1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በውዝግብ የታጀበው የኔታንያሁ የበርሊን ጉብኝት

ሐሙስ፣ ጥቅምት 11 2008

የእስራኤል ጠቅላይ ሚንስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ በሚሊየን የሚቆጠሩ አይሁዶች በናትሲ ዘመን ለመጨፍጨፋቸው የፍልስጥኤም የሃይማኖት አባት ሚና ነበራቸው በሚል ያደረጉት ንግግር የጀርመን ጉብኝታቸውን በውዝግብ የተሞላ አድርጎታል።

https://p.dw.com/p/1GskX
USA Israel Deutschland Kerry mit Netanjahu in Berlin
ምስል Reuters/C. Allegri

[No title]

የጀርመን መዲና በርሊን ውስጥ ከመራሒተ-መንግስት አንጌላ ሜርክል እና ከሌሎች ባለሥልጣናት ጋር ለመነጋገር ሲመጡ በመቶዎች የሚቆጠሩ ፍልስጤማውያን ለተቃውሞ አደባባይ ወጥተው ነበር። ጠቅላይ ሚንሥትሩ አይሁዶች በናትሲ ዘመን እንዲጨፈጨፉ የያኔው የእየሩሳሌሙ ፍልስጤማዊ የሃይማኖት አባት ወይንም ሙፍቲ አስተዋፅዖ አድርገዋል ማለታቸው ከመላው ዓለም ውዝግብ አስነስቶባቸዋል። የጀርመን ጉዞዋቸው እጅግ በውዝግብ የተሞላ ቢሆንም ዛሬ ከጀርመን ባለሥልጣናት ጋር ተነጋግረዋል።

Bundeskanzlerin Merkel trifft Israels Premierminister Netanjahu in Berlin
ምስል Reuters/Bundesregierung/G. Bergmann

በእስራኤል እና ፍልስጤም መካከል የተባባሰዉን ግጭት ለማብረድ የዩናይትድ ስቴትስ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ኬሪ በርሊን ጀርመን ከሚጎበኙት የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁጋር ዛሬ ተገናኝተዉ ተነጋገሩ። ባለፉት ሶስት ሳምንታት ብቻ 50 ፍልስጤማዉያን እና ዘጠኝ እስራኤላዉያን የከፋ በተባለዉ የጎዳና ላይ ጥቃት ተገድለዋል። ኔታንያሁ ቀደም ብለዉ ትናንት ከጀርመን መራሂተ መንግሥት አንጌላ ሜርክል ጋርም በጉዳዩ ላይ ተነጋግረዋል። ኔታንያሁ ከኬሪ በተጨማሪ ከጀርመን የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፍራንክ ቫልተር ሽታይንማየር እና ከአዉሮጳ የዉጭ ጉዳይ ኃላፊ ፌዴሪካ ሞጌሪኒ ጋርም ተወያይተዋል። ሜርክልም ሆኑ ኬሪ በመካከለኛዉ ምሥራቅ ዉጥረት ያነገሰዉ የእስራኤል ፍልስጤም ፍጥጫ እንዲበርድ አሳስበዋል። ጆን ኬሪ ከኔትንያሁ ጋር በበርካታ ጉዳዮች ላይ መነጋገራቸዉን ቢጠቅሱም ከፍልስጤሙ መሪ ማህሙድ አባስ እና ከዮርዳኖሱ ንጉሥ አብደህ ሁለተኛ ጋር በነጥቦቹ ላይ መነጋገር እንደሚኖርባቸዉ አመላክተዋል። በቀጣይ ቀናትም ለዉይይት ሊቀርቡ የሚችሉ አማራጮች ሊኖሩ እንደሚችሉም ጠቁመዋል።
«እነዚህ ወገኖች ብጥብጡን ለማብረድ መሞከር ቢፈልጉ፤ እናም እንደሚሞክሩም አምናለሁ፤ በርከት ያሉ አማራጮች አሉ።»
ሽታይንማየርም በበኩላቸዉ ሁለቱም ወገኖችን አካባቢዉን ለማረጋጋት አስተዋፅኦ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል።
«ሁለታችንም፤ ሁለቱም ወገኖች ፍልስጤማዉያንም ሆኑ እስራኤላዉያን የሚችሉትን በማድረግ ይህን ግጭት እንዲያበርዱ፤ ሁኔታዉን ለማረጋጋት የበኩላቸዉን እንዲያደርጉ እና ግጭቱን ከሚያባብስ ማንኛዉም ተግባር እንዲታቀቡበድጋሚ ጥሪ እናቀርባለን።»

Berlin Bundesaußenminister Steinmeier und John Kerry
ምስል picture-alliance/dpa/M. Kappeler

ይልማ ኃይለ ሚካኤል
ማንተጋፍቶት ስለሺ
አዜብ ታደሰ