1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሀገር አቀፉ የክትባት ዘመቻ በሶማሌ ክልል ሺንሌ ከተማ ተጀምሯል

ሐሙስ፣ መስከረም 28 2013

ዶ/ር ደረጀ ዱጉማ እንደተናገሩት በሀገሪቱ የህፃናትን ጤና በመጠበቅ ረገድ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አለው ያሉትን ክትባት ተደራሽነት እና ጥራት በማረጋገጥ በኩል ችግሮች አሉ ብለዋል። በዚህ ምክንያት ባህሪውን የቀየረ የፖሊዮ ቫይረስ በሀገሪቱ መታየቱን ጠቁመው ችግሩ በግዜ መፍትሄ ካልተበጀለት ጎጂ በመሆኑ ዘመቻው መዘጋጀቱን አስረድተዋል፡፡

https://p.dw.com/p/3je5M
Polio-Impfung in Äthiopien
ምስል Mesay Teklu/DW

ሀገር አቀፉ የክትባት ዘመቻ በሶማሌ ክልል ሺንሌ ከተማ ተጀምሯል

የፖሊዮ ቫይረስ  ስጋት በሆነባቸው የሀገሪቱ አካባቢዎች ተግባራዊ የሚሆን ሀገር አቀፍ የፖሊዮ ክትባት ዘመቻ ትናንት በሶማሌ ክልል ሺኒሌ ዞን ሺንሌ ከተማ ተጀምሯል፡፡ አራት ክልሎችን እና ሁለት የከተማ መስተዳድሮችን ሽፋን በሚሰጠው በዚህ የክትባት ዘመቻ እድሜያቸው ከአምስት አመት በታች የሆኑ ሰባት ሚሊየን ህፃናት እንደሚከተቡ የጤና ሚንስቴር አስታውቋል። 

የጤና ሚንስቴር ሚንስትር ዲኤታ ዶ/ር ደረጀ ዱጉማ የክትባት ዘመቻውን በሶማሌ ክልል ሺኒሌ ዞን ሺንሌ ከተማ ተገኝተው ሲያስጀምሩ እንደተናገሩት በሀገሪቱ የህፃናትን ጤና በመጠበቅ ረገድ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አለው ያሉትን ክትባት ተደራሽነት እና ጥራት በማረጋገጥ በኩል ችግሮች አሉ ብለዋል ፡፡ሚንስትር ዲኤታው በዚህ ምክንያት ባህሪውን የቀየረ የፖሊዮ ቫይረስ በሀገሪቱ መታየቱን ጠቁመው ችግሩ በጊዜ መፍትሄ ካልተበጀለት ጎጂ በመሆኑ ዘመቻው መዘጋጀቱን አስረድተዋል፡፡
በኦሮሚያ ፣ በደቡብ ብሄሮች ብሄረሰቦች እና ህዝቦች ክልል ፣ በሀረሪ እና ሶማሌ ክልሎች እንዲሁም በአዲስ አበባ እና ድሬደዋ አስተዳደር ለአራት ቀናት በሚካሄደው የክትባት ዘመቻ እድሜያቸው ከአምስት አመት በታች የሆኑ ሰባት ሚሊየን ህፃናት እንደሚከተቡ ዶ/ር ደረጀ አስታውቀዋል፡፡ዘመቻው የተጀመረበት የሶማሌ ክልል ጤና ቢሮ ሃላፊ ዶ/ር ዩሱፍ መሀመድ በአንድ ዞን እና ዘጠኝ ወረዳዎች ለሚካሄደው የፖሊዮ የክትባት ዘመቻ አስፈላጊውን ዝግጅት ማድረጋቸውን ለDW ተናግረዋል፡፡የድሬደዋ አስተዳደር ጤና ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ለምለም በዛብህ በበኩላቸው በዘመቻው ሰባ አራት ሺህ የሚሆኑ ህፃናትን ለመከተብ ኮሮና ወረርሽኝ መከላከልን ማዕከል አድርጎ በሚሰራው ስራ አንድም ህፃን ሳይከተብ እንዳይቀር ጥንቃቄ የተሞላበት ዘመቻ እንሰራለን ብለዋል።
ቤተሰብ ልጆቹን በማስከተብ እና በየደረጃው የሚገኙ አካላትም ዘመቻውን የተሳካ ለማድረግ የበኩላቸውን እንዲወጡ ጥሪ ቀርቧል ፡፡ ዛሬ ሁለተኛ ቀኑን ባስቆጠረው የክትባት ዘመቻ የተካተቱት አካባቢዎች የበሽታው አምጪ ቫይረስ ምልክት የታየባቸው መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡

Polio-Impfung in Äthiopien
ምስል Mesay Teklu/DW

መሳይ ተክሉ

ኂሩት መለሰ

ነጋሽ መሐመድ