1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ላይቤሪያ እንደገና ኤቦላ

ሐሙስ፣ ሰኔ 25 2007

ላይቤሪያ ከገዳዩ ተሕዋሲ ሥርጭት ነፃ መሆንዋን ባለፈዉ ግንቦት መጀመሪያ ሲያዉጅ ለምዕራብ አፊራቂዊቱ ሐገር መንግሥት ድል፤ ለጤና እን ለፀረ ኤቦላ ተፋላሚዎች ታላቅ ደስታ፤ ለሕዝቧ ከጭንቅ የመገላገል እፎይታ ነበር።በአርባ-ሁለተኛዉ ቀን ሌላ ዜጋዋ በዚያዉ ተሕዋሲ መሞቱ፤ ሌሎች መለከፋቸዉ ድል፤ ደስታ፤ እፎይታዉን ባጭር እንዳይቀጨዉ ነዉ ሥጋቱ

https://p.dw.com/p/1Frsl
ምስል J. Moore/Getty Images

[No title]

ላይቤሪያ ዉስጥ በገዳዩ የኤቦላ ተሕዋሲ የተለከፉ ተጨማሪ ሁለት ወጣቶች መገኘታቸዉን የሐገሪቱ የጤና ባለሥልጣናት አስታወቁ።ባለፈዉ ዕሁድ ከርዕሠ-ከተማ ሞንሮቪያ ወጣ ብሎ በሚገኝ ገጠራማ አካባቢ አንድ የአስራ-ሰባት ዓመት ወጣት በተሕዋሱ ተለክፎ መሞቱ ተረጋግጦ ነበር።የላይቢሪያ የጤና ባለሥልጣናት ዛሬ እንዳስታዉቁት ሁለቱ ወጣቶችም የሚኖሩት ሟቹ በሚኖርበት አካባቢ ነዉ።ላይቤሪያ ከኤቦላ ተሕዋሲ ሥርጭት ነፃ መሆንዋ በታወጀ በስድስተኛዉ ሳምንት ሰወስት ዜጎቿ በገዳዩ ተሕዋሲ መለከፋቸዉ ታላቁን ደስታ በሐዘን እንዳይለዉጠዉ አስግቷል።ዛራ ሽቴፋን የዘገበችዉን ነጋሽ መሐመድ እንደሚከተለዉ አጠናቅሮቶታል።

የተባበሩት መንግሥታት የጤና ድርጅት (WHO)፤ ላይቤሪያ ከገዳዩ ተሕዋሲ ሥርጭት ነፃ መሆንዋን ባለፈዉ ግንቦት መጀመሪያ ሲያዉጅ ለምዕራብ አፊራቂዊቱ ሐገር መንግሥት ድል፤ ለጤና እን ለፀረ ኤቦላ ተፋላሚዎች ታላቅ ደስታ፤ ለሕዝቧ ከጭንቅ የመገላገል እፎይታ ነበር።

ገዳዩ ተሕዋሲ ባለፈዉ አንድ ዓመት ባንዲት ላይቤሪያ ብቻ ከአስራ-አንድ ሺሕ በላይ ሕዝብ ለክፏል። አራት ሺሕ ሰምንት መቶ ገድሏል።ዕሁድ አንድ ተደገመ።ከገዳዩ ተሕዋሲ ነፃ መሆንዋ በታወጀ በአርባ-ሁለተኛዉ ቀን ሌላ ዜጋዋ በዚያዉ ተሕዋሲ መሞቱ፤ ሌሎች መለከፋቸዉ ድል፤ ደስታ፤ እፎይታዉን ባጭር እንዳይቀጨዉ ነዉ ሥጋቱ።የሥጋቱ-ሥጋት በእርግጥ አደገኛዉ መቅሰፍት ዳግም እንዳያንሰራራ ነዉ።

Liberia Ebola
ምስል picture-alliance/dpa/J. Moore

የዓለም ጤና ድርጅት ቃል አቀባይ ማርጋሬት ሐሪስ ተስፋ ሰጪ መልስ አላቸዉ።

«ሥርጭቱ መቆሙን ነዉ የገለፅነዉ።ይሕ ማለት ምንድነዉ፤ ተሕዋሲዉ ካንዱ ወደ ሌላዉ አይተላለፍም ማለት ነዉ።ሰዎች ከእንግዲሕ በተሕዋሲዉ አይለከፉም ማለት ነዉ።ይሕ ማለት ግን ተሕዋሲዉ ሙሉ በሙሉ ጠፍቷል ወይም ዳግም አይከሰትም ማለት አይደለም።»

ቃል አቀባይዋ የኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፕብሊክና የዩጋንዳን ልምድ አብነት ይጠቅሳሉ።በተደጋጋሚ በኤቦላ በሚጠቁት በሁለቱ ሐገራት የተሕዋሲዉ ሥርጭት ቆመ ከተባለ ከወራት በሕዋላ ሌሎት ተለካፊዎች ይገኛሉ።ብዙ ጊዜ ግን እንደመጀመሪያዉ ያክል ብዙ ሳይጎዳ በጤና ባለሙያዎች ቋንቋ «በቁጥጥር ስር» ይዉላል።

ላይቤሪም-እንዳዲስ የታየዉ ተሕዋሲ ብዙ-ሳይጎዳ፤ ቶሎ ይጠፋ ይሆናል ነዉ-ተስፋዉ።የላይቤሪያ መንግሥት የወሰደዉ እርምጃም ተሕዋሲዉ ዳግም እንዳይሰራጭ የሚያደርግ፤ በቃል አቀባይ ሐሪስ አገለጥ ፈጣንና አርኪ ነዉ።

«የላይቤሪያ መንግሥት በዉነቱ በጣም ጥሩ ደረጃ ላይ ነዉ።ፈጣን አፀፋ ለመዉሰድ በቅጡ ተዘጋጅቷል።ብዙ ነገር ነዉ ያደረጉት።ብዙ ጥሩ ሰዎች አሏቸዉ።እኛም እንሱን የሚደግፉ ሰዎች አሉን።»

የሟቹም ሆነ የተለካፊዎቹ ቤተሰቦች፤ ሐኪሞችና ወዳጆች፤ በድምሩ አንድ መቶ ሰባ-አምስት ሰዎች ከሌላ ሰዉ ጋር እንዳይገናኙ ተገልለዋል (ኳራንቲን ገብተዋል)

ፈጣኑ እርምጃ ጥሩ ዉጤት የሚያመጣዉ ግን ሰወስቱ ተሕዋሲዉን ከየት አመጡት-ለሚለዉ ጥያቄ መልስ ሲገኝ ነዉ።ሰወስቱም ያንድ አካባቢ ነዋሪ በመሆናቸዉ እዚያ አካባቢ ተሕዋሲዉ አለ ወይም አንዳቸዉ ከሌላቸዉ በተለይ የኋለኞቹ ሁለቱ ወይም አንዱ ከሟቹ ተሕዋሲዉ ተላለፈባቸዉ ብሎ መገመት አልገደደም።ሟቹ ከየት አመጣዉ? ከጊኒ፤ ከሴራሊዮን----«እዚያ አልሔደም ነበር» ይላሉ ቃል አቀባይ ሐሪስ

Liberia Monrovia Ebola
ምስል picture-alliance/dpa/A. Jallanzo

«ይሕ ወጣት ካካባቢዉ አለመዉጣቱን እናዉቃለን።የጤና ጥበቃ ሚንስቴር ከWHO ባለሙያዎች ጋር ሆኖ እስካሁን ባደረግነዉ ምርመራ ከሟቹ ቤሰብ አባላት መሐልም ወደ ሁለቱ ሐገራት የተጓዘ አላገኘንም።ሌሎች ምክንያቶችን ለማወቅ ሁሉንም የቤተሰቡን አባላት፤ የሚቀርቡትንና ባካባቢዉ የነበሩትን በሙሉ እየመረመርን ነዉ።»

እንደ ላይቤሪያ ሁሉ በርካታ ዜጎቻቸዉ በኤቦላ ያለቀባቸዉ ጊኒ እና ሴራሊዮን አሁንም ከኤቦላ ተሕዋሲ ጋር እየታገሉ ነዉ።የላይቤሪያ ምክትል የጤና ሚንስትር ቶልበርት ንዬኔንስዋሕ ተሕዋሲዉ ከሁለቱ ሐገሮች ለመምጣቱ ምንም መረጃ የለም ባይ ናቸዉ።ሰወስቱ ወጣቶቾ ከሚኖሩበት አካባቢ ዉጪ ሌላ አካባቢ አልተሰራጨም ባይ ናቸዉ።ሰወስቱ ከየት ተለከፉ-ያልተመለሰ ጥያቄ።

ነጋሽ መሐመድ

ሸዋዬ ለገሠ