1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ስፓኝ ዳግም የአውሮፓ ሻምፒዮን

ሰኞ፣ ሰኔ 25 2004

በፖላንድና በኡክራኒያ የጋራ አስተናጋጅነት ባለፉት ሶሥት ሣምንታት ሲካሄድ የሰነበተው የአውሮፓ እግር ኳስ ዋንጫ ውድድር ባለፈው ምሽት ኪዬቭ ላይ በተካሄደ ፍጻሜ ግጥሚያ በስኬት ተጠናቋል።

https://p.dw.com/p/15PvW
ምስል Reuters

በፖላንድና በኡክራኒያ የጋራ አስተናጋጅነት ባለፉት ሶሥት ሣምንታት ሲካሄድ የሰነበተው የአውሮፓ እግር ኳስ ዋንጫ ውድድር ባለፈው ምሽት ኪዬቭ ላይ በተካሄደ ፍጻሜ ግጥሚያ በስኬት ተጠናቋል። በፍጻሜው ግጥሚያ በአጨዋወት ስልቱም ሆነ ብቃቱ አቻ የማይገንለት ዕጹብ-ድንቅ የስፓን ብሄራዊ ቡድን ኢጣሊያን በፍጹም ልዕልና 4-0 ሲያሸንፍ ይህም ከአራት ዓመት በኋላ ዳግም ድሉ መሆኑ ነው።

የስፓን ብሄራዊ ቡድን በአራት ዓመት ጊዜ ውስጥ የአውሮፓ፣ የዓለምና እንደገና መልሶ የአውሮፓ ሻምፒዮን በመሆን አዲስ ታሪክ ሲያስመዘግብ ፍጻሜው ግጥሚያ በዚህ መጠን በብዙ ጎል ሲለይለትም ለመጀመሪያ ጊዜ መሆኑ ነው። አሠልጣኙ ቪቼንቴ-ዴል-ቦስክ የኢጣሊያ ተጫዋቾች አንዳች ዕድል እንዳልነበራቸው ነው የገለጹት።

«ጨዋታው ለኛ ቀደም ብሎ ነው የቀና የነበረው። ለነገሩ የኢጣሊያ ተጫዋቾች በአሥር ሰው እንኳ ሆነው ማጥቃታቸውን አላቆሙም። ሆኖም በዚሁ የተነሣ ከኋላ ብዙ ይከፍታሉ። እናም ፋታ አልነበራቸውም»

UEFA EURO 2012 Spanien vs. Italien Tor
ምስል Reuters

በእርግጥም የስፓኝ ቡድን ልዕልና ለማንም የተሰወረ አልነበረም። ቡድኑ «ቲኪ-ታካ» የተሰኘ የአጭር ቅብብል ስልቱን በተካኑት የመሃል ሜዳ መሃንዲሶቹ በሻቪና በኢኒየስታ መሪነት ድንቅ ጨዋታ ሲያሳይ በዚሁ ግሩም ጥበቡና በጎል ፌስታው ዓለምን ይበልጥ ነው የማረከው። ስፓን ውስጥም የእግር ኳስ የበላይነት በአደባባይ ሲነግስ ተጫዋቹ ሤስክ ፋብሬጋስ እንዳለው የደስታውን ሰሜት ሊገልጹት እጅጉን የሚያዳግት ነው።

«ሊያምኑት የሚያዳግት ነገር ነው። ስሜቴን ለመግለጽ በዕውነቱ ቃላት ያጥሩኛል። ወደፊትም በማሸነፍ እንደምንቀጥል ተሥፋ አደርጋለሁ። ምክንያቱም ገና ወጣቶች ነንና»

በዕውነትም ይህ ቡድን አብሮ ከቆየ ከሁለት ዓመታት በኋላ ብራዚል ውስጥ በሚካሄደው የዓለም ዋንጫ ውድድር ለሌላ አዲስ ታሪክ የሚበቃም ነው። ወደ አውሮፓው ዋንጫ ውድድር እንመለስና በጎል አግቢነትም ከአራት ዓመታት በፊት የስፓን የድል ዋስትና የነበረው ፌርናንዶ ቶሬስ ቀደምቱ ለመሆን በቅቷል። በተረፈ ፖላንድና ኡክራኒያ ደግሞ መስተንግዶው እንደተዋጣላቸው አንድና ሁለት የለውም።

Swasiland Sportler
ምስል Farina Klüver

አትሌቲክስ

ቤኒን ውስጥ ካለፈው ረቡዕ ወዲህ የተካሄደው የአፍሪቃ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ትናንት ተጠናቋል። በውድድሩ ናይጄሪያ አንደኛ ስትሆን ኬንያ ሁለተኛ ወጥታለች። ኢትዮጵያ ደግሞ ከኬንያ 27 ሜዳሊያዎች ሲነጻጸር እጅግ ዝቅተኛ በሆነ ሶሥት ሜዳሊያ በመወሰን 17 ነው የሆነችው። በአጠቃላይ ስለ ኢትዮጵያ አትሌቶች ተሳትፎ በስፍራው የተገኘችውን ወኪላችንን ሃይማኖት ጥሩነህን ዛሬ ረፋዱ ላይ በስልክ አነጋግሬ ነበር። ያድምጡ!

ለማጠቃለል ከአስናጋጇ አገር በኩል የዝግጅትና የቅንጅት ብቃት ጉድለት በጣሙን ጎልቶ ታይቷል። በሶሥት ሺህ ሜትር መሰናክል ሩጫ ሁለተኛ የወጣችው ብርቱካን አዳሙ እንዳመለከተችው አትሌቶች እስከመራብና እስከመንገላታት ደርስው ነበር። እንዲያውም ከነርሱ ይልቅ እንክብካቤው ለባለሥልጣናት ያደላ ሆኖ ነው የተገኘው። በዳንነትም በኩል ብዙ ውዥምብር መከሰቱን ከወኪላችን ለመረዳት ችለናል።

መሥፍን መኮንን

ሒሩት መለሰ