1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በማንዴላ የሙት ዓመት የማስጠንቀቅያ ደወል

ዓርብ፣ ኅዳር 26 2007

የደቡብ አፍሪቃዉ የነፃነት ታጋይና የሰላም ኖቤል ተሸላሚ ኔልሰን ማንዴላ ልክ በዛሬዋ ቀን የዛሬ ዓመት ነበር ላይመለሱ ይህችን ዓለም የተሰናበቷት። በአንደኛ የሙት ዓመታቸዉ ዛሪ ታድያ የሀገሪቱ ነዋሪ ከዳር እስከ ዳር በቩቩዜላ ጡሩምባ፤ የፖሊስ እና የቀይ መስቀል ጡሩምባን በማስጮኽ ለስድስት ደቂቃ አስተጋብቶላቸዋል፤ አስቦአቸዋልም።

https://p.dw.com/p/1DzjB
Nelson Mandela Statue enthüllt
ምስል Reuters

ውዲህም ይህ የተስተጋባ ጩኸት የደቡብ አፍሪቃ የዲሞክራሲ ርምጃ አስጊ ደረጃ ላይ መሆኑን ለማመላከት መቀስቀሻ መሆኑ ነዉ የተመለከተዉ። የዶይቼ ቬለዉ ክላዉስ ሽቴከር፤ የደቡብ አፍሪቃዉ የነፃነት ታጋይ የኔልሰን ማንዴላን የሙት ዓመት በማስመልከት የዘገበዉን አዜብ ታደሰ እንዲህ አሰባስባ ታቀርበዋለች።

ሶስት ደቂቃ ከሰባት ሰከንድ ቩቩዜላ ጡሩምባ፤ የፖሊስ እና የቀይ መስቀል መለያ የሆነዉ ልዩ ጡሩምባ፤ ደወል በሀገሪቱ ከጫፍ እስከ ጫፍ ተስተጋብተዋል፤ ከዝያም ለሶስት ደቂቃ ረጭ ያለ ፀጥታም ሰፍኖ ነበር፤ ደቡብ አፍሪቃዉያን አንጋፋዉን የፀረ-አፓርታይድ ታጋይ እና የመጀመሪያዉን የሃገሪቱን ጥቁር ፕሬዝዳት የኔልሰን ማንዴላን የሙት ዓመት ሲያስቡ ዛሬ። ይህ ሶስት ደቂቃ ከሰባት ሰከንድ በሙሉ የጡሩምባ ድምፅ የተስተጋባበትና፤ ሶስት ደቂቃ ረጭ ያለ ፀጥታ የሰፈነበት ሥርዓት ፤ ማንዴላ 67 ዓመት ሙሉ ለሃገራቸዉ ለደቡብ አፍሪቃ ነፃነት እና ዲሞክራሲ ያገለገሉበትን ግዜ ለማሰብም እንደሆነ ነዉ የተመለከተዉ። ከኔልሰን ማንዴላ በጎ አድራጎት ድርጅት፤ ለድርጅቱ መስራች ለኔልሰን ማንዴላ ይህ ዓይነቱ የማስታወሻ ሥርዓት መከናወኑ ታድያ ያልተለመደ ነበር። ግን ለበርካታ ደቡብ አፍሪቃዉያን ይህ የጩኸት ማስታወሻ ጥሪ፤ በሃገሪቱ ነፃ ምርጫ ከተደረገ ከ20 ዓመት በኋላ በጉዞ ላይ ተደናቅፎ የቆመዉ የሀገሪቱ የዲሞክራሲ ጉዞ ዳግም እንዲያንሰራራ እና ትክክለኛ መንገዱን ይዞ እንዲጓዝ የተደረገ እንደ ማስጠንቀቅያ ደወል መሆኑ ነዉ የተመለከተዉ፤
የደቡብ አፍሪቃዉ ፓርላማ በቅርቡ ያሳየዉ አንድ ጽልመታዊ አሻራ አንድ ወር እንኳ አልሞላዉም። የኢኮኖሚ ነፃነት ታጋዮች ፓርቲ በአህፅሮቱ «EFF» የተሰኘዉ የደቡብ አፍሪቃ መንግስት ተቃዋሚ ፓርቲ አባል እና የህዝብ ተወካዮች አባል፤ ንዋንማካዊትል ማሻባላ፤ የሀገሪቱን ፕሪዚዳንት ዙማን «ሌባ» ፤ «ወንጀለኛ» ሲሉ በአደባባይ ፓርላማ ዉስጥ መስደባቸዉ ይታወቃል። ይህን ተከትሎ በፓርላማዉ ሥርዓት በመጥፋቱ እና ጋጠወጥነት በመንገሡ፤ አንድ የገዥዉ መንግሥት ፓርቲ ማለት የANC አባል ፀጥታ አስከባሪ ፖሊሶችን ጠርተም ነበር።

የስልክ ጥሪዉን ተከትሎ በከፍተኛ ሁኔታ የታጠቁ ልዩ ኮማንዶዎች ፓርላማዉን በርግደዉ እንደገቡ ግርግሩ ይጦፋል። በግርግሩ አፍንጫዉ የደማ የቆሰለ መኖሩም ትንሽ ቆየት ብሎ ታዉቆ ነበር። ይህ ሁሉ ሲፈፀም ታድያ ፓርላማዉ ዉስጥ ያለዉ ቴሌቭዝን እየተደረገ ያለዉን ሁሉ እየቀረጸ ከነድምፁ ያሳይ ነበር። ታሳፍራላችሁ ! ታሳፍራላችሁ! የሚል ጥሪም እንዲህ ተደምጦአል፤ ታይቷልም
ፖሊስ ፓርላማ ዉስጥ ዘልቆ እንዲገባ ስልክ ትደዉላላችሁ- አስነዋሪ !ሲሉ የገዥዉ መንግሥት ተቃዋሚ ፓርቲ አባላት በጋራ ጥሪያቸዉን በጩኸት ማሰማታቸዉ ቀጥለዉ ነበር። ይህ ሁኔታ በመከሰቱ የመንግሥት ተቃዋሚዎች « በሀገሪቱ ሕገ-መንግሥት ላይ ትልቅ ቀዉስ ተከስቷል» ሲሉም ተደምጠዋል። ታዋቂዉ የማኅበረሰብ ጉዳይ ተቆርቋሪ ላዉሶን ናይዶ በበኩላቸዉ ይህ ዓይነቱ ተግባር የአፍሪቃዉ አባት ኔልሰን ማንዴላ ቢኖሩ ኖሮ የማይታሰብ ጉዳይ ነበር ሲሉ ተናግረዋል ፤

« እንዲህ ዓይነቱ ተግባር ዲሞክራሲያዊ ሥርዓትን በምታራምደዉ በኛ ሀገር እናያለን ብለን አልገመትንም። በአንድ መስቀለኛ መንገድ ላይ ነዉ የምንገኘዉ። ጫናዉ ያለዉ ፓርላማዉ ላይ ብቻ ሳይሆን ማህበረሰቡ በሚገኝበት ተቋም ዉስጥም ነዉ»
ደቡብ አፍሪቃ መሪ ያስፈልኛል እያለች ያለችዉ፤ በፕሬዚዳንት ደረጃ ብቻ ሳይሆን በሀገሪቱ ዉስጥ በሁሉም ዘርፍ በሚገኙ የመሪነት ቦታዎች ላይ ሁሉ መሆኑን ላዉሶን ናይዶ ተናግረዋል። እንደ ናይዶ መሪዎች በአቅድ እና በሕገ-መንግስት የሚያራምዱ፤ ተቋማትን የሚያረጋጉና ማኅበረሰቡን በተገቢዉ የሚመሩና የሚያስተዳድሩ መሆን አለባቸዉ። ክስ የተመሰረባቸዉና ቅጣት የተላለፈባቸዉ የገዥዉ ፓርቲ ፖለቲከኞች ትክክለኛ የፓርቲዉ አባልነት መታወቅያ በኪሳቸዉ ከያዙ በመንግሥት መሥርያ ቤቶች በቀጣይ እንዲያገለግሉ እንደሚፈቀድላቸዉም ተመልክቶአል። በፍጥነት እያደገ ያለዉ የሀገሪቱ ነዋሪዎች ቁጥር፤ ገዥዉ ፓርቲ «ANC» ሥራ አጡን የወጣት ቁጥር ለመቀነስ በየግዜዉ የሚገባዉን ቃል እንዳይጠብቅ እንዳደረገዉም ተዘገብአል። ከዚህ ትይዩ መዋለ ንዋይ አፍሳሾች የሥራ እና የደህንነታቸዉ ሁኔታ እንዲሁም ኤኮኖሚዉ እጅግ እየተበላሸ መምጣቱ ነዉ የተመልከተዉ። « ጆን ሩበርት» በሚል መጠርያ የሚታወቀዉ የደቡብ አፍሪቃ ከፍተኛ መዋለ ንዋይ አፍሳሽ ከጥቂት ጊዜ በፊት ደቡብ አፍሪቃ ወደ ክስረት እየተንሸራተተች ናት ሲል ማስጠንቀቁ ይታወቃል። የጀርመኑ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ፍራንክ ቫልተር ሽታይን ማየር በበኩላቸዉ በኅዳር ወር ደቡብ አፍሪቃን ሲጎበኙ ፖለቲካዊ ቀዉስን መሸሸግ አይቻልም ሲሉ ተናግረዉ ነበር፤

« የአፓርታይድ ስርዓት ከተገረሰሰ ከ 20 ዓመታት በኋላ ዛሬም አንዳንድ የሃገሪቱ መሠረተ ልማቶች በጥያቄ ዉስጥ ናቸዉ ይታያሉ። የገዥዉ ፓርቲ አባላት ራሳቸዉን በግልፅ ማስቀመጥ አለባቸዉ። ,, እርግጥ ነዉ ይህ ዉይይት ደግሞ ምንም አይነት የፖለቲካ ቀዉስን ሳይጭር መልስ ያስገኛል የሚል ተስፋም አለኝ»
በርግጥ የጀርመን መንግሥት በሀገሪቱ ትልቅ ፖለቲካዊ ቀዉስ ይመጣል የሚል እምነት የለዉም። የገዥዉ ፓርቲና ተቃዋሚ ፓርቲዎች በፓርላማ ዉስጥ ብዙ ክርክርና ዉይይትን ማድረግ በመጀመራቸዉ የደቡብ አፍሪቃዉ ዲሞክራሲ ጤናማ የክትባት መርፊን ማግኘት ጀምሮአል ብለዉ የሚያምኑና የሀገሪቱ የዴሞክራሲ ርምጃ አሳሳቢ ደረጃ ላይ ሳይሆን ጤናማ ሁኔታ ላይ ነዉ የሚሉ ጥቂቶች አይደሉም። ኔልሰን ማንዴላ ይህችን ዓለም ትተዉ ከሄዱ ዛሬ ከአንድ ዓመት በኋላ በዚህ ሃሳብ የሚስማሙ ሁሉም ደቡብ አፍሪቃዉያን ባይሆኑም፤ ተስፋን የሰነቁ ግን ሁሉም የሀገሪቱ ነዋሪዎች መሆናቸዉ ተመልክቶአል።

12.2013 DW Liveübertragung Trauerfeier Nelson Mandela Portrait
የደቡብ አፍሪቃዉ ነፃነት ታጋይና የሰላም ኖቤል ተሸላሚ ኔልሰን ማንዴላ በጎርጎረሳዊዉ ኅዳር 5/ 2013 ዓ,ም ከዚህ ዓለም በሙት ተለዩ
Südafrika Kapstadt Protest Partei EFF
የኢኮኖሚ ነፃነት ታጋዮች ተቃዋሚ ፓርቲ በአህፅሮቱ የ «EFF» የአደባባይ ተቃዉሞምስል picture-alliance/dpa/Nic Bothma
Südafrika Parlament in Cape Town Screenshot Chaos
ኬፕታዉን በሚገኘዉ በደቡብ አፍሪቃ ፓርላማ ዉስጥ በቪዲዮ ምስል የተቀረፀዉ ግጭትምስል YouTube

ክላዉስ ሽቴከር / አዜብ ታደሰ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ