1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በሖሮ ጉድሩ ወለጋ 88 ታጣቂዎች ላይ "እርምጃ መወሰዱን" የክልሉ ባለሥልጣን ተናገሩ

ቅዳሜ፣ ኅዳር 4 2014

በኦሮሚያ ክልል ሖሮ ጉድሩ ወለጋ ዞን በዚህ ሳምንት 88 ታጣቂዎች ላይ "እርምጃ መወሰዱን" የክልሉ የኮምዩንኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ኃይሉ አዱኛ ለዶይቼ ቬለ ተናገሩ። ሌሎች 28 የታጣቂ ቡድኑ አባላት መማረካቸውን፤ "ሎጂስቲክስ ሲያቀባብሉ ነበር" የተባሉ 113 ሰዎች እና በታጣቂ ቡድኑ የተደራጁ 67 ሰዎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን አቶ ኃይሉ ገልጸዋል

https://p.dw.com/p/42xR7
Karte Äthiopien Ethnien EN

በኦሮሚያ ክልል ሖሮ ጉድሩ ወለጋ ዞን በዚህ ሳምንት 88 ታጣቂዎች ላይ "እርምጃ መወሰዱን" የክልሉ ባለሥልጣን ተናገሩ

በሰሜን ኢትዮጵያ የተስፋፋውን ጦርነት ተከትሎ በተለያዩ የአገሪቱ አከባቢዎችም ግጭት፣ አለመረጋጋትና መፈናቀሎች ተስተውሏል። የኦሮሚያ ክልል ከሳምንት በፊት በፌዴራሉ መንግስት የታወጀውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተከትሎ ህብረተሰቡን ከመንግስት ጋር በማቀናጀት የሰላም የፀጥታ እርምጃዎችን እየወሰድኩ ነው ብሏል። የክልሉ የኮምዩንኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ኃይሉ አዱኛ እንዳሉት ታጣቂዎች የሚንቀሳቀሱበት የወለጋ እና ምዕራብ ሸዋ ዞኖች መሰል እርምጃዎች ከተወሰደባቸው ናቸው።  

የኦሮሚያ ክልል ኮሚዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ኃይሉ አዱኛ አክለውም ኦፕሬሽን ያሉት ታጣቂዎች ላይ ያነጣጠረ የመንግስት የተቀናጀ እርምጃ ከአዲስ አበባ በቅርብ ርቀት ላይ የምትገኘውን የምዕራብ ሸዋ ዞን አደዓ በርጋ ወረዳን ጨምሮ ዜጎችን ለማፈናቀል ያሴሩ ባሏቸው ላይ በምስራቅ ወለጋ ዞንም እርምጃ ተወስዷል ብለዋል። 

የጸጥታ ኃይላት በዚህን ወቅት ንጹሃን ዜጎችን እንዳይጎዱ እየተወሰደ ያለው እርምጃ ምን ይሆን የተባሉት ኃላፊው፤ በአዋጁ መሰረት ንጹኃን ሰለባ እንዳይሆኑ የክልሉ መንግስት አጽእኖት ሰጥቷል ሲሉ መልሰዋል።

በሌላ በኩል በአቶ ዳውድ ኢብሳ የሚመራው የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ሰሞኑን በይፋ ማህበራዊ ገጹ ላይ ባወጣው መግለጫ ከባለፈው ሃምሌ ወር ጀምሮ አወጅኩ ያለውን የኦሮሚያ ብሔራዊ የሽግግር መንግስት መሬት ላይ እንዲወርድ ስሰራ ቆይቻለሁ ብሏል።  አክሎም በክልሉ ዞኖችን የሚያስተባብሩ አመራሮችን እንደሚመድብ በማስታወቅ ህብረተሰቡ ከጎናቸው በመሆኑ በአሁን ወቅት በአገሪቱ ውስጥ እየተካሄደ ያለውን ጦርነት እንዲቀለብስ ጠይቋል። የክልሉ ኮሚዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ መንግስታቸው በኦነግ ስም የሚያውቀው በአቶ አራርሶ ቢቂላ የሚመራውን መሆኑን በማሳወቅ መግለጫውም ተግባራዊ የማይሆን ብለውታል።

ስዩም ጌቱ
እሸቴ በቀለ