1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢትዮጵያ የመንግሥት ሰራተኞች ስብሰባዎች እና ውይይቶች

ዓርብ፣ ጥር 19 2009

የኢትዮጵያ መንግሥት ላለፉት ሁለት ሳምንታት የመንግሥት ሰራተኞችን ሰብስቦ ሲያወያይ፤ ሲያሰለጥን እና ሲገመግም ከርሟል። ለውይይት በዝግጅት ላይ የሚገኙም አሉ። በውይይቱ የተሳተፉት ግን አገሪቱ የገጠሟት ችግሮች በዚህ መንገድ ስለመፈታታቸው ጥርጣሬ አላቸው።

https://p.dw.com/p/2WT4o
Äthiopien Protesten der Oromo in Bishoftu
ምስል REUTERS/File Photo/T. Negeri

Can meetings and trainings solve Ethiopia’s Political Gridlock? - MP3-Stereo

የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ሰራተኞቹን ወደ « በጥልቅ ተሀድሶ ግምገማ» ሊያስገባ መዘጋጀቱን አስታውቋል። የክልሉ መንግሥት ካሉት 345 ሺህ ያህል ሰራተኞች መካከል ከመምህራን ውጪ ያሉት በዚሁ «ጥልቅ ተሃድሶ ግምገማ» ይሳተፋሉ። ይህ ግን የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ብቻ ተግባር አይደለም። የገዢው ግንባር አባል የሆነው የደቡብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ማዕከላዊ ኮሚቴ 265 አመራሮቹ በሕዝብ ግምገማ ከኃላፊነታቸውን መነሳታቸውን ባለፈው ሳምንት ገልጧል። ከፍተኛ ተቃውሞ እና ኹከት ተቀስቅሶበት የነበረው የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በበኩሉ ላለፉት አራት ቀናት በመንግሥት ሰራተኞቹ ዘንድ «የጥልቅ ተሀድሶ ወይይቶች» ሲያካሒድ ከርሟል። ስሜን ደብቁልኝ ያሉን አድማጭ ገዢው ፓርቲ ችግሮች ሲገጥሙት ስብሰባ እና ውይይት የተለመደ እንደሆነ ይናገራሉ። 
ለአምስት ቀናት በተመሳሳይ የተሐድሶ ውይይት ላይ የተሳተፉት የመንግሥት ሰራተኛ በአማራ ክልል ነዋሪ ናቸው። የመንግስት ሰራተኛው የተሳተፉት በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ስርዓት እና ጥልቅ ተሐድሶ የሚል ርዕሶች በተሰጣቸው የውይይት መድረኮች ላይ ቢሆንም ከጅማሮው አለመግባባት እንደነበረበት አስተውለዋል። 
በኦሮሚያ እና የአማራ ክልሎች ከተከሰተው ተቃውሞ እና ኹከት በኋላ የኢትዮጵያ መንግሥት የውይይት መድረኮች የጀመረው በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ነበር። አቶ መብራቱ ማርሴ በወልድያ ዩኒቨርሲቲ መምህር ናቸው። መምህሩ ከመስከረም 5-10 ቀን ድረስ በተካሔዱት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መምህራን እና ሰራተኞች ውይይቶች ላይ አቶ መብራቱ ተሳትፈዋል። መምህሩ በኦሮሚያ እና አማራ ክልሎች የተቀሰቀሱት ተቃውሞዎች ወደ ሌሎች አካባቢዎች እንዳይስፋፉ እና የንብረት ውድመት እንዳያስከትሉ «በእንጭጩ መቀጨት አለባቸው» የሚሉ ውይይቶች መካሔዳቸውን ያስታውሳሉ። መምህራን እና የአስተዳደር ሰራተኞች በነፃነት በገለጹበት መድረክ የአማራ ክልል ባለስልጣናት ምላሽ መስጠታቸውንም ተናግረዋል። የአማራ ክልሉ ነዋሪ በውይይት መድረኮቹ ትችት የቀረበባቸው ባለሥልጣናት ለጥፋታቸው ሲጠየቁ አለመመልከታቸውን ይናገራሉ። አስተያየት ሰጪው የኢትዮጵያ መንግሥት የሚወስዳቸው እርምጃቸዎች መፍትሔ ስለመሆናቸው አጥብቀው  ይጠይቃሉ።

Äthiopien Gedeo Grundstücke Brand Protest
ምስል W/O Aynalem/R.Abeba

በዶይቼ ቬለ የፌስቡክ ማሕበራዊ ድረ-ገፅ እንዲሁም በዋትስ አፕ በዚሁ ርዕሰ ጉዳይ ላይ አስተያየታቸውን ያደረሱንም ቢሆኑ የኢትዮጵያ መንግሥት ስብሰባዎች እና ውይይቶች መፍትሔ ስለመሆናቸው ጥርጣሬ አላቸው። ደስአለኝ ሙሼ «ሽህ ጊዜ መሰብሰብ ስልጠና መስጠት ለውጥ አያመጣም ህዝብ የጠየቀው የስርአት ለውጥ ነው አበቃ!» ሲሉ አስተያየታቸውን አስፍረዋል። እዮብ ተክሉ ደግሞ «መንግሰት ሁሌም ህዝብን ሳያወያይ ያዘጋጀውን የራሱን ፖሊሲና ስትራቴጂ አትሞ ከላይ ከአንድ ማዕከል ወደ ታች በማውረድ አሰልጣኝ አመራሮቹ እንኳ በአግባቡ ያልተረዱትን ሰነድ ስልጠና ብለው የግዜ የገንዘብና ጉልበት ወጪ ወጥቶበት ወር ሳይሞላው ሌላ ስለጠና ስብሰባ» ሲሉ መንግሥት የሚከተለውን ስልት ነቅፈዋል። ሱደየስ ሬያን «ስብሰባዉ ገዢው መደብ ላይ በተነሱበት አመጾች እና አንፈልህግም በመባሉ ሂደት እነማን አሉበት ብሎ ለመሰለልና ወይ ለማፈን አለያም ወደ እስርቤት ለመወርወር የታቀደ መድረክ ነዉ።» የሚል አስተያየት አስፍረዋል። 


እሸቴ በቀለ
አዜብ ታደሰ