1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ማዕከላዊ ኢጣልያን የመታው የመሬት መንቀጥቀጥ

ረቡዕ፣ ነሐሴ 18 2008

ትናንት ለሊት ማዕከላዊ ኢጣልያን በመታው ከባድ ርዕደ መሬት የሞት ሰዎች ቁጥር 73 መድረሱን መንግሥታዊ ምንጮች አስታወቁ ።ነፍስ አድን ሠራተኞች እንዳሉት በአደጋው ክፉኛ የተጎዱት አማትሪስ ፣አቹሞሊ እና ፔስካላ ዴል ትሮንቶ የተባሉት ከተሞች ናቸው ።

https://p.dw.com/p/1Jp7s
Italien Erdbeben Pescara del Tronto
ምስል Reuters/R. Casilli

በአማትሪስ ብቻ 35 ሰዎች መሞታቸው ተነግሯል ።በመቶዎች የሚቆጠሩ የቆሰሉ ሲሆን በሺህዎች የሚቆጠሩ ደግሞ ጊዜያዊ መጠለያ ያስፈልጋቸዋል ። በአስኮሊፒቼኖ ክፍለ ሃገር ደግሞ የሞቱት ቁጥር 17 መድረሱ ተነግሯል ።በሬክተር መለኪያ 6 በተመዘገበው እና ሦስት ከተሞችን ወደ ፍርስራሽነት በቀየረው በዚሁ ርዕደ መሬት በተለይ ከከተማ ወጣ ባሉ አካባቢዎች የሞቱት እና የተጎዱት ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል የዓይን ምስክሮች ተናግረዋል ። በ አማትሪስ እንዳልነበረች መሆንዋን ያሳወቁት የከተማይቱ ከንቲባ ሰርግዮ ፒሮዚ የአደጋው ሰለባዎች ቁጥር ይጨምራል የሚል እምነት እንዳላቸው ተናግረዋል ። የኢጣልያ የሲብል ጥበቃ መሥሪያ ቤት ሃላፊ ፋብሪዝዮ ኩርችዮ እንዳሉት በህይወት ያሉ ሰዎች ለማግኘት ፍለጋው ቀጥሏል ።
«በአሳሳቢ እና በአስቸኳይ ሁኔታ ላይ የሚገኙት ፣የአርኳታ አማትሪቼ እና አኩማሊ እንዲሁም ማርቼ አካባቢዎች መሆናቸውን ማረጋገጥ እንችላለን ። አሁን የምንናገረው ስለ ነፍስ አድን ዘመቻዎች ነው ።ጥሩው ዜና ከመንገዶች አብዛኛዎቹ እንደገና አገልግሎት መስጠት ጀምረዋል ። ስለዚህ እነዚህ አካባቢዎች ዘንድ የእሳት አደጋ ሠራተኞች በአሁኑ ጊዜ ሊደርሱ ይችላሉ ።በተጨማሪም ስለዚህ እዚያ የነፍስ አድን ሠራተኞች አሉን ፍለጋ የሚያካሂዱ እና ሰዎችን የሚታደጉ አነፍናፊ ውሾች አሉ ። ግልፅ ነው ሁሉም በበጎ ፈቃድ ሠራተኖች እገዛ ነው የሚካሄደው ። »
ላቲን የተባለችው ክፍለ ሃገር አስተዳደር ሃላፊ ብሩኖ ፍራታሲ እንደተናገሩት በአሁኑ ደረጃ የአደጋውን ሰለባዎች ቁጥር በትክክል ለመናገር አስቸጋሪ መሆኑን ያስረዳሉ ።
«ለጊዜው የተረጋገጠ ቁጥር የለንም ። ማረጋገጥ ያለብን የምናውቀውን ብቻ ነው ።የፈረሱ ህንፃዎች አሉ ። ስለዚህ ምናልባት በዚያ የአደጋው ሰለባዎች ሊኖሩ ይችላሉ ።ሆኖም ለአሁኑ በበርካታ ምክንያቶች የየአደጋውን ሰለባዎች ቁጥር ለማወቅ አይቻልም ።ምክንያቱም ያለው መረጃ በቂ አይደለም ።የሚገኘውም ዜና በሙሉ አልተረጋገጠም ። »
ትናንት ከለሊቱ 9 ሰዓት ከ36 ደቂቃ ላይ ማዕከላዊ ኢጣልያን የመታው ርዕደ መሬት ሮምን ነዝሯል ። የአድርያቲክ ባህር ዳርቻዎቹ የላዝዮ የኡምባርያ እና የሌማርቺ አካባቢዎች ድረስም ተሰምቷል ።

Italien Erdbeben Amatrice
ምስል Reuters/E. Grillotti

ኂሩት መለሰ

አርያም ተክሌ