1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ጀርመን፤ የሳይበር ዘረፋ ወንጀለኛዉ ታወቀ

ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 30 2011

የጀርመን የዲጂታል ጥቃት ተከላካይ መስሪያ ቤት የመራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክልን ጨምሮ በመቶዎች በሚቆጠሩ ፖለቲከኞች እና ታዋቂ ሰዎች ላይ የመረጃ ዘረፋ መፈፀሙን ይፋ ካደረገ ከጥቂት ቀናት በኋላ አንድ የ 20 ዓመት ወጣት ተጠርጣሪ በቁጥጥር ስር እንዳዋለ አመለከተ። ወንጀለኛዉ ይህን ያደረገዉ በብስጭት ነዉ ብሎአል።

https://p.dw.com/p/3BCof
Symbolbild Cyberkriminalität
ምስል picture-alliance/dpa/H. Fohringer

«የሳይበር ጥቃቱን የፈፀመዉ የአንዳንድ ሰዎች ይፋዊ አቋም ተበሳጭቶ ነዉ»

የጀርመን የዲጂታል ጥቃት ተከላካይ መስሪያ ቤት የመራሒተ መንግሥት አንጌላ ሜርክልን ጨምሮ በመቶዎች በሚቆጠሩ ፖለቲከኞች እና ታዋቂ ሰዎች ላይ የመረጃ ዘረፋ መፈፀሙን ይፋ ካደረገ ከጥቂት ቀናት በኋላ አንድ የ 20 ዓመት ወጣት ተጠርጣሪ በቁጥጥር ስር እንዳዋለ አመለከተ።  ተጠርጣሪዉ ወጣት ወንጀሉን መፈፀሙን ከትናንት በስትያ እሁድ  ማመኑን የጀርመን ወንጀል ምርመራ ቢሮ ዛሬ አስታዉቋል። የምርመራው ቢሮ ሰራተኞች ተጠርጣሪውን ከማሰራቸው በፊት መኖሪያ ቤት መፈተሻቸውን ገልጸዋል። ዛሬ ፍራንክፈርት ላይ የከፍተኛዉ አቃቤ ሕግ ጊዮርግ ኡንገፉክ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ግለሰቡ ይህን ድርጊት የፈፀመዉ በግለሰቦቹ አቋም ስለተበሳጨ ነዉ።   
«የፍራንክፉርት አም ማይን  አቃቤ ሕግ እና የጀርመን የወንጀል ምርመራ ቢሮ ባለፈዉ እሁድ ምሽት በማዕከላዊ ሄሰ ግዛት የሚገኘዉን የወንጀለኛዉን መኖርያ ቤት ፈትሸዉ፤ ወንጀለኛዉን ለተወሰኑ ጊዜያት በቁጥጥር ስር አዉለዋል። ግለሰቡ የቀረበበትን ክስ ሙሉ በሙሉ አምኖአል።  ወንጀለኛዉ የመረጃ ዘረፋ ድርጊት የፈጸመ በትን እና መረጃዎቹን ይፋ ያደረበት ምክንያትን ሙሉ በሙሉ መግለፅ ባንችልም ግለሰቡ እንደተናገረዉ ፤ የግለሰቦቹን መረጃ በሳይበር ይፋ የለቀቀዉ የአንዳንድ ሰዎች ይፋዊ አቋም አገላለፅ ስላበሳጨዉ ነዉ።» 
እስካሁን በተካሄደዉ ምርመራ ከ20 ዓመቱ ወጣት ጋር አብሮ ወንጀሉን የፈፀመ የለምም ተብሎአል። ተፈፀመ በተባለዉ የመረጃ ዘረፋ ወደ 1000 የሚሆኑ ፖለቲከኞች እና ታዋቂ ሰዎች መረጃ ተሰርቀዋል። ከነዚህ መካከል ወደ 50 የሚሆኑት ይፋ መደረጋቸው ተነግሯል። አሁን በመሀሉ ወጣቱን ተጠርጣሪ በእስር ማቆየት የሚያስችል ሕጋዊ ድጋፍ ባለመኖሩ ተጠርጣሪው መለቀቁ ነዉ የተነገረዉ።

አዜብ ታደሰ 

አርያም ተክሌ