1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በአፍጋኒስታን፣ የጀርመን ኮማንዶ ጦር ተግባር፣ ዳግም ያስነሣው ክርክር ፣

ዓርብ፣ ታኅሣሥ 2 2002

የጀርመን የመከላከያ ሚንስትር ካርል ቴዎዶር ሱ ጉተንበርግ፣ አከራካሪ የሆነውን በኩንዱስ አቅራቢያ የተፈጸመን የአየር ጥቃት የሚያጣራ፣ በፓርላማ ከተወከሉ ፓርቲዎች ተውጣጣ የቃል አቀባዮች ኮሚቴ በመምራት፣

https://p.dw.com/p/L0Ep
በሰሜን አፍጋኒስታን ፣ ኩንዱስ አቅራቢያ ባለፈው ነሐሴ ወር ማለቂያ ላይ በአየር የተደበደቡ ሁለት ቦቴዎች፣ በተሠነዘረው ጥቃት፣ 142 ያህል ሰዎች ተገድለዋል።ምስል AP

አፍጋኒስታን የገቡ ሲሆን፣ የኮሚቴው ምርመራ፣ በዚያ የሚገኙትን ወታደሮች ለፍርድ ይቅርቡ እንዳይል አስጠንቅቀዋል። ሶሺያል ዴሞክራቶች፣ የአረንጓዴው ፓርቲና የግራ ፈለግ ተከታይ ፓርቲዎች ተወካዮች፣ የመከላከያው ሠራዊት (ቡንደስቬር) ልዩ ኮማንዶ ጦር፣ በአፍጋኒስታኑ የአየር ድብደባ፣ ተሳትፎው እስከምን ድርስ እንደነበረ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት፣ (ቡንደስታኽ) ግልጽ ማብራሪያ ሊቀርብለት ይገባል ብለዋል። ነሐሴ 29 ቀን 2001 ዓ ም፣ በሰሜን አፍጋኒስታን በተካሄደው የአየር ድብደባ፣ 142 ያህል ሰዎች መገደላቸው ታውቋል።

አዲሱ የጀርመን መከላከያ ሚንስትር ካርል ቴዎዶር ሱ ጉተንበርግ ፣ የመሥሪያ ቤታቸው የመረጃ አያያዝ እንዲሻሻልና ውጣ-ውረድ እንዲወገድ ጽኑ ፍላጎታቸው መሆኑን አስታውቀዋል። ከአንድ ሳምንት በፊት፣ በምክር ቤት ባሰሙት ንግግርም፣ በኩንዱስ አፍጋኒስታን የተፈጸመው የአየር ጉዳይ ድብደባ እንዲጣራ እንደሚፈልጉና ከህዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባላት ጋር እንደሚተባበሩ መግለጻቸው ይታወሳል።

«ክቡራትና ክቡራን ባልደረቦቼ፣ በኩንዱስ ከተፈጸመው ድርጊት አኳያና በአጠቃላይ በአፍጋኒስታን ሠራዊታችን ስላለው ሥልጣን፣ ለፓርላማው በተቻለ ሁሉ በግልጽ ለማሳወቅ፣ ለመርማሪ ኮሚቴው ጭምር፣ ለቁጥጥር የሚያመች ሁኔታ እንዲፈጠር ለማድረግ ቃል ገብቻለሁ። የተፈጸመው ድርጊትም ሆነ ጉዳዩ እንዲጣራም ፍላጎቴ ነው»

የህዝብ እንደራሴዎቹ፣ የአየር ድብደባውን በተመለከተ ፣ የትኛው ኀላፊ፣ መቼ፣ ምን ከጉዳዩ ጋር ግንኙነት ያለው ምን ዓይነት መረጃ እንደነበረውና እንዳለው ማወቅ ይሻሉ።

የቀድሞው የመከላከያ ሚንስትር ፍራንትዝ ዮሰፍ ዩንግ፣ ከሚንስትርነት ሥልጣናቸው የወረዱ ሲሆን፣ ራሳቸው አዲሱ የመከላከያ ሚንስትር ጉተንበርግ፣ ጥቅምት 27 ቀን 2002 ዓ ም፣ የነሐሴው ድብደባ በወታደራዊ ግምገማ መሠረት ፣ ተመጣጣኝ እርምጃ ነበረ ማለታቸው የሚታውስ ሲሆን፣ ኅዳር 24 ቀን፣ በምክር ቤት ባሰሙት ንግግር ደግሞ፣ የመጀመሪያውን ቃላቸውን በማጠፍ፣ የተወሰደው እርምጃም ሆነ የአየር ድብደባው በወታደራዊ ስሌት ተመጣጣኝ እንዳልነበረ አስረድተዋል።

«አሁን ሚዛናዊነት ባለው ዐይን ሲታይ፣ ሁሉም በግልጽ ሲመረመር፣ ( ለእኔም ያልቀረቡልኝ ሰነዶች ነበሩና)፣ ያኔ የተፈጸመው ድርጊት፣ ለወታደራዊ እርምጃ የሚመጥን አልነበረም። »

ይኸው የሚንስትሩ አባባል፣ Stern በተሰኘው መጽሔት አመለካከት ፍጹም የተብራራ አይደለም። የመከላከያ ሚንስትሩ፣ ጥቅምት 27 ቀን ባሰሙት ንግግር ላይ፣ «የተወሰደው እርምጃ ከወታደራዊ ግምገማ አኳያ ተመጣጣኝ ነበረ» ቢሉም፣ በዚያኑ ዕለት ዓለም አቀፉ ቀይ መስቀል ማኅበር ያቀረበውን ዘገባ አንብበው እንደነበረ፣ የመከላከያ ሚንስቴሩ ዜና ምንጮች ለጀርመን ዜና አገልግሎት ድርጅት (DPA)ማስረዳታቸው ተደርሶበታል። የጀርመን የመከላከያ ሚንስቴር ቃል አቀባይ Steffen Moritz እንዳረጋገጡት ጉተንበርግ የቀይ መስቀልን ዘገባ ከመመልከታቸውም፣ ስለዚህ ጉዳይ በይፋ ሲናገሩ ተደምጠዋል።

ቀይ መስቀል እንዳብራራው፣ 74 ሲቭሎች፣ ህጻናት ጭምር ነበሩ በነሐሴው የአየር ድብደባ የተገደሉት። እስቴፈን ሞሪትዝ---

«በዚህ መሠረት፣ በዘገባው የሠፈረውን ጉዳይ በተለይም ስለሲቭል ሰለባዎች ማወቅ ብቻ ሳይሆን፣ መገምገማቸውም አልቀረም። ይህ ምንጊዜም ግልጽ ጉዳይ ነው። ይሁንና በ 24 ሰዓት ውስጥ፣ የተመለከቱት ዘገባ እንዳላዩት እንዳልሰሙት ዓይነት ጉዳይ ሆነ።»

ጉተንበርህን የሚነቅፉት ወገኞች አዲስ ጉድም አገኘን እያሉ ነው። Bild የተባለው ጋዜጣ፣ ከጀርመን የመከላከያ ሠራዊት (ቡንደስቬር) ምንጮች ያገኘሁት ነው ብሎ፣ ልዩው ኮማንዶ የጦር ግብረ ኃይል፣ በአየር ድብደባው እርምጃ ፣ እጁ አለበት ሲል ጽፏል። በፓርላማው የመከላከያ ጉዳይ ኮሚቴ ባልደርባ የሆኑት፣ የግራ ፈለግ ተከታዩ ፓርቲ ቃል አቀባይ ቮልፍጋንግ ጌርከ ፣ መከላከያ ሚንስትሩ እምነት የሚጣልባቸው አይደሉም ባይ ናቸው።

«ድርጊቶች የመከላከያ ሚንስትሩን ንግግር ይጻረራሉ። አንድም እርሳቸው፣ የጀርመን ልዩ ጦር፣ ኮሎኔል ክላይን በመከሩበትና በመሩት መሠረት ፣ በኩንዱስ ድብደባ መሳተፉን አላወቁም፣ ይህን ካላወቁ ደግሞ ለሥራው ብቁ አይደሉም፣ ስለድርጊቱ አውቀው ከሆነ ደግሞ ለፓርላማው ዋሽተዋል ማለት ነው። መዋሸት ደግሞ እምነትን አያሳድርም።»

ገርከ፣ በ BILD ጋዜጣ የተጠቀሰው መረጃ ሐቀኛነቱ ከተረጋገጠ፣ በአጠቃላይ የኩንዱሱ ወታደራዊ ተልእኮ በአዲስ መልክ መመርመር ይኖርበታል ነው የሚሉት። ምርመራው አመክንዮ ባለው መልክ፣ ክርክሩም በሠከነ አአምሮ ተካሂዶ እልባት ሊያገኝ እንደሚገባው ነው ያስገነዘቡት።

ሀይነር ኪዝል/ተክሌ የኋላ/አርያም ተክሌ