1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ማስተር ፕላንና የተማሪዎች ተቃዉሞ በኦሮሚያ ክልል

Merga Yonas Bulaረቡዕ፣ ኅዳር 22 2008

በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት የሚገኙ ከአንደኛ እስከ ዩኒቨርሲቲ ያሉ ተማሪዎች የአዲስ አበባ እና ኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላን እና የመልካም አስተዳደር ጉድለትን በመቃወም ላይ ናቸው። በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙት ተማሪዎች ተቃዉሟቸዉን ካለፉት ሁለት ሳምንት ጀምሮ እያካሄዱ መሆኑ ታዉቋል።

https://p.dw.com/p/1HG33
Karte Ethiopia und Eritrea ENG

[No title]

ከኅዳር 9 ቀን 2008 ዓ,ም ጀምሮ በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የአዲስ አበባ እና ኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጃ የጋራ ማስተር ፕላን እና የመልካም አስተዳደር ጉድለትን በመጠቆም በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች ተማሪዎች ተቃዉሞ እያደረጉ ነዉ። ሰላማዊ ሰልፍ ማድረጋቸዉ በሰላም በሚካሄድ ትግል ዉስጥ ችግርን በይፋ መግለጽ በሕገ መንግስቱ የተደነገገ መብት መሆኑን እንደሚያምኑ የሚናገሩት ተማሪዎች የተጠቀሰዉ የማስተር ፕላን ልዩ ዞኑ ዉስጥ የሚገኙ ኗሪዎችን ከመሬታቸዉ እንደሚያፈናቅል ያም አግባብ እንዳልሆነ ይናገራሉ። ከዚህም ሌላ ከአደስ አበባ ከተማ የሚወጡ ፈሳሾች ለሰዉም ሆነ ለእንስሳዎች ጠንቅ በመሆኑ መፍትሄ እንዲፈለግ ተቃዉሞ ማሰማታቸዉን ያስረዳሉ። በተጨማሪም የመልካም አስተዳደር እጥረት ያመጣዉ ነዉ ያሉት በግንጭ የሚገኘዉን የጭልሞ ጫካ ለግለሰቦች መንግስት ሸጧል በሚልም ተማሪዎቹ በኦሮሚያ ክልል የሚገኙ ተማሪዎች ተቃዉሟቸዉን አሰምተዋል።


በተቃዉሞዉ ወቅትም ቁጥራቸዉ ብዙ የሆኑት ተማሪዎች እንደታሰሩ፣ በፖሊስ ሃይልም ድብደባም የተጎዱ መኖራቸዉን ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የጠየቁ እማኝ ለዶቼ ቬለ ተናግረዋል። <<በአምቦ የመሰናዶ ትምህርት ቤት እና በድሬ እንጭኒ ተማሪዎች ለሰለማዊ ሰልፍ ወጥተዉ ነበር። እሱንም ተከትሎ የኦሮሚያ ፖሊስ ተማሪዎቹን ማሰር ጀመረ። ሕዳር 14 ዘጠኝ ተማሪዎች ታስረዋል፣ ትላንትም ብዛታቸዉን ባላዉቀዉም ወደ አምስት ተማርዎች መታሠራቸዉን ሰምቼ ነበር። በተጨማሪ እሄን እስር አምልጠዉ ወደ ፊንፊኔ የሸሹ ተማሪዎች እንዳሉ ሰምቼ ነበር።>>

ስምንት ከተሞችን ያቀፈዉ የኦሮሚያ ልዩ ዞን በዚህ የተቀናጀ የጋራ ማስተር ፕላን እንዲገባ ሲታቀድ የፌድራል መንግስትም ሆነ የኦሮሚያ ምክር ቤት ህዝብን ጠርቶ አለመወያየቱ ከዛም አልፎ ለተቃዋሚ ፓርቲዎች መድረኩን አለመፍቀዱ ችግሩ እንዲባባስ አድርጓል በሚል የሚተቹ አሉ። የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግሬስ ቃል አቀባይ የሆኑት አቶ በቀለ ናጋ ለዶቼ ቬሌ ይህን አስመልክተዉ ሲናገሩ፤ <<የመሬት ጉዳይ የመኖር ህልዉና ጉዳይ ነዉ። እናም የኦሮሞ ህዝብ እየተቸገረ ስለሆነ ይህ የመሬት ዘረፋ በአሰቸኳይ እንዲቆም እንፈልጋለን። ባለፈዉ የጨፌ ኦሮሚያ ያወጣዉ ሕግ፣ ከተሞች መቀላቀልና አንድ ማድረግ ይችላሉ የሚለዉ፣ ባህሉንና ቋንቋዉን የሚያጠፋ ሆኖ ስለታየን፣ በጽሑፍም ጠይቀናል። እናም ሰዉ በሰላማዊ መንገድ እየታገለ ስለሆነ ይህ አዋጅ መቆም አለበት እንላለን። ሁለተኛ ኦሮሞ ለልማቱ ተብሎ ከመሬቱ የሚነሳ ከሆነ ያ ልማት እሱን መጥቀም አለበት። ያም ማለት፣ መሬቱን ይዞ ካለዉ አካል ጋር እንደግለሰብ አክስዮን ኖሮት የሚቋቋመዉ ኢንዱስትሪ ዉስጥ ሚና ሊኖረዉ ይገባል ነዉ የምንለዉ። ጎረቤቶቻችንም ይህን ችግር ከእኛ ጋር እየተካፈሉ መከላከል አለባቸዉ።>>
ሌላዉ ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የፈለጉ የ89 አመት አዛዉንት በበኩላቸዉ ሱሉልታ አካባቢ ባለፈዉ ሳምንት ጀምሮ 600 ቤተሰብ ይኖርበት በነበረ ቦታ ላይ መንግስት ኢንዱትሪ ለመገንባት በመፈለጉ ካሳ ሳይሰጥ ኗሪዎቹን እንዳስነሳ ይናገራሉ። ለዚህም ወደ ኦሮሚያ ክልል መንግስት ድረስ ሄደዉ ቢጠይቁም መልስ አለማግኘታቸዉን እንደዉም እዚያ የሚገኙ የመንግስት ካቢኔዎች በእስር እንዳሰፈሯሯቸዉ ይናገራሉ። አዛዉንቱ አክለዉም፤ <<የተወለድንበትን ቦታ ትተን የት ነዉ የምንሄደዉ? ልጆች አሉን፣ እንስሶዎች አሉን፣ የት ነዉ የምንሄደዉ? አዉሬ ይበላናል፤ ማንስ ያስጠጋናል።>>

Dr. Merera Gudina Addis Abeba Äthiopien Oromo Pressekonferenz PK
ምስል DW/Y.Egziabhare

ይህን በሚመለከት ምላሽ ለማግኘት ከፌዴራልም ሆነ ከኦሮሚያ መንግስት የሚመለከታቸዉን ባለስልጣናት ለማነጋገር ያደረግነዉ ሙከራ አልተሳካም።

መርጋ ዮናስ

ሸዋዬ ለገሰ