1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል
ትምህርትአፍሪቃ

በአማራ ክልል ውዝግብ ያስነሳዉ የተማሪዎች ውጤት

ቅዳሜ፣ መጋቢት 10 2014

በአማራ ክልል የ12ኛ ክፍል ውጤት አሁንም እያወዛገበ ነው። ዝቅተኛ ውጤት ያመጡ አንዳንድ ተማሪዎች ዉጤታቸውን ሲያስመረምሩ ከፍተኛ ሆኖ እየተገኘ ነው። አንድ ተማሪ ብቻ ያለፈባቸው ትምህርት ቤቶች ጭምር እንደሚገኙም ተነግሯል። ክልሉ ከሰላማዊ አካባቢዎች ጋር እኩል መታየቱ በተማሪዎችና በወላጆች ዘንድ ቅሬታ እየፈጠረ እንደሆነ ተመልክቷል።

https://p.dw.com/p/48jGs
Äthiopien Amhara-Region Bildungszentrum
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

ውዝግብ የተነሳበት የ12ኛ ክፍል ዉጤት መፍትሔ አላገኘም

በአማራ ክልል የ12ኛ ክፍል ውጤት አሁንም እያወዛገበ ነው፣ ዝቅተኛ ውጤት ያመጡ አንዳንድ ተማሪዎች ዉጤታቸውን ሲያስመረምሩ ከፍተኛ ሆኖ እየተገኘ ነው፣ አንድ ብቻ ተማሪ ያለፈባቸው ትምህርት ቤቶች ይገኛሉ ተብሏል፣ በምስራቅ አማራ ከነበረው ጦርነት ጋር ተያይዞ የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ከሌሎች በሰላም አካባቢዎች ከተማሩት ጋር እኩል መሆኑ በተማሪዎችና በወላጆች ዘንድ ቅሬታ እየፈጠረ እንደሆነ ተመልክቷል፣ የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ የታዩ አንዳንድ ችግሮችን ለመረም ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር እየሰራሁ ነው ብሏል፣ ስለጉዳዩ ከትምህርት ሚኒስቴር ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት ያደረግነው ሙከራ አልተሳካም፡፡

 የዚህ ዓመት የአማራ ክልል የ12ኛ ክፍል ተማሪዎች ውጤት በሁለት መልኩ እያወዛገበ ነው፣ አንደኛው በምስራቅ አማራ በጦርነት ውስጥ የነበሩ ተማሪዎች በሰላም አካባቢ ሲማሩ ከነበሩት ጋር እኩል የዩኒቨርሲቲ መግቢያ መቆረጡ ትክክል አይደለም የሚል ሲሆን፣ ሌላው ደግሞ ፈተናው ባግባቡ ባለመታረሙ የሚጠበቁ ተማሪዎች ዝቅተኛ ውጤት አምጥተዋል የሚል ሲሆን በማስረጃዎች ያብራራሉ፡፡

በምስራቅ ጎጃም አበርሀ ወአፅበሀ በተባለ ትምህርት ቤት ፈተናውን ወስዶ 162 እንዳመጣ ተነግሮት ሲመረመር ግን ውጤት 647 ሆኖ የተገኘው አማኑኤል ጸሓይ አንዱ ነው፣ ውጤቱ እስካሁን ባለው መረጃ በክልሉ ከፍተኛው ነው ተብሏል፡፡

አንዳንድ ትምህርት ቤቶች አንድ ብቻ ተማሪ ያለፈባቸው እንዳሉ የነገሩን አንድ የደብረማርቆስ ነዋሪ ችግሩ ሌላ ቀውስ ሊፈጥር እንደሚችል አስጠንቅቀዋል፡፡

የወልዲያ መሰናዶ ትምህርት ቤት ተማሪ በጦርነት ውስጥ ቆይተን ከሌሎቹ እኩል መታየቱ ትክክል እንዳልሆነ ነው ያመለከተው፣ ወላጆችም ተመሳሳይ ቅሬታ አቅርበዋል

የምስራቅ ጎጃም ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ስለሺ ተመስገን የፈተና ውጤቱ ብዙ ችግሮች ያለበትና ብዙ ቅሬታዎች እየቀረቡ ለክልል ትምህርት ቢሮና  ለትምህርት  ሚኒስቴር ማመልከታቸውን ተናግረዋል፡፡

በምስራቅ አማራ በጦርነት ውስጥ የበሩ ተማሪዎችም የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ውጤታቸው ከሌሎች ጋር መታየት አልነበረበትም ባይ ናቸው፡፡

በአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ የፈተናዎች ጉዳይ ባለሙያ አቶኃይሉ ታምር ችግሮች ሊኖሩ እንደሚችሉ ጠቁመው ከሚመለከተው ጋር አካል ጋር በመወያየት ይፈታል ብለዋል፡፡

ከትምህርት ሚኒስቴር ተጨማሪ ማብራሪያ ለማግኘት ያደረግሁት ተደጋጋሚ ጥረት ለጊዜው አልተሳካም፡፡

ዓለምነው መኮንን

ታምራት ዲንሳ