1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

‎ሱርማ‬ የተፈጠረው ምንድነው?

ሐሙስ፣ መጋቢት 1 2008

ፌስቡክና ትዊተርን በመሳሰሉ ማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ሰሞኑን የሱርማ ሰዎች በጸጥታ ኃይሎች እንግልት ሲደርስባቸው የሚያሳዩ ምስሎች ተሰራጭተዋል። ምስሎቹ በበርካታ ኢትዮጵያውያን ዘንድ ቁጣ ቀስቅሷል። ይሁንና ኩነቱ የተፈጸመበት ቦታ ጊዜ እና ምክንያት አይታወቅም።

https://p.dw.com/p/1IAvd
Äthiopien Minister Getachew Reda
ምስል DW/G. Tedla

[No title]

ሰሞኑን በኢትዮጵያ የደቡብ ክልል የሱርማ ብሔረሰብ አባላት በጸጥታ ኃይሎች እጅ እና እግራቸው በገመድ ታስሮ በተሽከርካሪ ላይ ሲጫኑ የሚያሳዩ ምስሎች በማህበራዊ መገናኛ ብዙሃን ታይቷል። ግለሰቦቹ የተጫኑበት ተሽከርካሪ የደቡብ ፖሊስ ንብረት መሆኑን የሚጠቁም ሰሌዳ ያለው ሲሆን የጸጥታ ኃይሎች ግለሰቦቹን የፊጥኝ ሲያስሩ የሚያሳይ ምስልም ይገኝበታል። ከታሳሪ ግለሰቦች መካከል የአንዱ ግንባር ላይ ደም ይታያል። በርካታ የማህበራዊ ድረ-ገጽ ተጠቃሚ ኢትዮጵያውያንን ያሳዘነው እና ያስቆጣው ድርጊት መነሾ እንዲሁም ኩነቱ የተፈጸመበት ጊዜ እና ቦታ ግን በውል አይታወቅም። በዶይቼ ቬለ የፌስቡክ ማህበራዊ ድረ-ገጽ አስተያየታቸውን የሰጡ አምባቸው በየነ የተባሉ ግለሰብ «እሄን ድርጊት ምንም ሚስጥር የለዉ መሬታችን ለሱኳር ፋብሪካ ልትጠቀሙበት አሳልፈን አንሰጥም ስላሉ ብቻ ነዉ።» ሲሉ ጽፈዋል። ከተማው ጥሩነህ ሙሉዬ በበኩላቸው «እኔ ምክንያቱ ምን እንደሆነ አላወኩም ። ምክንያቱ ምንም ይሁን ምን ግን ድርጊት በጣም አሳፋሪ እና የቀድሞ ዘመንን አስታዋሽ ነው ።» ሲሉ በድርጊቱ የተሰማቸውን ሐዘን ገልጠዋል።የኢትዮጵያ መንግስት ኮምዩንኬሽን ሚኒስትር አቶ ጌታቸው ረዳ የሱርማው ኩነት በክልሉ መንግስት በመጣራት ላይ መሆኑን ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል።

በሱርማ የተፈጸመውን ድርጊት አስመልክቶ የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ዝምታን ቢመርጥም ፌስቡክና ትዊተርን የመሳሰሉ ማህበራዊ ድረ-ገጽ ተጠቃሚ አራማጆች ድርጊቱ ክፉኛ ተኮንኗል። በዶይቼ ቬለ የፌስቡክ ገጽ «አሳሪዎች የት ሀገር ዜጋ ናቸው?» ሲሉ የጠየቁም ይገኛሉ። ድርጊቱን ጭካኔያዊ እርምጃ ሲሉ የኮነኑ በርካታ ኢትዮጵያውያን በሕገ-መንግስቱ ተከበረ የተባለውን የብሄር ብሄረሰቦች መብት ተጨባጭነት በተደጋጋሚ ጠይቀዋል። አቶ ጌታቸው ረዳ ድርጊቱን መንግስታው እንደሚያወግዝ ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል።

የሱርማ ወረዳ በደቡብ ብሔር ብሄረሰቦች እና ህዝቦች ክልል በቤንች ማጂ ዞን የሚገኝ ሲሆን በከብት እርባታ እና አነስተኛ የእርሻ ሥራ የሚተዳደሩት ሱሪ አሊያም ሱርማ ጎሳ መገኛ ነው። የኢትዮጵያ መንግስት ለመገንባት ካቀዳቸው የስኳር ፋብሪካዎች መካከል አንዱ የሆነው የኦሞ ኩራዝ የስኳር ፋብሪካ የሚገነባው የሱርማ ጎሳ አባላት በሚገኙበት የደቡብ ኦሞ ነው።

እሸቴ በቀለ

ነጋሽ መሐመድ