1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ሶሻል ዲሞክራቶች በጥምር መንግሥት ምስረታው ተስማሙ

እሑድ፣ የካቲት 25 2010

በጀርመን ምክር ቤት በርካታ ወንበር በመያዝ ሁለተኛ የሆነው ሶሻል ዲሞክራቲክ ፓርቲ (SPD) ከመራኂተ-መንግሥት አንጌላ ሜርክል ፓርቲ ጋር ጥምር መንግሥት ለመመስረት የደረሰበትን ስምምነት አባላቱ ዛሬ አጸደቁ፡፡

https://p.dw.com/p/2tfv4
Deutschland Ergebnis des SPD-Mitgliedervotums
ምስል Reuters/H. Hanschke

ሶሻል ዲሞክራቶች ጥምር መንግስት ምስረታን አጸደቁ

በጀርመን ምክር ቤት በርካታ ወንበር በመያዝ ሁለተኛ የሆነው ሶሻል ዲሞክራቲክ ፓርቲ (SPD) ከመራኂተ-መንግሥት አንጌላ ሜርክል ፓርቲ ጋር ጥምር መንግሥት ለመመስረት የደረሰበትን ስምምነት አባላቱ ዛሬ አጸደቁ፡፡ የሶሻል ዴሞክራቶቹ ውሳኔ ላለፉት አምስት ወራት በሞግዚት ስትተዳደር ለቆየችው ጀርመን አዲስ መንግስት ያስገኝላታል፡፡ 

የSPD መሪዎች ከሜርክል ወግ አጥባቂ ፓርቲ ጋር ጥምር መንግስት ለመመስረት ውሳኔ ላይ የደረሱት ከሳምንታት በፊት ቢሆንም ወደ ተግባር ለመግባት የፓርቲያቸው አባላትን ይሁንታ መጠበቅ ነበረባቸው፡፡ ከ460 ሺህ በላይ የፓርቲው አባላት ስምምነቱን መቀበል ወይንም አለመቀበላቸውን የወሰኑበት ድምጻቸውን በደብዳቤ እንዲልኩ ተጠይቀው ነበር፡፡ ድምጻቸውን ከሰጡ አባላት መካከል 66 በመቶው የጥምር መንግሥት ምስረታውን መደገፋቸውን እና 33 በመቶው መቃወማቸውን ፓርቲው ዛሬ በርሊን ከሚገኘው ዋና ጽሕፈት ቤቱ ይፋ አድርጓል፡፡ የጥምር መንግስቱ ደጋፊዎች ቁጥር አስቀድሞ ከተገመተው በላይ ከፍ ያለ ነው ተብሏል፡፡ 

Infografik SPD Mitgliederbefragung GroKo DEU
66 በመቶው ለጥምር መንግሥት ምስረታው የይኹንታ ድምፃቸውን ሲሰጡ፤ 33 ከመቶው አልተስማሙም

የፓርቲው ተጠባባቂ ሊቀመንበር ኦላፍ ሾልዝ “ውሳኔው ለSPD ቀላል አልነበረም” ብለዋል፡፡ “በስምምነቱ ላይ በነበረን ውይይት ይበልጥ አንድ ሆነናል፡፡ ያ ለጀመርነው የተሃድሶ ሂደት ጥንካሬ ሆኖናል” ሲሉ አክለዋል፡፡ የጥምር መንግሥት ምስረታው ስምምነት ከሁለት ሳምንት ባነሰ ጊዜ ውስጥ ይፈረማል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የጀርመን ምክር ቤት (ቡንደስታግም) ሜርክልን በድጋሚ መራኂተ-መንግሥት አድርጎ ይመርጣል ተብሏል፡፡ አዲስ የሚመሰረተው ጥምር መንግሥት ሜርክል በመሪነት በቆዩባቸው 13 ዓመታት ውስጥ ሦስተኛው ይሆናል፡፡

የሶሻል ዲሞክራቶቹ አባላት ውሳኔን በተመለከተ የበርሊኑ ወኪላችን ይልማ ኃይለሚካኤል ጋር የተደረገው ሙሉ ቃለ መጠይቅ ከታች የድምፅ ማዕቀፉ ውስጥ ይገኛል። 

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ይልማ ኃይለሚካኤል

ተስፋለም ወልደየስ