በዓለም ላይ ወደ 250 ሺህ ሕፃናት በዉትድርና ተሰማርተዋል
ማክሰኞ፣ የካቲት 5 2011ማስታወቂያ
በአስር ሺሕዎች የሚቆጠሩ ልጆች በተለያዩ የዓለም ክፍሎች በሚካሔዱ ግጭቶች እና ጦርነቶች በውትድርና ተመልምለው ለስቅየት መዳረጋቸውን የተባበሩት መንግሥታት የሕፃናት መርጃ ድርጅት አስታወቀ። ለረዥም አመታት የዘለቁ ግጭቶች በሚገኙባቸው በደቡብ ሱዳን፤ በማዕከላዊ አፍሪቃ ሪፐብሊክ፤ ኮንጎ፤ ሶማሊያ፤ ሶርያ እና የመን ተቀናቃኝ ወገኖች ሕፃናትን በውትድርና መመልመላቸውን እንደቀጠሉ ድርጅቱ ገልጿል። የተባበሩት መንግሥታት የሕፃናት መርጃ ድርጅት እንዳለው ዕድሜያቸው ለትምህርት የደረሰ ወንዶች እና ሴቶች ልጆች በአፍጋኒስታን፣ በማሊ እና በምንያማር ወታደሮች ወይም የታጣቂ ቡድኖች ረዳቶች ለመሆን ተገደዋል። ሕፃናት ወደ ጦርነት አውድማዎች በግዴታ ከመሔዳቸው ባሻገር የታጣቂ ቡድኖች ወታደር መልማይ፣ እንጨት ለቃሚ እና አብሳይ ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉ ተብሏል። ታጣቂዎች ለማግባት የተገደዱ አዳጊ ልጆች መኖራቸውን እና ወንዶችም ሆኑ ሴቶች ሕፃናት ለወሲባዊ ባርነት ተዳርገዋል ሲል ዩኔሴፍ አክሏል። በውትድርና የተመለመሉ ሕፃናት ትክክለኛ ቁጥር ባይታወቅም ድርጅቱ ግን 250,000 እንደሚደርሱ ገምቷል።
እሸቴ በቀለ
አዜብ ታደሰ