1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሔይቲን ለመርዳት የሚደረገዉ ጥረትና እንቅፋቱ

ዓርብ፣ ጥር 14 2002

ካለፈዉ ሮብ እስከ ዛሬ ድረስ ብቻ በሰወስት ከፍተኛ ነዉጦች ተርገፍግፋለች።በአስር የሚቆጠሩ ተጨማሪ ሰዎችን ቀብራለች።የርዳታ ሠራተኞችና ርዳታ ጠባቂ ሕዝቧ በሥጋት ጭንቀት ተራዉጠዉባታል።ርዳታዉ ግን እልተቋረጠም

https://p.dw.com/p/Ldzd
ጥፋቱምስል AP

22 01 10

ሔይቲን በመታዉ የመሬት መንቀጥቀጥ አደጋ ፍርስራሽ የተጫናቸዉን ሰዎች በሕይወት የማገኘቱ ተስፋ እየተሟጠጠ ነዉ።የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዛሬ እንዳስታወቀዉ የርዳታዉ ምዕራፍ ሕይወትን ከማዳን በሕወት የሚገኙትን ወደ መርዳቱ ተሸጋግሯል።ይሁንና የመዋቅር ችግርና በተደጋጋሚ የሚደርሰዉ የመሬት መንቀጥቀጥ የቆሰሉና የተፈናቀሉ ሰዎችን ለመርዳት የሚደረገዉን ጥረትም እያወከዉ ነዉ።የካረቢያዊቷን ሐገር ለዘላቂዉ መልሶ መገንባት ሥለሚቻልበት ሁኔታ የሚመክር አለም አቀፉ ጉባኤም ሰሞኑን ይደረጋል።ነጋሽ መሐመድ የጀርመኑን የሳይንስና የፖለቲካ ጥናት ተቋም ባልደረባ ፕሮፌሰር ጉንተር ማይሆልድን አነጋግሮ የሚከተለዉ ዘገባ አጠናቅሯል።

ሕዝብ አልቋል።በመቶ ሺሕ የሚገመት ሕዝብ።አስከሬን ማግኘት፥መለየት፥ ቀባሪ ማግኘት ብርቅ ነዉ።ሰወስት ሚሊዮን ሕዝብ አንድም ቆስሏል፥ አለያም ሐብት-ንብረቱ ወድሟል።መድሐኒት፥ እሕል-ዉሐ፥ ልብስ፥ መጠለያ አሳር ነዉ።ሔይቲ።ዛሬ አስራ-አንደኛ ቀንዋ።ቀን ታሰላለች።

አለም በርግጥ ለጥቂት ወይም ለማንም አድርጎት በማያዉቀዉ ፍጥነትና ደግነት የርዳታ እጅን ዘርግቶላታል። አደጋዉ ግን ሌላጋ እንደሚታወቀዉ ሕይወት፥አካል፥ ሕንፃ፥ ቤት፥መዋቅር ብቻ ቢያጠፋ ኖሮ እዳዉ በቀለለ ነበር።ፕሮፌሰር ጉተር ማይሆልድ እንደሚሉት አስተዳደርና የመንግሥትን መዋቅር ያልነበረ ያክል መፈረካካሱ እንጂ የጭንቁ-ጭንቅ።

«አለም አቀፉ ማሕበረሰብ ባንፃራዊነት ሲታይ ፈጥኖ ነዉ-የተንቀሳቀሰዉ።ይሁንና ርዳታዉን ለማደራጀትና ለማቀናጀት የሚያስችል የአስተዳደር ሥለሌ፥ የተቸገረዉን ሕዝብ በበቂ ፍጥነት መርዳት አልተቻለም።ይሕን ለማቃለል ነዉ-በተለይ ዩናይትድ ስቴትስ ለጊዜዉ አስራ-አንድ ሺሕ አባላት ያሉት ከፍተኛ የጦር ሐይል ያዘመተችዉ።ሠራዊቱ ርዳታዉን የማቀናጀትና ፀጥታ የማስከበሩን ምግባር እየተወጣ ነዉ።»
ከአምስት አመት በፊት ባብዛኛዉ የሕንድ ዉቅያኖስ ተዋሳኝ ሐገራትን በሱናሚ ሲመቱ አለም ለመርዳት ያሳየዉ ደግነትና ፍጥነት ብዙ አስገርሞ፥ አስመስግኖ፥ አንዳዴም ሌላ ጋና ጊዜ ለምን? አሰኝቶ-አጠያይቆም ነበር።ሔይቱን ለመርዳት ደግሞ ያኔ ስማቸዉ ብዙም ያልተጠቀሰዉ እንደ ብራዚልና ቻይናን የመሳሰሉት ሐገራት ከብዙዎች ፈጥነዉ ነዉ-የደረሱት።

Haiti Erdbeben
ርዳታዉምስል AP

ፕሮፌሰር ማይሆልድ ለሔይቲ ግን አዲስ አይደለም-ይላሉ።

«በሔይቲ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ተልዕኮ ረጅም ጊዜ አስቆጥሯል።የአስራ፥ አራት ሐገራት ሠራዊት የሚሳተፍበት ተልዕኮን የምትመራዉ ብራዚል ነበረች።ከዚሁ ጎን በተደራጀዉ የፖሊስ ሠራዊት የሕዝባዊት ቻይና ሪፐብሊክን ጨምሮ አርባ ሐገራት ተሳታፊዎች ናቸዉ።ቻይና የራስዋን ሐይል ከማስፈሯም በላይ የሔይቲን ፖሊስ እያሰለጠነችም ነዉ።»
ሰብአዊነት፥ ደግነት፥ እራስን ማሳየት፥ ጥቅም-ይሁን ሌላ አለም ግን ደሐይቱን፥በእስካሁን ታሪኳ ተፈጠሮም ፍጡሯም የጨቀነባትን ሐገር ለመርዳት እየተረባረበ ነዉ።ተፈጥሮ ግን አሁንም አልራራችላትም።የድሕረ-እንቅጥቃጤ ነዉጥ-እየጎነጣት ነዉ።

Haiti Nahrungsmittel
ችግረኛዉምስል AP

ካለፈዉ ሮብ እስከ ዛሬ ድረስ ብቻ በሰወስት ከፍተኛ ነዉጦች ተርገፍግፋለች።በአስር የሚቆጠሩ ተጨማሪ ሰዎችን ቀብራለች።የርዳታ ሠራተኞችና ርዳታ ጠባቂ ሕዝቧ በሥጋት ጭንቀት ተራዉጠዉባታል።ርዳታዉ ግን እልተቋረጠም።ለጋሹ አለም ከአስቸኳይ ርዳታዉ ጎን ዘላቂ ግንባታንም እያሰላ ነዉ። እንደገና ፕሮፌሰር ማይሆልድ።
«ሔይቲን ዳግም ለመገንባት፥ፈረንሳይ፥ የአዉሮጳ ሕብረት እና የደቡብ አሜሪካ ሐገራት በመጪዉ ሰኞ ካናዳ ዉስጥ አለም አቀፉ የለጋሽ ሐገራት ጉባኤ አዘጋጅተዋል።»

ዳግም ግንባታዉ ግን ከባድ ነዉ-ይላሉ ፕሮፌሰሩ።
«ሔይቲን መልሶ መገንባቱ ከባድና የረጅም ጊዜ ሒደት ነዉ-የሞሆን።ምክንያቱም የመሥረተ ልማቱ መዋቅር ብቻ ሳይሆን አንድ ሐገር የሚያስፈልጋት የመንግሥትና ያስተዳደር መዋቅሮችም ጠፍተዋል።የመሠረተ ልማትና የመንግሥት መዋቅሮችን ዳግም እኩል መገንባት ከባድ ነዉ።»

ካባድ ነዉ።ግን ይጀመራል።ረጂም ነዉ ግን ሰኞ አንድ ይላል።

Agenturen,Intev.mit Pro.Haihold

Negash Mohammed

Hirut Melesse