1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ቀጠርና የአደራዳሪነት ሚናዋ

ዓርብ፣ ሰኔ 14 2005

የቀተር የውጭ መርህ እንደ እስካሁኑ ላይቀጥል ይችላል። የቀተሩ አሚር ሼክ ሃማድ ቢን ካሊፋ ጤና በማጣታቸው ከሥልጣናቸው ሳይነሱ አይቀርም ። እንደ መጀመሪያ ደረጃ ተደርጎ የሚወሰደው የሚተካቸው ወንዱ ልጃቸው ሼክ ታሚም የጠቅላይ ሚኒስትርነቱንም ቦታ እንዲይዙ ማድረግ ሳይሆን አይቀርም ። በዚህም ቀጠር አስተዋይና ታዋቂ ዲፕሎማትዋን ታጣላች ።

https://p.dw.com/p/18u5F
ምስል XtravaganT/Fotolia

በቀጠር ዋና ከተማ ዶሃ በትናትናው እለት ዩናይትድ ስቴትስና ታሊባን የሰላም ንግግር ለማካሄድ ቀጠሮ ይዘው ነበር ። ይሁንና ታሊባን ቀጠር ውስጥ ቢሮ መክፈቱ የአፍጋኒስታን መንግሥትን አስቆጥቶ በተከተለው ግርግር ምክንያት ንግግሩ ሳይካሄድ ቀርቷል ። የአሜሪካንና የታሊባን ንግግር መቼ እንደሚካሄድ ከዶሃ በኩል የሚታወቅ ነገር እንደሌለ ቢገለፅም የዋሽንግተን መንግሥት ግን የሰላም ድርድሩ በቅርቡ ይካሄዳል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስታውቋል ። ድርድሩም እዚያው ዶሃ ይሆናል ተብሎ ነው የሚታሰበው ። ትንሽቷ ቀጠር በተደጋጋሚ ጊዜያት በዓለም ዓቀፍ አደራዳሪነት የምትጫወተው ሚና ከፍተኛ ነው ። በስፋት ከጀርመኑ የሄሰን ፌደራዊ ክፍለ ሃገር ግማሽ ያህል የምትሆነው ቀጠር ከመካከለኛው ምሥራቅ ተሰሚነት ያላት ሃገር ናት ። ከ 10 ዓመታት አንስቶ ቀጠር በየአካባቢው የሚከሰቱ ግጭቶችን ስትሸመግል ቆይታለች ።

Taliban eröffnen Büro in Doha Qatar
የዶሃው አዲሱ የታሊባን ቢሮምስል Reuters

በዚህ ረገድ የየመን የሶማሊያ የሊባኖስ የዳርፉርና የቻድ ግጭቶችን ለመፍታት የተጫወተችው የሽምግልና ሚና በምሳሌነት ይጠቀሳል ። ይህ ሚናዋ እየተጠናከረ የመጣውም በብሩኪንግስ የዶሃ የጥናት ማዕከል ባልደረባ ሻዲ ሃሚድ እምነት ሃገሪቱ ፣ ከእስራኤል ከሃማስ ከቴህራን እንዲሁም ከዋሽንግተን ከታሊባንና ከአፍጋኒስታን ፕሬዝዳንት ሃሚድ ካርዛይ ጋር ለመነጋገር ዝግጁ ሆና በመገኘትዋ ነው ።«ቀጠር ለብዙ ዓመታት አዳዲስ ሃሳቦችን ያካተተ ፣ ገለልተኛ ና ልዩ የውጭ መርህ አላት ። ያ ነው ለቀተር በዓለም ውስጥ ልዩ ቦታ የሚያሰጣት ። ቀተር ግጭቶችን በገለልተኛ መንገድ ለመፍታት በ ምታደርገው ሙከራ መቀጠሏ ትርጉም አለው ። ቀተር ለዚህ ወይም ለዚያኛው የወገነች ሆና ለመታየት አትፈልግም ። እንደሚመስለኝ ይህ ቀተርን ይጠቅማል ። ይህን ማድረግም ትፈልጋለች ። ለማንም ያልወገነ ገለልተኛ አቋም መያዝ ነው የምትፈልገው ።»በአፍጋኒስታኑ የሰላም ንግግር ቀጠሮች ለማንም አልወገኑም ። ሆኖም ከአሜሪካን ጋር ወታደራዊ አጋር ናቸው ፤ ከታሊባን አንጃዎች መካከል ቢያንስ የአንዱን አመኔታ ማግኘታቸው ያስደስታቸዋል ።

Katar Doha USA Außenminister Kerry mit Hamad ibn Dschasim ibn Dschabir Al Thani
ሼክ ሃማድ ቢን ያሲም አልታኒምስል Reuters

ይህ ደግሞ አስቸጋሪ ሊሆን እንደሚችልና ረዥም ጊዜ እንደሚወስድም ለሚገመት ንግግር ገለልተኛ ሚና መጫወት ያስችላቸዋል ። ቀጠር ገለልተኛ የውጭ መርህ ልትይዝ የመቻልዋ ምክንያት ሃብታም፣ የዓለም ዋነኛዋ ነዳጅ ዘይት አምራች ና ሻጭ ሃገር በመሆንዋ ነው ይላሉ RUSI የተባለው የዶሃ የጥናት ተቋም ባልደረባ ማይክል ስቴፈንስ «ካታር እጅግ ብዙ ገንዘብ ያላት ሃገር ናት ። በገንዘቡ ምን ማድረግ እንዳለባት በርግጥ አታውቅም ። ገንዘቡን በተለይ ለውጥ ለማምጣት የሚያስችሉ መንገዶች ለማመቻቸት ልትጠቀምበት ትችላለች ። ያንንም ታደርጋለች ። በምትንቀሳቀስባቸው ሃገሮች የብዙሃኑን አመለካከት ይወክላሉ ብላ የምታስባቸውን ንቅናቄዎች ወይም የፖለቲካ ፓርቲዎች በገንዘብ ለመደገፍ ትሻለች ። »

ዋነኛው የጉዳዩ አንቀሳቃሽ የ53 ዓመቱ የቀጠር ጠቅላይ ሚኒስትርና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሼክ ሃማድ ቢን ያሲም አልታኒ ናቸው ። አልታኒ ጠንካራ ስብዕናና ተስጥኦ ያላቸው ፖለቲከኛ ና የተካኑ ዲፕሎማትም ጭምር ናቸው ። ማይክል ስቴፈንስ እንደሚሉት ቀጠሮች ድርድሮች እንዲካሄዱ የሚያደርጉባቸው መንገዶች ይለያሉ ።

« አንዳንድ ጊዜ ቀጠሮች እጅግ የከረረ ጠብ ያላቸውን አንጃዎች ያደራድራሉ ። በሮቹን ዘግተው አንድ መግባቢያ ላይ እስክትደርሱ ድረስ እዚሁ እንቀመጣለን ይላሉ ። ይህን ለማድረግ የሆነ ጥንካሬ ያስፈልጋል ። »

Ghazi Salah Al-Deen Al-Attabani
የሱዳን መንግሥትና ና የሱዳን የፍትህና የነፃነት ንቅናቄ ስምምነት በዶሃምስል picture-alliance/dpa

አንዳንዴ ግጭቶች ሰላማዊ መፍትሄ ሲታጣላቸው ውዝግብን በወታደራዊ ኃይል ለመፍታት ነው ጥረት የሚደረገው ። ለዚህም ሶሪያና ሊቢያ ምሳሌዎች ናቸው ። ቀጠር በውጭ መርኋ መሰረት ግጭቶችን ለማስወገድ የምታደርጋቸው ጥረቶች በሙሉ ተሳክተዋል ማለት አይቻልም ። ምንም እንኳን ቀጠር የሶሪያ ተቃዋሚ ወገኖችን በትጋት የምትደግፍ ቢሆንም በሶሪያም ይህን ነው የሚባል ውጤት አልተገኘም ። ይህ የቀተር የውጭ መርህ እንደ እስካሁኑ ላይቀጥል ይችላል ። እንደሚሰማው ከሆነ የቀተሩ አሚር ሼክ ሃማድ ቢን ካሊፋ ጤና በማጣታቸው ከሥልጣናቸው ሳይነሱ አይቀርም ። እንደ መጀመሪያ ደረጃ ተደርጎ የሚወሰደው የሚተካቸው ወንዱ ልጃቸው ሼክ ታሚም የጠቅላይ ሚኒስትርነቱንም ቦታ እንዲይዙ ማድረግ ሳይሆን አይቀርም ። በዚህም ቀጠር ታታሪና አስተዋይ ታዋቂ ዋና ዲፕሎማትዋን ታጣላች ። ሼክታሚም እንደሚተኳቸው ባለሥልጣን ፣ ተግባራቸውን ያካሂዳሉ ተብሎ የሚጠብቅ የለም ። ታሚም የ 33 ዓመት ጎልማሳ ናቸው ። እድሜ ትልቅ ሚና በሚጫወትበት በአረቡ ዓለም የሼክታሚ እድሜ ለሽምግልና ብቁ አያደርጋቸውም ።

ሂሩት መለሰ

አርያም ተክሌ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ