1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በስፔን ድንበሮች የቀጠለዉ ስደት

ሐሙስ፣ ሰኔ 8 2009

ሲዉታ እና ማሊያ መልክዓ ምድራዊ አቀማመጣቸዉ በሰሜን አፍሪቃ የባህር ዳርቻ አቅራቢያ የሚገኙ እና ከሞሮኮ የሚጎራበቱ የስፓኝ ከተሞች ናቸዉ። አፍሪቃ እና አዉሮጳ ክፍለ ዓለም የሚገናኙባቸዉ ብቸኛ የየብስ መስመሮች በመሆናቸዉ ከሰሃራ በስተደቡብ ከሚገኙ የአፍሪቃ ሃገራት በሺዎች የሚቆጠሩ ተሰዳጆች በየዓመቱ ወደእነዚህ ከተሞች ይመጣሉ።

https://p.dw.com/p/2ei5e
Spanien Melilla Flüchtlinge
ምስል picture-alliance/AP Photo/S. Palacios

Melilla migrants - MP3-Stereo

 ምንም እንኳን ሞሮኮ በዚህ አካባቢ ጥብቅ የድንበር ቁጥጥር ብታደርግም በርካታ ተሰዳጆች አጥሩን ዘልለዉ ወይም በባህር ዞረዉት ይሻገራሉ። በዚህ ጊዜም ፖለቲካ ሚና ይኖረዋል ይላል በስፍራዉ ተገኝቶ ሁኔታዉን የተመለከተዉ  የዶቼ ቬለዉ ጋይ ሄድግኮ።

በሰሜናዊ ሞሮኮ ራቅ ብላ በምትገኘዉ ቤኒ አንሳር ከተማ ዉስጥ ነኝ። እንቅስቃሴ የበዛባት ከተማ ናት። እዚህ ሆኜ ከድንበር አጥሩ ባሻገር በመቶ ሜትሮች ርቀት ላይ የምትገኘዉን የስፔኗን የድንበር ከተማ ማሊያን በቅርብ ርቀት አያታለሁ። እዚህ አፍሪቃ ምድር ላይ ነኝ፤ ከማዶ ደግሞ አዉሮጳ ነዉ። በሺዎች የሚቆጠሩ የሞሮኮ እና ስፔን ዜጎች በተለይ ለመሸጥ እና እና ለመግዛት በየዕለቱ ድንበሩን ሲያቋርጡ ይዉላሉ። ሆኖም ለሌሎች ግን ከሞሮኮ ወደ ስፔን መሻገር በጣም አዳጋች ነዉ።

መሻገሩ የተሳካላቸዉ የአዲስ ሕይወት መጀመሪያ ነዉ ብለዉ በማመን ይፈነጥዛሉ። እነዚህ ከሰሃራ በስተደቡብ የመጡ አፍሪቃዉያን ሲዉታ መዝለቅ የተሳካላቸዉ ባለፈዉ የካቲት ወር ነበር።

«ድንበሩን ተሻግረናል፤ ሆኖም እጅግ በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ዉስጥ ነዉ ያለፍነዉ። በእነዚያ አደጋዎች ዉስጥ ማለፍ በመቻላችን ፈጣሪን ተመስገን እንላለን፤ አሁን ያለነዉ የስፔን ከተማ በሆነችዉ ሲዉታ ነዉ።»

Spanien Marokko | Flüchtlinge in der Enklave Ceuta
አጥሩን አልፈዉ ስፔን የገቡ አፍሪቃዉያን ተሰዳጆችምስል picture-alliance/AP Photo/J. Moron

በሺዎች የሚቆጠሩ ተሰዳጆች ባለፈዉ የካቲት ወር ብቻ በሦስት ቀናት ጊዜ ዉስጥ አጥሩን እያለፉ ሲዉታ ገብተዋል። በጎርጎሪዮሳዊዉ 2016 ዓመተ ምህረትም እንዲሁ በርከት ያሉ ተሰዳጆች ተሻግረዋል። በርካቶች ሞሮኮ የድንበር ቁጥጥሯን ያላላችዉ አወዛጋቢ በሆነዉ በምዕራብ ሰሃራ ግዛቷ ጉዳይ የአዉሮጳ የፍትህ ፍርድ ቤት በወሰዉ ዉሳኔ በመበሳጨቷ ነዉ ብለዉ ያምናሉ። ራሞን ካራስኮ ማሊያ የሚገኘዉ የስፔን ሲቪል የድንበር ጥበቃ ባልደረባ ናቸዉ። ይህ እዉነት ለመሆኑ አይጠራጠሩም።

«ከስፔን ጋር ማንኛዉንም ነገር ለማድረግ ስትፈልግ ሞሮኮ ገንዘብ ይመስል ስደትን ትጠቀማለት። የዓሣ ማስገርም ሆነ የግብርና ጉዳይ ስምምነት ሲቀርብ፤ ጫና ለማሳደር ከተለመደዉ እጅግ የበለጠ ቁጥር ያላቸዉ ስደተኞች መምጣት ይጀምራሉ። »

ማሊያ በሚገኘዉ ጊዜያዊ የስደተኞች መጠለያ ማዕከል አሁን የምሳ ሰዓት ነዉ። ወደማሊያ መግባት የቻሉ ተሰዳጆች ወደዚህ ነዉ የሚወሰዱት። ምግብ እና ልብስ ይሰጣቸዋል፤ እናም ወደስፔን ማዕከላዊ ግዛት እስኪወሰዱ ድረስ እዚሁ ለበርካታ ወራት ይቆያሉ። 20 ዓመቱ አላሳን ባሪ አዉሮጳ ለመግባት አልሞ የትዉልድ ሀገሩን ሴራሊዮን ትቶ የተሰደደ ወጣት ነዉ።m ማሊያ ከገባ ሦስት ወር ሆነዉ። ስፔን ስለሚኖረዉ የወደፊት እጣ ፈንታ ምን ያህል እርግጠኛ ይሆን?

«ዕድሉን ካገኘሁ የወደፊት ሕይወቴን ለማሳካት እመኛለሁ። ወደፊት አንቱ የተባልኩ ሰዉ ለመሆን እፈልጋለሁ። ለወደፊት በዕድሉ መጠቀም የተሳካለት ሰዉ መሆን እመኛለሁ።»

ለመሆኑ ወደማሊያ እንዴት ገባ?

Spanien Enklave Melilla Flüchtlinge am Zaun
ረዝሙን የድንበር ላይ የሽቦ አጥር ለመሻገርምስል AFP/Getty Images/B.d. Avellaneda

«አጥሩን ዘልዬ ነዉ፤ ግን ቀላይ አይደለም። በጣም አስቸጋሪ ነዉ። በጣም በጣም አስቸጋሪ። ዕድሉ ቢያጋጥመኝ ወንድሜን እና ጓደኞቼን እንዳይሞክሩት እነግራቸዉ ነበር። በጣም አስቸጋሪ ነዉ። »

አላሳን ባሪ ወደስፔን ለመግባት ሙከራ ሲያደርግ የመጀመሪያዉ አይደለም። ሦስት ጊዜ ታግሎ በአራተኛዉ ነዉ የተሳካለት። ለዚያም ዕድለኛ ነኝ ይላል። እንዲያም ሆኖ እሱም ሆነ ሌሎች ተሰዳጆች  ወደ ስፔን ማሊያ እና ሲዉታ ከተሞች እንዲሻገሩ ዕድል ስለከፈተላቸዉ በአዉሮጳ ኅብረት እና ሞሮኮ መካከል በቅርቡ ስለተፈጠረዉ ዉዝግብ የሚያዉቁት ነገር የለም። ምንም እንኳን የስፔን የድንበር ከተሞች ጥበቃ ጥብቅ ቢሆንም ከአጥሩ ባሻገር ያለዉ የተሻለ የወደፊት ሕይወት ተስፋ ተሰዳጆች አሁንም አጥሩን ዘልለዉም ይሁን በዙሪያዉ አቋርጠዉ ወደዚያ ማለፋቸዉ የማይቀር ይመስላል።

ሸዋዬ ለገሠ/ ጋይ ሄድግኮ

አዜብ ታደሰ