1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በኢራቁ ጦርነት የጀርመን ሚና

ዓርብ፣ ነሐሴ 9 2006

ኢራቅ ውስጥ ለአክራሪዎቹ የሱኒ ታጣቂ ቡድን ኃይሎች ጥቃት የተጋለጡትን ሰሜን ኢራቅ ውስጥ በጭንቅ ላይ የሚገኙትን ስደተኞች ለመታደግ እርዳታ ማቅረቡ ተገቢ መሆኑን የጀርመን መንግሥት ተስማምቶበታል ።

https://p.dw.com/p/1Cuzd
Deutsche Hilfe für Irak 15.08.2014
ምስል Reuters

የጀርመን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየር በኢራቅ በፍጥነት በመለዋወጥ ላይ ያለውን ሁኔታ ከግምት ውስጥ በማስገባት መንግሥታቸው በፖለቲካውም ሆነ በዓለም ዓቀፍ ህግ የሚቻለውን የመጨረሻ አማራጭ እንደሚወስድ አስታውቀዋል ። ሆኖም ገደቡ የት ድረስ እንደሆነ ግልፅ አይደለም ። የጀርመን መከላከያ ሠራዊት ወደ ኢራቅ መዝመት ፈፅሞ የማይታሰብ በመሆኑ በመንግሥት በኩል ጉዳዩ ለውይይት ይቀርባል ተብሎ የሚጠበቅ ጉዳይ አይደለም ።በዚህ ወቅት ላይ ውጊያ ለሚካሄድበት ኢራቅ የጦር መሣሪያ ማቅረብም በጀርመን መንግሥት እቅድ ውስጥ የተያዘ አይደለም ። በአሁኑ ጊዜ መንግሥት ዓለም ዓቀፍ ህግ በሚፈቅደው ገደብ መሠረት ሰብዓዊ እርዳታ ከማቅረብ ባለፈ ምን ሊያደርግ እንደሚችል እየመከረ መሆኑን የመንግሥት ቃል አቀባይ ትናንት አስታውቀዋል ።

Verteidigungsministerin von der Leyen im Verteidigungsausschuss
ምስል picture-alliance/dpa

ጀርመን በአሁኑ ጊዜ ከጦር መሣሪያና ጥይት በስተቀር የሌሎች ወታደራዊ ቁሳቁሶችን አቅርቦት እያስተባበረች ነው ። የጀርመን መከላከያ ሚኒስትር ዑርዙላ ፎን ዴር ላየን ጀርመን በአሁኑ ጊዜ በተጨባጭ ሁኔታ ወታደራዊ ቁሳቁሶች ለኢራቅ ቶሎ የሚደርሱበትን ሁኔታ እያመቻቸች መሆኑን ተናግረዋል ።

Symbolbild Waffen Waffenhandel Waffenlieferung Rüstung Rüstungsexport
ምስል picture-alliance/dpa

«በአሁኑ ጊዜ በአሁኑ ቅፅበት ማድረግ የሚቻለንን ለማከናውን በጥድፊያ ላይ ነን ብርድ ልብስ ድንኳኖች የጥይት መከላከያ ሰደርያ የብረት ቆብ የመሳሰሉትን ማቅረብ ይቻላል ። ሁለተኛ እንዴት አድርገን ይህን እርዳታ እናደርሳለን የሚለው ጥያቄ ነው ። በአካባቢው አየር የበበረራ መብት ጥያቄ አስተማማኝ አውሮፕላን ማረፊያ ለአውሮፕላኖችም አስተማማኝ ጥበቃ እነዚህ ተጨባጭ የሆኑ ጉዳዮች ግልፅ የሆነ ምላሽ ማግኘት ይኖርባቸዋል ። ይህ ሁሉ በአጣዳፊ እየተመከረበትና መላ እንዲገኝለትም ጥረት እየተደረገ ነው ። እርዳታውን በፍጥነት ለማድረስ ሁኔታዎች ተመቻችተዋል ።»ዩናይትድ ስቴትስ የኩርዶቹን የፔሽሜርጋ ሚሊሽያዎች ስትደግፍ ቆይታለች ። ካለፈው ሳምንት አንስቶ ሚሊሽያዎቹ የአክራሪ ሱኒ ሚሊሽያዎችን የሚዋጉባቸውን የጦር መሣሪያዎችና ጥይቶች አስታጥቃቸዋለች ። ፈረንሳይም ለኩርዶች የጦር መሣሪያ እንደምታቀርብ አስታውቃለች ። ሆኖም ጀርመን ቀውሱ ወደተከሰተበት አካባቢ ወታደራዊ ቁሳቁሶችን ማጓጓዝ ይፈቀድላታል ወይ የሚለው አጠያያቂ ሆኗል ።ውሳኔው ፖለቲካዊ ነው የሚሆነው ። የጀርመን መራኂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ባለፈው ዓመት ጀርመን የሶሪያውን መሪ የበሽር አልአሳድን ኃይሎች ይወጉ የነበሩትን ለዘብተኛዎቹን የሶሪያ ተቃዋሚዎች ትደግፍ እንደሆነ በተጠየቁበት ወቅት ’‘እስካሁን ባለው አሠራር በመርህ ደረጃ ጀርመን ግጭት ወደተከሰተባቸው አካባቢዎች የጦር መሣሪያዎችን አትልክም‘‘ሲሉ ነበር የመለሱት ።ይህ መርህም እጎአ በ2000 ጀርመንን ይመራ የነበረው የሶሻል ዲሞክራቶቹና የአረንጓዴዎቹ ጥምር መንግሥት ባፀደቀው በፌደራል መንግሥቱ የጦር መሣሪያ የውጭ ንግድ ደንብ መሠረት የሚሰራበት ሲሆን አሁን ጀርመንን የሚያስተዳድረው የእህትማማቾቹ የክርስቲያን ዲሞክራትና የክርስቲያን ሶሻል ህብረት ፓርቲዎችና የሶሻል ዲሞክራቶች ፓርቲ ጥምር መንግሥትም የተቀበለው መርህ ነው ። ሆኖም የጦር መሣሪያ ሽያጭን በሚመለከተው ደንብ ላይ የተለየ አንቀፅ አለ ጦር መሣሪያ መሸጭም ሆነ ማቅረብን የሚፈቅድ።ይሄምበተለይ የጀርመንን የውጭም ሆነ የፀጥታ ፖለቲካ መርህ በተመለከተ እጅግ አስፈላጊ ሆኖ በሚገኝበት ጊዜ የተለየ ፈቃድ ይሰጣል ።ሆኖም የጀርመን መንግሥት ቃል አቀባይ ሽቴፋን ዛይበርት በሰጡት መግለጫ በተለይ በኢራቅ መንግሥታቸው በደፈናው ማድረግ የሚችለውን እንደሚያደርግ ነው የተናገሩት «እንዲቀርብ የሚደረገው እርዳታ በዚያ ቦታ ተፈላጊ የሆነው የተጠየቀው ነው ።እኛ ተባባሪዎቹ እርዳታ የሚያሻቸው ወገኖች በቦታው ከአሸባሪው ቡድን ጋር በመፋለም ላይ መሆናቸውን ነው የምንገነዘበው። እናም እኛ ማድረግ የምንችለው አቅማችን የሚፈቅደውን ነው ።»

Symbolbild Munition Waffenlieferungen
ምስል picture-alliance/dpa

የጀርመን ፖለቲከኞች ጀርመን የኢራቅ ኩርዶችን የጦር መሣሪያ ታስታጥቅ አታስታጥቅ የሚለው የጀርመን ፖለቲከኞች ሲያከራክር ቆይቷል ። መሣሪያ መሰጡትን የሚደግፉ የሚቃወሙም ፖለቲከኞች አሉ ። የጀርመን መንግሥት ግን ጀርመን ወደ ኢራቅ ጦር መሳሪያ መላክ የማያስፈልጋት ዋነኛ ምክንያት አላት ይላል ። የጀርመን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ የኩርድ ወታደሮች ከዩናይትድ ስቴትስና ከሩስያ የጦር መሣሪያ እንደሚያገኙና ወታደሮቹም አነዚህኑ በቅጡ የሚያውቋቸውን የጦር መሣሪያዎች ቢጠቀሙ ነው የሚሻለው ብለዋል ። የጀርመን የመከላከያ ሚኒስትር ዑርዙላ ፎን ዴር ላይንም ለኢራቅ ጦር መሣሪያ ከማቅረብ ውጭ ያሉት አማራጮች ብቻ ተግባራዊ ለማድረግ መታቀዱን ነው ያስረዱት

«እንደሚመስለኝ የጦር መሣሪያ ጥያቄ ብለን በማንሳት ነገሩን አካረን ወይም ማገነን እይኖርብንም ። ይሄ በጣም ተፈላጊ ነው ። እርግጥ ነው በዛ እርዳታ የሚያስፈልጋቸውን የስደተኞች ሁኔታ አይተናል ። እናም መከላከያ እንደሚያስፈልጋቸው እናውቃለን ያን በማድረግ ጦር መሣሪያ የሚሰጡትን የሌሎቹን ወገኖች እዳ እናቃልላለን የኛ ተግባር ይህ ነው ።»

ጀርመን ለሰሜናዊ ኢራቅ ወታደራዊ ቁሳቁሶችን ማቅረብ አለማቅረቧና በምን ያህል መጠንም እንደምታቀርብ በይፋ የተወሰነ ነገር የለም ። ሆኖም ጀርመን የሚያስፈልጉትን አቅርቦቶች ለይቶ ለማወቅና በማን በኩል ሊላኩ እንደሚችሉ ከአውሮፓ አጋሮቿ ከዩናይትድ ስቴትስና ከኢራቅ እንዲሁም ከኩርድ ራስ ገዝ አስተዳደር ጋር እየመከረች ነው ።

ኂሩት መለሰ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ