1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በሱማሊያ የባለስልጣናቱ ሽኩቻ

ረቡዕ፣ ኅዳር 10 2007

በሱማሊያ ፕሬዚዳንት ሐሳን ሼይክ ሞሐሙድ እና በጠቅላይ ሚንስትር አብዲዋይል ሼይክ አኽመድ መካከል የተፈጠረው ውዝግብ መባባሱ ተነግሯል። ጠቅላይ ሚንስትሩ ያቀረቡትን የሚንስትሮች ምክር ቤት መዋቅር ፕሬዚዳንቱ እንዳልተቀበሉት ተገልጿል።

https://p.dw.com/p/1DpPb
Symbolbild Somalia Abstimmung Wahlen
ምስል imago/Xinhua

እጎአ በ1991 ዓም የያኔው የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ሞሐመድ ዚያድ ባሬ ሀገሪቱን ጥለው ከኮበለሉበት ጊዜ አንስቶ ሶማሊያ የሰከነ አስተዳደር በዘላቂነት መመስረት ተስኗታል። በሶማሊያ የሚመሰረት መንግስት በተደጋጋሚ የባለስልጣናት ሽኩቻ የሚስተዋልበት ነው። ሰሞኑን የሶማሊያ ጠቅላይ ሚንስትር አብዲዋይል ሼይክ አኽመድ የሚንስትሮች ምክር ቤት ላይ ለውጥ በማድረጋቸው ከሱማሊያው ፕሬዚዳንት ሐሳን ሼይክ ሞሐሙድ ጋር መወዛገባቸው ተጠቅሷል። በኹለቱ ባለስልጣናት መካከል የተፈጠረው ውዝግብ መባባሱም ተነግሯል። በሱማሊያ የዶቸቬለ ዘጋቢ መሀመድ ዑመር ሑሴን

የሶማሊያ ጠቅላይ ሚንስትር አብዲዋይል ሼይክ አኽመድ
የሶማሊያ ጠቅላይ ሚንስትር አብዲዋይል ሼይክ አኽመድምስል picture-alliance/AP Photo

«ሶማሊያ ውስጥ የሽግግር መንግስቱ ከተመሰረተበት ጊዜ አንስቶ በፕሬዚዳንት እና ጠቅላይ ሚንስትር መካከል ተደጋጋሚ ግጭቶች ተስተውለዋል። ይኽ ያሁኑ ግጭት የእዛ አንድ አካል ነው።»

ጠቅላይ ሚንስትሩ ለፕሬዚዳንቱ ቅርብ የሆኑትን ሰው ከስልጣናቸው ማንሳታቸውን ፕሬዚዳንቱ እንዳልተቀበሉት፤ ጠቅላይ ሚንስትሩ በበኩላቸው ያን የማድረግ ሥልጣን የእሳቸው መሆኑን በመጥቀሳቸው ውዝግቡ በዋናነት እንደተቀሰቀሰ መሀመድ ዑመር ሑሴን ጠቅሷል።

የአሁኑ ግጭት የተከሰተው ጠቅላይ ሚንስትሩ የሚንስትሮች ምክር ቤትን እንደ አዲስ በማዋቀራቸው ነው። በመዋቅሩ ደግሞ የፕሬዚዳንት ሐሳን ሼይክ ሞሐሙድ ወዳጅ የሆኑት የፍትኅ እና የእኩልነት ሚንስትሩ አብዱልቃድር ሼይክ ከስልጣናቸው እንደሚነሱ ይጠቅሳል።

የሶማሊያ ወታደር መዲና ሞቃዲሾ ውስጥ ሲዘዋወር
የሶማሊያ ወታደር መዲና ሞቃዲሾ ውስጥ ሲዘዋወርምስል Mohamed Abdiwahab/AFP/Getty Images

ጠቅላይ ሚንስትሩ ሶማሊያን መልሶ ለመገንባት ለማድረገው ጥረት ደስተኞች ካልሆናችሁ ስልጣኔን ልለቅ እችላለሁ ሲሉ የሚንስትሮች ምክር ቤት ላይ መዛታቸውን ሮይተርስ ዘግቧል። የሶማሊያ ድረ-ገፆች ሰኞ ዕለት እንደዘገቡት ከሆነ ደግሞ 14 የሚንስትሮች ምክር ቤት አባላት ጠቅላይ ሚንስትር አብዲዋይል ሼይክ አኽመድ ሥልጣናቸውን እንዲለቁ የሚጠይቅ ደብዳቤ ማስገባታቸው ተገልጿል።

በሌላ ዜና በተመድ የሶማሊያ ልዩ ልዑክ ኒኮላስ ኬይ ከምዕራባውያን የአምባሳደሮች ልዑካን ጋር በመሆን የሶማሊያ ጠቅላይ ሚንስትር እና ፕሬዚዳንቱን ለማነጋገር መጣራቸው ተገልጧል። ልዑካኑ «በሶማሊያ የተከሰተው ፖለቲካዊ ቀውስጥ ሌላ ነገር ለማስከተል የሚችል ከባድ አደጋ ነው» ሲሉ መግለጫ ሰጥተዋል።

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ