1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በማራ ክልል የተቀሰቀሰዉ ግጭት

ሐሙስ፣ ጥር 18 2015

ባለፈው ቅዳሜ በጂሌ ዱሙጋ ተከስቷል የተባለው ግጭት ወደ አጎራባች አከባቢዎች ተዛምቶ የከፋ ቀውስ ካስከተለ በኋላ የተለያዩ አካላት መፍትሄ ያሉትን እየገለጹ ነው፡፡ኦነግ ግጭቱ ፖለቲካዊ እልባት ይሻል ሲል የአማራ ክልል መንግሥት ያልታወቁ ታጣቂዎች በፀጥታ ኃይሎችና በዜጎች ላይ ከፈቱት ላለው ጥቃት የመጨረሻ እልባት እንደሚሰጥ አስታውቋል።

https://p.dw.com/p/4MjF1
Äthiopien Regierung reagiert auf humanitäre Krise
ምስል Seyoum Getu/DW

በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደርና በሰሜን ሸዋ ዞን አዋሳኝ ወረዳዎች የተቀሰቀሰው ግጭት

ሰሞኑን በአማራ ክልል በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደርና በሰሜን ሸዋ ዞን አዋሳኝ ወረዳዎች የተቀሰቀሰዉ ግጭት ለበርካቶች ህልፈትና የንብረት ውድመት ምክንያት መሆኑ ተነግሯል፡፡ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ቅዳሜ ከሰኣት በጂሌ ዱሙጋ ተከስቷል የተባለው ይህ ግጭት ወደ አጎራባች አከባቢዎች ተዛምቶ የከፋ ቀውስ ካስከተለ በኋላ የተለያዩ አካላት አስተያየት እና መፍትሄ ያሉትን እየገለጹ ነው፡፡የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ)ግጭቱን በተመለከተ ባወጣው መግለጫ አከባቢውን ደጋግሞ የሚጎበኘው አለመረጋጋት “የፖለቲካ ሸፍጥ” በመሆኑ ዘላቂ  ፖለቲካዊ እልባት ይሻል ብሏል፡፡የአማራ ክልላዊ መንግስት ከአንድ ቀን በፊት በሰጠው መግለጫ «ያልታወቁ ታጣቂዎች» በፀጥታ አካላት እና ንጹኀን ዜጎች ላይ ከፍተዋል ላለው ጥቃት የመጨረሻ እልባት እንደሚሰጥ አስታውቋል።

የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) በሰሞኑ የኦሮሞ ብሔረሰብ ልዩ ዞን እና ሰሜን ሸዋ አዋስ ግጭቱ ላይ ባወጣው መግለጫ በጂሌ ዱሙጋ ተከስቶ የተስፋፋው የቅዳሜ ከሰዓቱ ግጭት መነሻ የመንግስት ታጣቂዎች ሰላማዊ ያላቸው አርሶ አደሮች ላይ ተኩስ መክፈታቸው ነው ይላል፡፡ ከክልሉ መንግስት እውቅና ውጪ ወሎ የተደረገ አንዳችም ነገር የለም ያለው የኦነግ መግለጫ በህብረተሰቡ ላይ በታጣቂዎች የተቀናጀ ጥቃት ተደጋግሞ ይፈጸማል በማለትም ትችቱን ሰንዝሯል፡፡ የፓርቲው ቃል አቀባይ አቶ ለሚ ገመቹ በተለይም ለዶይቼ ቬለ በሰጡት ተጨማሪ ማብራሪያ፤ “ወሎ ላይ በተደጋጋሚ በሚሰነዘሩ የተቀናጁ ጥቃቶች በየጊዜውም የህይወት እና የሃብት ውድመቶች ይከሰታሉ፡፡ በዚያ በወሎ የኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ላይ እያስተዋልን ያለነውን ጥቃት በኦሮሚያም ከታወጀው ጦርነት አንድ አካል አድርገን ነው የምንመለከተው፡፡ የጦርነቱ ዓላምም ከሃብት እና መሬት ማቀራመት አልፎ ወደ ማንነት የተሸጋገረ ነው የሚመስለው፡፡ ላለፉት አምስት ቀናት የቀጠለው ይህ ግጭት አሁን በአጎራባች ወረዳዎች በሰፊው ተስፋፍቶ መስተዋሉን ነው በመዋቅራችን በኩል በሚደርሰን መረጃ ያረጋገጥነው” ብለዋል፡፡

 

ኦነግ ይህን ይበል እንጂ ስለግጭቱ መነሻ፣ ሥለደረሰዉ ጉዳት መጠንና ተጠያቂ ስለሚባሉ ወገኖች የሚሰጡ አስተያየቶች የተለያዩ ናቸው፡፡ ለአብነትም መቀመጫውን ዩናይትድ ስቴትስ ያደረገዉ የሰሜን አሜሪካ የአማራ ማህበር «ድንገት ተከፈተ» ያለውን የቅዳሜ ከሰኣቱ ጥቃት በኦሮሞ ነፃነት ጦር ተከፍቶ ከ100 በላይ የአማራ ልዩ ኃይል ባልደረቦች በዚሁ ሰበብ ለመገደላቸዉ መረጃ አለኝ ይላል።

የኦነግ ባለስልጣኑ አቶ ለሚ ገመቹ ግን ይህን በሀሰትነት ጠቅሰው፤ ለግጭቱ መነሻው የመንግስት ፀጥታ ኃይሎች ንጹሃን ላይ ያነጣጠረ ጥቃት መውሰዳቸው ነው ብለዋል፡፡ “ሲጀመር ሸማቂ ኃይሎች ቤት ንብረት አፍርተው እንዴት እዚያ አከባቢ ይኖራሉ? ጥቃቱ እኮ የተጀመረው እዚያው አከባቢ በሚኖሩ ወጣቶች ላይ ነው፡፡ ሰላማዊ ዜጎች ላይ ያነጣጠረ ጥቃት ነው የተፈጸመው፡፡ የኦሮሞ ቤቶችም ተለይተው ይቃጠላሉ፤ ከዚህ በፊትም ከወሎ ኦሮሞ የተወከሉት የፓርላማ ተወካይ እንዳብራሩት በክልሉ ታጣቂዎች ሸነ የሚል የዳቦ ስም ተሰጥቷቸው ሰላማዊ ዜጎች ሰለባ ሆነዋል በሚል ተገልጾ ነበር፡፡ አሁንም ያው ነው መልኩን እየቀያየረ ሸማቂ ኃይልን ማጥፋት በሚል መጋረጃ ስር መጣ፡፡”

አቶ ለሚ በወሎም ይሁን በወለጋ ብሔር ላይ አነጣጥሮ ለሚፈጸም ጥቃትና ግጭት ፖለቲከኞች የፖለቲካ እልባት ሊሰጡት የሚገባው ነው በማለትም አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ ፓርቲያቸው ህዝብ መሃል ያለ ጥላቻ እና አለመተማመን የለም አይኖርምም ብሎ እንደሚያምን የገለጹ ሲሆን በፖለቲከኞች ይጎሰማል ያሉት ጥላቻ እና ግጭት አባባሽ ንግግሮች በፖለቲከኞች መካከል ውይት በማድረግ በመፍታት ለማህበረሰቡ ዘላቂ እፎይታ መስጠት ይገባልም በማለት ምልከታቸውን አጋርተውናል፡፡

የአማራ ክልላዊ መንግስት ይህንኑን ለሰሞነኛው ግጭት ምክኒያት ያለውን የጥር 13 ቀን 2015 ዓ.ም የቅዳሜ ከሰኣቱን ጥቃት በስም ያልጠቀሷቸው “ፀረ ሰላም ኃይሎች” ያሏቸው በኤፍራታና ግድም ወረዳ ጀውሃ ቀበሌ በሚገኘው የአማራ ልዩ ኃይል ፖሊስ እና በፌደራል ፖሊስ አባላቶቻችን ላይ የተፈጸመው ጥቃት ነው በማለት ገልጾታል፡፡

ክልሉ በመግለጫው እነዚሁ ታጣቂዎች የሰሜን ሸዋ ዞን እና የኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን አዋሳኝ ወረዳዎች በሚገኙ ቀበሌዎች ላይ ንጹሃን ላይ አነጣጥረው ጥቃት በመፈፀም በሰው ሕይወት እና ንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ማድረሳቸውንም አመልክቷል፡፡ ክልሉ በመግለጫው አክሎም በተለይም በኤፍራታ ግድም፣ አጣየ፣ ሰንበቴ፤ ጀውሃ እና በሸዋሮቢት ከተማ አቅራቢያ በሚገኙ ቀበሌዎች ጥቃቶች የብሔር መልክ ያለው እንዲመስል ጥረት ተደርጓል በማለት፤ ሕጋዊ፣ የተጠና እና የማያዳግም እርምጃ በመውሰድ መንግሥት በሕግ የተጣለበትን ግዴታውን ይወጣልም ብሏል፡፡

ስዩም ጌቱ 

ኂሩት መለሰ

ታምራት ዲንሳ