በኢትዮጽያ የወፍ ዘራሹን የቡና ዘር ጥበቃ
ማክሰኞ፣ መስከረም 28 2000በኢትዮጽያ ብቻ የሚገኘዉ በጥራቱ አንደኛ የሆነዉ ወፍ ዘራሹ ቡና የሚበቅልበትን ቦታ በአለም አቀፍ ደረጃ እንዴት ጥበቃ ሊያገኝ ይችላል የሚለዉ ሌላዉ የአዉደ ጥናቱ ርዕስ እንደሆነ በመቱ የሚካሄደዉን መረሃ ግብር ያስተባበሩት ዶክተር ጋትዝቫይለር ፍራንስ በተለይ ለዶቸ ቬለ በሰጡት ቃለ ምልልስ ገልጸዋል። የፊደራል ጀርመን የተፈጥሮ ጥበቃ ባለስልጣን በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጽያ የወፍ ዘራሽ ቡና የሚበቅልበት ስፍራ በተባበሩት መንግስታት የትምህርት የሳይንስ እና የባህል ድርጅት ማለት የUNESCO ጥበቃ ሊደረግለት ይገባዋል ሲል በመግለጫዉ አስፍሮአል። የቦን ዩንቨርስቲ የልማት ምርምር ማእከል ከኢትዮጽያዉያን የቡና ምርምር አዋቂዎች ጋር በመተባበር በኢትዮጽያ የቡና ልማት እና ጥበቃ ላይ ሲሰራ አመታትን አስቆጥሮአል።
ስለ ቡና ጥናት የሚያካሂዱ ኢትዮጽያዉያን ከጀርመን የተፈጥሮ ጥበቃ ባለስልጣን ቢሮ ጋር በመተባበር በተለይ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጽያ የሚገኘዉን የቡና ደን ለመጠበቅ እና በጥንቃቄ ለመጠቀም በመስራት ላይ ይገኛሉ። ሌላዉ የረጅም ግዜ እቅድ ደግሞ ይህ ቡና የሚበቅልበት አካባቢ ልዩ አዕዋት የሚበቅልበት ቦታ መሆኑ እንዲታወቅ እና ልዩ ጥበቃ እንዲደረግለት ነዉ ሲሉ ዶክተር ጋትዝቫይለር ፍራንስ ገልጸዋል በመቀጠል በመቱ የተጀመረዉ አዉደ ጥናት የወፍ ዘራሹ ቡና የሚበቅልበትን የመሪት አቀማመጥ የተፈጥሮ ቅያስ ለማወቅም እንዲያስችል እና ልዩ ክልል እና ጥበቃ ለመስጠት ቀለል ያለ ስራን ለማመቻቸት መሆኑን ጠቁመዋል። በአዉደ ጥናቱ የአካባቢ ተጠሪዎች የቀበሌ ተወካዮችን የመስተዳድሩ ዋና ተጠሪ ባለስልጣናትን እንዲሁም በአካባቢዉ የሚገኙ የገበሪ ተወካዮች ይገኙበታል።
አዉደ ጥናቱ የፊደራል ጀርመን የተፈጥሮ ጥበቃ ባለስልጣናትን ስለሚያካትት በእንጊሊዘኛ ቋንቋ ቢሰጥም ቅሉ ከአካባቢዉ ለመጡ በትጉም መልክ በመቅረብ ላይ መሆኑንም ገልጸዋል።
ይህ አይነቱ አዉደ ጥናት ከጀርመናዉያን ባለሞያዎች ጋር በኢትዮጽያ ሲካሄድ ይህ ለሁለተኛ ግዜ ሲሆን የዛሪ አመት ይህ አዉደ ጥናት በሚካሄድበት ወቅት በደቡብ ምእራብ ኢትዮጽያ የሚገኘዉን ልዩ ቡና የሚበቅልበትን ስፍራ እንክብካቤ እንዲደረግለት ሃስብ የመነጨበት አዉደ ጥናትም እንደነበር ተገልጾአል። የኢትዮጽያ የቡናን ምርት በብዛት በመግዛት የምትታወቀዋ ጀርመን በተለይ እዚህ ራድዮ ጣብያችን በሚገኝበት በቦን ከተማ ዪንቨርስቲ ከኢትዮጽያዉያን የቡና አዋቂዎች ጋር በመሆን በኢትዮጽያ የቡና ጥበቃ እና የቡና ዝርያ ከፍተኛ ምርምር ይካሄዳል ትምህርትም ይሰጣል። በመቱ ትናንት የተጀመረዉ ይህ እስከ ፊታችን አርብ የሚዘልቀዉ አዉደ ጥናት ቡና አምራቹ ገበሪ በምርቱ የተመጣጠነ ጥቅም የሚያገኝበትን መንገድ እንደሚጠቁምም ተጠቅሶአል።