት ወደ ሌሎች ተያያዥ ችግሮችን እንድያመራ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል።

የባለስልጣኑን በዉሃ ላይ ተመን የመጨመር እቅድ ተፈጻሚ እንዳይሆን ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይሌማርያም ደሳለኝ ትዕዛዝ መስጠታቸዉን የአገር ዉስጥ ዘገባዉ ጠቁመዋል። በትዕዛዙም መሰረት የተመን ጭማሪዉ ተፈጻሚ ከመሆኑ በፊት የዉሃ አገልግሉት አሰጣጡን ማሻሻል አስፈላጊ መሆን እንዳለበት ጠቅላይ ሚንስትrru ማሳሰባቸውን ዘገባዉ ጠቅሶዋል።

ይህ የጠቅላይ ሚንስትሩ ትዕዛዝ ጊዚያዊ ቢሆንም አቶ ግርማ እና አጥናፍ በበጎ መልኩ አይተውታል።

ከባለስልጣኑ በኩል የበለጠ መረጃ ለማግኘት ያደርግነዉ ሙከራ አልተሳካም።  

መርጋ ዮናስ

አርያም ተክሌ