ለብሔራዊ ውይይት የኦፌኮ ቅድመ-ኹኔታ
ረቡዕ፣ ጥቅምት 17 2014የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግሬስ (ኦፌኮ) ከቀናት በፊት ባወጣው መግለጫው ያስቀመጣቸው አራት ቅድመ ሁኔታዎች የማይሟሉ ከሆነ በብሔራዊ መግባባት መድረክ እንደማይሳተፍ ለዶይቼ ቬለ ገልጧል። የኦፌኮ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ጥሩነህ ገምታ እንደሚሉት፦ በውይይቱ መሳተፍ ያለባቸው በግጭት እና በተቃርኖ ውስጥ ያሉ የአገሪቱ ጉዳይ ይመለከተኛል ያሉ ሁሉም አካላት ናቸው። በመንግሥት በኩል ግን ስለ ብሔራዊ መግባባት ዝርዝር ጉዳዮች ላይ የሚደረገው ውይይት እና ቅድመ ዝግጅት ገና ያልተጠናቀቀ ነው ተብሏል።
የኦሮሞ ፌዴራላዊ ኮንግሬስ (ኦፌኮ)መንግስት በቀጣይ ሊያዘጋጅ ስላሰበው የብሔራዊ መግባባት መድረክ አስመልክቶ ሰኞ ባወጣው የአቋም መግለጫው የተለያዩ ቅድመ ሁኔታዎችን አኑሯል። በመግለጫውም የሀገሪቱን ወቅታዊ የፖለቲካ ቀውስ ሊፈታ የሚችለው ሐቀኛ እና ሁሉን አቀፍ ውይይት ነው ብሏል ፓርቲው። የኦፌኮ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ጥሩነህ ገምታ መግለጫውን በዚህ ወቅት ማውጣት ያስፈለገበትን ምክንያት ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል።
ኦፌኮ ስላስቀመጣቸው አራት ቅድሜ ሁኔታዎችም ከኃላፊው ማብራሪያ ጠይቀናል። አቶ ጥሩነህ አክለው እንዳሉት ፓርቲያቸው ያስቀመጠው አራት ቅድመ ሁኔታዎች በውይይት መድረኩ አስቀድመው ካልተሟሉ በታቀደው መድረክ መሳተፍ ዋጋ የማይኖረው ስለሆነ አንሳተፍም ብለዋል። በመንግስት በኩል በተለያዩ መድረኮች እንደሚሰማው በወንጀል ተጠጥረው እንጂ በዚህን ወቅት በፖለቲካ አመለካከት ልዩነት የታሰረ የለም። አቶ ጥሩነህ ግን በቀጣይ ስለታቀደው ውይይት አስቀድመው የተለየ ውሳኔን እንጠብቃለን ባይ ናቸው። መንግስት በቀጣይ አዘጋጃለሁ ስላለሁ ሁሉን አቀፍ የብሔራዊ መግባባት መድረክ እና የትኩረት ነጥቦቹ እንዲሁም ኦፌኮ ስላነሳቸው ጉዳዮች የመንግስት ኮሚዩኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዶ/ር ለገሰ ቱሉን ጠይቀናቸው በመድረኩ ዝርዝር ሁኔታዎች ላይ ገና ውይይት እየተደረገ መሆኑን ነግረውናል።
ሥዩም ጌቱ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
እሸቴ በቀለ