1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በኦሮሚያ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ፖለቲካ ፓርቲዎች ምሬት

ቅዳሜ፣ ሐምሌ 25 2012

«መንግስት በተለያዩ አከባቢዎች የሚገኙ አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎቻችንን እያሳደደብን ነው» በማለት  በኦሮሚያ ክልል የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ወቀሱ፡፡ የፖለቲካ ድርጅቶቹ «ጽህፈት ቤትን ከመዝጋት ጀምሮ የፖለቲካ አውዱን የሚያጠቡ ተግባራት እየተከናወነ »ነው በሚልም ከሰዋል፡፡

https://p.dw.com/p/3gGR0
Karte Äthiopien Amhara, Tigray, Oromia Englisch

በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ላይ የፖለቲካ ፓርቲዎች ወቀሳ እና የመንግስት ምላሽ

በኦሮሚያ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ፖለቲካ ፓርቲዎች ምሬት

«መንግስት በተለያዩ አከባቢዎች የሚገኙ አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎቻችንን እያሳደደብን ነው» በማለት  በኦሮሚያ ክልል የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ወቀሱ፡፡ የፖለቲካ ድርጅቶቹ «ጽህፈት ቤትን ከመዝጋት ጀምሮ የፖለቲካ አውዱን የሚያጠቡ ተግባራት እየተከናወነ »ነው በሚልም ከሰዋል፡፡

የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግሬስ በተለይም በስድስት ዞኖች ውስጥ ያሉ አስተባባሪዎቹ በመታሰራቸው ጽህፈት ቤቶቻቸውም የእለት ተእለት ስራቸውን መከወን እንዳልተቻላቸው ነው የጠቆመው፡፡ በምስራቅ ወለጋ፣ ሆሮ ጉዱሩ ወለጋ እና ምዕራብ ወለጋ እንዲሁም በምስራቅ ሐረርጌ፣ ምዕራብ አርሲ እና ሰሜን ሸዋ ዞኖች ጽ/ቤቶቹ ከመዘጋቱ ባለፈ የፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች ላይ የማሳደድ ተግባራት መፈጸማቸውን ፓርቲው ለዶይቼ ቬለ ተናግሯል፡፡

የኦፌኮ ሊቀመንበር ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና እንዳሉት «ፓርቲው በ1997ቱ ምርጫ ባሸነፈባቸው አከባቢዎች በተለይ ልዩ ትኩረት የተሰጠው በሚመስል መልኩ አባላቶቻችን ላይ የእስር እና ሌሎች እርምጃዎች እየተወሰዱ ይገኛሉ » ብለዋል፡፡

በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ የሰጡን በፌዴራል ጠቅላይ አቃቤ ህግ የተደራጁና ድንበር ተሻጋሪ ወንጀሎች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ፍቃዱ ጸጋው «መንግስት ተጠርጣሪዎችን በቁጥጥር ስር እያዋለ የሚገኘው ከከተሞች ከንቲባዎች ጀምሮ የገዢውም ሆነ ተፎካካሪ ፓርቲዎች አመራር ሳይለይ መሆኑንና በወንጀል የተጠረጠሩትን ነው» ብለውናል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ከሁለት ቀናት በፊት ከፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ጋር ባደረጉት ውይይት «የገዢ ፓርቲ አባላትና አመራሮችን ጨምሮ የተለያዩ ሰዎች በቁጥጥር ስር የዋሉት በወንጀል መጠርጠራቸውንና በሀገሪቱ የህግ የበላይነትን ለማስከበር ነው» ማለታቸው ይታወሳል፡፡

የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ ህልፈትን ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል በተከሰተው አለመረጋጋት በጠፋው 200 ገደማ የሰው ህይወት እና ከፍተኛ ግምት ላለው የንብረት ውድመት የተጠረጠሩ ከ7000 በላይ ተጠርጣሪዎች በመንግስት በቁጥጥር ስር መዋላቸውም አይዘነጋም፡፡

ስዩም ጌቱ

ታምራት ዲንሳ