1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ስለHIV የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በኑረንበርግ

ማክሰኞ፣ ጥቅምት 9 2008

ከዓመታት በፊት ከነበረዉ ጋር በማነፃፀር የHIV ተሐዋሲ ስርጭት በመጠኑ መቀነሱ ቢነገርም ዛሬም ይህ በሽታ አሳሳቢ እንደሆነ ነዉ። ባለፈዉ ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት 2014 ብቻ ከአንድ እስከ አንድ ነጥብ አምስት ሚሊየን የሚገመቱ ሰዎች በHIVእና ከእርሱ ጋር በተያያዙ የጤና እክሎች ሕይወታቸዉ አልፏል።

https://p.dw.com/p/1Gr8n
Gemeinsamer Arm Gegen Aids e.V. Preisverleihung
ምስል Gemeinsamer Arm Gegen Aids e.V.

ስለHIV የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በኑረንበርግ

የዓለም የጤና ድርጅት ስለHIV በድረ-ገጹ ካሰፈራቸዉ እዉነታዎች አንዱ በዚህ በሽታ ክፉኛ ከተጠቃዉ የዓለም ክፍል ከሰሃራ በስተደቡብ የሚገኘዉ አካባቢ ግንባር ቀደሙ መሆኑን ያመለክታል። በድርጅቱ ዘገባ መሠረትም በጎርጎሪዮሳዊዉ 2014ዓ,ም በተጠቀሰዉ አካባቢ 24 እስከ 28,7 ሚሊየን ሕዝብ ቫይረሱ በደሙ ዉስጥ እንደሚገኝ ተረጋግጧል። በHIV ምክንያት በየዓመቱ ከሚሞተዉ ሰዉ 70 በመቶዉም የሚገኘዉ ከሰሃራ በስተደቡብ ባሉ ሃገራት ነዉ። ኢትዮጵያ ዉስጥ በHIV ወላጆቻቸዉን ላጡ ልጆች የበኩላቸዉን ከመርዳት አልፈዉ በኑረንበር ከተማ እና አካባቢዉ ለሚገኙ ወገኖቻቸዉ ስለበሽታዉ የሚያዉቁትን በበጎ ፈቃደኝነት በማካፈል ተግባር የተጠመዱት ሶስት ኢትዮጵያዉያን ስለማኅበራቸዉ እንቅስቃሴ ባለፈዉ ሳምንት በከፊል አካፍለዉናል።

Gemeinsamer Arm Gegen Aids e.V. Preisverleihung
ምስል Gemeinsamer Arm Gegen Aids e.V.

የኅብረት ክንድ በኤድስ ላይ ማኅበር በኑረንበርግ ከተማ አቅራቢያ በሚገኘዉ የስደተኞች መመዝገቢያ እና መጠለያ ስፍራ በወር አንድ ጊዜ እየተገኘ በሀገር ባህልና ወግ መሠረት ቡና እየተጠጣ ስለHIV ሰዎች ሊያዉቁት የሚገባ መረጃን ሲያካፍል ዓመታት ተቆጥረዋል። ከዚህም ሌላ በምርመራ HIV ተሐዋሲ በደማቸዉ ዉስጥ እንደሚገኝ ያወቁ ሆኖም ግን የመድኃኒት አቅርቦት ችግር በሌለበት በጀርመን ሀገር የሚያደርጉት ጠፍቷቸዉ አንገታቸዉን ሰብረዉ የተቀመጡ ወገኖችን ወደተገቢዉ ስፍራ የመዉሰድና የማበረታታት ተግባርንም ያከናዉናል። በየጊዜዉም ኢትዮጵያ ዉስጥ በHIV/AIDS ወላጆቻቸዉን ላጡ በርካታ ልጆች አቅም የፈቀደዉን ድጋፍ ያደርጋል። ይህን ጥረት ለየት የሚያደርገዉ የሃሳቡ ጠንሳሾች የሆኑት ሶስት የማኅበሩ ዓባላት በበጎ ፈቃደኝነት ለራሳቸዉ የሰጡት የማይቋረጥ ኃላፊነት መሆኑ ነዉ። ይህ ማኅበር በዚህ ረገድ ላበረከተዉ አስተዋፅኦ ጀርመን ሀገር ዉስጥ ከሚንቀሳቀሱ አንድ መቶ ፕሮጀክቶች ጋር ተወዳድሮ ያለምንም የገንዘብ ድጋፍ ያከናወነዉ ተግባር ሚዛን በመድፋቱ እንደሆነ በይፋ ተነግሮለታል።

Gemeinsamer Arm Gegen Aids e.V. Preisverleihung
ምስል Gemeinsamer Arm Gegen Aids e.V.

በአዉሮጳ የሩጫ ኑሮ በተለይም እዚህ ጀርመን ሀገር ይህን መሰሉን ሰብዓዊ ተግባር ለማከናወን በጥገኝነት የሚኖሩ ወገኖች በራሳቸዉ የሕይወት ድር ተተብትበዉ እጅግም ትኩረት ሲሰጡት መመልከት ብዙም አልተለመደም። አንዳንድ እንቅስቃሴዎች ቢኖሩን የሌሎች ወገኖችን ቀልብ የሚስብ ዉጤት ሲያሳዩ አይታይም። ይልቁንም መከራከር መለያየት መጓተቱ አይሎ ይታያል። የኅብረት ክንድ በኤይድስ ላይ ማኅበር ሊቀመንበር አቶ ዮናስ ትርጉም ያለዉ ሥራ ለመሥራት የሰዎች ብዛት ሳይሆን የሃሳብ አንድነት ትርጉም እንዳለዉ የእነሱ ዉጤት እንደሚያመላክትና ለሌሎችም ትምህርት እንደሚሆን ሳይገልፅልን አላለፈም። ሙሉዉን ቅንብር ከድምጽ ዘገባዉ ያድምጡ፤

ሸዋዬ ለገሠ

አዜብ ታደሰ