1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በአዲስ አበባ 741 ያለሥራ የታጠሩ ቦታዎች

ረቡዕ፣ ጥር 17 2009

በአዲስ አበባ ከተማ  ለበርካታ አመታት ያለ ግንባታ ታጥረዉ የተቀመጡ  በርካታ የሊዝ ቦታወች  መኖራቸዉን አንድ ጥናት ይፋ አደረገ።  መሬቶቹ በቀጣይ ለመንግስት ገቢ ሊሆኑ እንደሚችሉ  የአዲስ አበባ መሬት አስተዳደር  ቢሮ  አስታዉቋል። በጥናቱ  741  ያለ ሥራ ለዓመታት የተቀመጡ የሊዝ ቦታወች ተለይተዋል ተብሏል።

https://p.dw.com/p/2WM0L
Äthiopien Addis Abeba Müll
ምስል DW/Y. Geberegiabeher

mmt Addis Ababa City Administration found 741 building sites idle . - MP3-Stereo

ከ 4 ሚሊዮን ህዝብ  በላይ መኖሪያ እንደሆነች የሚነገርላት  አዲስ አበባ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሻቀበ ከመጣዉ የነዋሪወቿ ቁጥር ጋር የሚጣጣም የመኖሪያ ቤትና ቦታ አለመኖር በችግርነት ሲጠቀሱ ይሰማል።  የዚህ ችግር ባለቤት በሆነችዉ አዲስ አበባ  ታዲያ ለዓመታት ታጥረዉ ያለስራ የተቀመጡ  በርካታ ቦታወች  በነዋሪወች ዘንድ አነጋጋሪ ሆኖ ቆይቷል። 

 ይህንን ችግር በመገንዘብ ይመስላል ሰሙኑን የአዲስ  አበባ መሬት አስተዳደር አንድ ጥናት ይፋ አድርጓል። በአዲስ አበባ ከተማ ግንባታ ሳይካሄድባቸዉ ለበርካታ ዓመታት ታጥረዉ የተቀመጡ ቦታወች መበራከት  አሳሳቢ እየሆነ በመምጣቱና በህዝቡ ዘንድም ቅሬታ እያሳደረ  በመምጣቱ የተነሳ  የአዲስ አበባ መሬት አስተዳደር  የዳሰሳ ጥናት ማካሄዱን የቢሮዉ  የኮሚኒኬሽን ደጋፊ የስራ ሂደት ሀላፊ አቶ ንጉሱ ተሾመ ለዶቸቬለ ገልጸዋል።

በጥናቱ መሰረትም 741 የሊዝ ቦታወች ለአመታት ታጥረዉ የተቀመጡ ሲሆን  ከእነዚህ ዉስጥም በርካቶቹ  ምንም ግንባታ ያልተጀመረባቸዉ መሆናቸዉን ጥናቱ አመልክቷል።

በመሆኑም የችግሩን አሳሳቢነት በመገንዘብ አፋጣኝ መፍትሄ ለመስጠት ጥናቱ ያግዛል ሲሉ ሀላፊዉ ተናግረዋል።

በሊዝ የተሸጡ ቦታወች  ወደ ስራ እንዲገቡ የሚያስገድድ አሰራር እያለና የመሬት አስተዳደርም ቢሆን  የከተማዋ መሬት እንዲለማ ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ ያለ አግባብ ታጥረዉ የተቀመጡ ሲገኙም እርምጃ የመዉሰድ  ሃለፊነት እያለዉ በመሃል አዲስ አበባና በከተማዋ የማስፋፊያ አካባቢወች የሚገኙ  በሊዝ ለባለሀብቶች የተሸጡና ያለ ስራ የተቀመጡ ቦታወች ለምን እስካሁን በቸልታ ታለፉ ብለን ላነሳንላቸዉ ጥያቄ መመሪያዉና አሰራሩ ቢፈቅድም  በተጨባጭ ግን  ክፍተት ነበረ  ሲሉ አቶ ንጉሱ ገልጸዋል።

ከአሁን ቀደም በመሬት አስተዳደር ዘርፍ በርካታ ችግሮች እንደነበሩ የገለጹት ሀለፊዉ የመኖሪያ ቤትና ቦታ ከፍኛ ችግር በሆነባት አድስ አበባ እነዚህ ቦታወች ያለ ስራ ታጥረዉ መቆየታቸዉ  መሬቱን እንደሚያስተዳድር አካል ቢሮዉ ከፍተኛ የሆነ ቁጭት እንደተሰማዉ ሀላፊዉ ገልጸዋል።በመሆኑም  ከዚህ  በኋላ በመሬት ዘርፍ የተንሰራፋዉን ችግር ለመፍታት ቢሮዉ አስፈላጊዉን ክትትል በማድረግ ያለ አገልግሎት የተቀመጡ ቦታወች ለመንግስት ገቢ ሊሆኑ እንደሚችሉ አቶ ንጉሱ አብራርተዋል።

የተሃድሶ አንድ አካል ነዉ የተባለዉ ይሄዉ የጥናት ሰነድ የአዲስ አበባ የመሬት አስተዳደርና ለሙስናና ብልሹ አሰራር የተጋለጠና የመሬት ዘርፍ አገልግሎት አሰጣጡም ቢሆን ችግር ያlለበት መሆኑን አመልክቷል።በመሆኑም ስር የሰደደ ችግር አለባቸዉ የተባሉ አመራርና ሰራተኞች ላይ ርምጃ መዉሰድ መጀመሩን ከቢሮዉ የተገኘ መረጃ ያመለክታል።

ፀሐይ ጫኔ

አዜብ ታደሰ