1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሐዋላና የGTZ አገልግሎት

ሐሙስ፣ ታኅሣሥ 8 2002

ለምሳሌ አምደ-መረቡን ከፍተዉ ኢትዮጵያ የሚለዉ ጋ ቢጫኑ፥ገንዘብ የሚያስተላልፉ ወደ ሃያ የሚሆኑ ተቋማትን ዝርዝር ያገኛሉ።መጀመሪያ ላይ Money Bookers አለ

https://p.dw.com/p/L6Tv

17 12 09

የጀርመን የቴክኒክ ተራዶኦ ማሕበረሰብ (GTZ) አዉሮጳ የሚኖሩ የሰወስተኛዉ አለም ተወላጆች ወደየ ትዉልድ ሐገራቸዉ ገንዘብ የሚያስተላልፉበት ሥልት ዘርግቷል።ድርጅቱ ፍራክ ፈርት ከሚገኝ የትምሕርት ተቋም ጋር በመተባበር በከፈተዉ ዌብ ሳይት ወይም አምደ-መረብ አማካይነት ፈጣንና ርካሽ የገንዘብ ማስተላለፊያ መንገዶችንና ገንዘብ አስተላላፊ ባንኮችን ይጠቁማል።የGTZ የሥደተኞችና የልማት ጉዳይ ሐላፊ ረጊና ባወርኦክሰ እንደሚሉት መስሪያ ቤታቸዉ አገልግሎቱን የከፈተዉ ሥደተኞች ለልማት የሚያደርጉትን አስተዋፅኦና ግልፅነትን ለማበረታት ነዉ።ነጋሽ መሐመድ ወይዘሮ ባወርኦክሰን አነጋግሮ የሚከተለዉን ዘገባ አጠናክሯል።


በበለፀጉት ሐገራት የሚኖሩ የአደጊ ሐገራት ተወላጆች በየትዉልድ ሐገራቸዉ ለሚኖሩ ወላጅ፥ ወዳጅ-ዘመዶቻቸዉ በየአመቱ በርካታ ገንዘብ ይልካሉ-ኢመደበኛና በደበኛ ተብለዉ በሚከፈሉ ሁለት መንደገዶች።በመንገደኞች፥ በአድርሱ-ስጡልኝ ቅብብሎሽ መልክ የሚላከዉ ገንዘብ የሚደርስበት ትክክለኛ ጊዜ አይታወቅም፥ የመለኪያዉ ዋጋም የተለያየ ነዉ።ከሁሉም በላይ በመንገድ አንዱ መጭላፋ ሊያስቀረዉ ይችላል።

ሥደተኛዉ በመደበኛ ባንክ ወይም ተቋማት በኩል የሚላከዉ ደግሞ-የGTZ-የስደተኝነትና የልማት ጉዳይ ሐላፊ ረጊና ባወርኦክሰ እንደሚሉት በርግጥ አይጠፋም።ግን ይዘገያል።ቢፈጥን እንኳን መላኪያዉ ዉድ ነዉ።ይሕን ደግሞ ድርጅታቸዉ በጥናት አረጋግጧል።

«አንድ ሰዉ ለምሳሌ መቶ ዩሮ መላክ ቢፈልግ፥ ለመላኪያዉ እስከ ሃያ-አራት ዩሮ ድረስ ይከፍላል።ይሕ ማለት ለተላከለት የሚደርሰዉ ገንዘብ ሥደተኛዉ መላክ ከሚፈልገዉ ያነሰ ነዉ-ማለት ነዉ።»

GTZ-የቀየሰዉ ሥልት ግን አስተማማኝ-ርካሽም አይነት ነዉ።ድርጅቱ ከፍራንክፈርቱ School of Finance and Managment ጋር በመተባበር ያዘጋጀዉን አምደ-መረብ ጀርመን የሚኖሩ WWW.Geldtransfair.de በሚለዉ አድራሻ ያገኙታል።የሚሰጠዉ መረጃ፣-እንደገና ባወርኦክሰ

«በዚሕ አምደ-መረብ ሰላሳ-ሰወስት ሐገራት ተዘርዝረዋል።አንድ ሰዉ በመደበኛ መንገድ ወደ ትዉልድ ሐገሩ ገንዘብ የሚልክባቸዉ የተለያዩ አማራጮች አሉ።»

GTZ ይሕን ሥልት የቀየሰበት-አለማ በግርድፉ ግልፅነትን፥ ልማትን ማበረታታትና ቅናሽን ማፈላለግ ተብሎ እሰወስት የሚከፈል-ግን ብዙ ነዉ።

«በመሠረቱ ሐሳቡ ግልፅነትን ለማስፋፋት አንዱ ሥልት ነዉ።በተለያዩ (ተቋማት) መካካል ፉክክርን ለመፍጠርና ልዩነቱን ለማሳየት ነዉ።ይሕን በማድረግም ዋጋዉን ዝቅ ለማድረግ ነዉ)

ቴክኒካዊ አፈፃፀሙ ግን እስካሁን ገንዘብ በማስተላለፍ ከሚታወቁ እንደ ዌስቴር ዩኒየንና መኒግራም ከተሰኙት ትላልቅ ተቋማት የተለየ ነዉ።በሁለቱ ተቋማትና በብጤዎቻቸዉ በኩል ገንዘብ ማስተላለፍ የሚፈልግ በርግጥ-ያለ ብዙ ዉጣ ዉረድ በቀላሉ መላክ ይችላል።ተቀባዩም ገንዘቡን ፈጥኖ ያገኘዋል።መላኪያዉ ግን ዉድ ነዉ።

«መጥፎ ጎኑ-እርስዎ እንዳሉት የመላኪያዉ ዋጋ መብዛቱ ነዉ።አንዳድ ሐገሮች ደግሞ በጣም ከፍተኛ ነዉ።ለምሳሌ አምደ-መረቡን ከፍተዉ ኢትዮጵያ የሚለዉ ጋ ቢጫኑ፥ገንዘብ የሚያስተላልፉ ወደ ሃያ የሚሆኑ ተቋማትን ዝርዝር ያገኛሉ።መጀመሪያ ላይ Money Bookers አለ።ይሕ ለምሳሌ-የኢንተርኔት ነዉ።በዚሕ በኩል ገንዘብ ቢልኩ ከሁለት እስከ ሰወስት ቀን ይፈጃል።ዋጋዉ ለመቶ ዩሮ 2: ከ 30 ነዉ።»

የርዳታዉን ድርጅት ወደዚሕ አገልግሎት የሳበዉ ምክንያትም-እንደ አለማዉ ሁሉ ብዙ ነዉ።ዋናዉ ግን የሥደተኞችንና አስተዋፅኦቸዉን ከልማት ጋር ማቀናጀት ነዉ።
«GTZ ከሚንስቴር መስሪያ ቤታችን ሐላፊነቱ ከተሰጠዉ ሁለት አመት ተኩል ነዉ።ሐላፊነቱ ሥደተኞችን ከልማት ተራድኦ ጋር ማቀናጀት የሚቻልበትን እና አስተዋፅኦቸዉን ከልማት ሥራ ጋር ማጣጣም ነዉ።እስከዚያ ድረስ የስደተኞች ጉዳይ በGTZ ሥራ ዉስጥ አልተካተተም ነበር።በዚሕ ሐላፊነት መሠረት ግን ሥደተኝነት ለልማት የሚኖረዉ አስተዋፅኦ እና አስተዋፅኦዉ የሚጎላበትን ሥፍራ ለመመልከት ችለናል።»

እስካሁን ድረስ አምደ መረቡ በየአመቱ ከሁለት ሺሕ-የሚበልጡ ጎብኚዎችን አስተናግዷል።ለብሪታንያ፥ ለፈረንሳይ፥ ለኔዘርላንድና ለኖርዌ ነዋሪዎች ጨምሮ በበርካታ የአዉሮጳ ሐገራት ለሚኖሩ ስደተኞችም በየቋንቋዉ ተመሰሳይ አምደ-መረብ ተዘጋጅቷል።

Ein interview mit Frau REGINA BAUEROXE-Leiterin von Migrationen und Entwicklung in der GTZ

ነጋሽ መሐመድ

ሒሩት መለስ