1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በድሬደዋ የደንጊ በሽታ ወረርሽኝ ተከሰተ

ቅዳሜ፣ መስከረም 29 2014

በድሬደዋ ከተማ የደንጊ በሽታ ወረርሽኝ መከሰቱን የአስተዳደሩ ጤና ቢሮ ኃላፊ ለዶይቼ ቬለ ተናገሩ። የድሬደዋ አስተዳደር ጤና ቢሮ ኃላፊ ለምለም በዛብህ እንዳሉት ለ87 ናሙናዎች ምርመራ ተደርጎ አራት ሰዎች በደንጊ መያዛቸው ተረጋግጧል። ከመስከረም እስከ ኅዳር ባሉት ወራት በድሬደዋ ቺኩንጉንያ፣ ደንጊ እና ወባ በሽታዎች በወረርሽኝ መልክ ይከሰታሉ

https://p.dw.com/p/41TPj
Äthiopien Lemlem Bezabih
ምስል Messay Teklu/DW

በደሬደዋ የደንጊ በሽታ ወረርሽኝ ተከሰተ

የድሬደዋ አስተደደር ጤና ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ለምለም በዛብህ ለዶይቼ በሰጡት መግለጫ በአስተዳደሩ የደንጊ በሽታ ወረርሽኝ መከሰቱን ተናግረዋል።

ባለፉት አመታት በተመሳሳይ ወቅት የከተማዋን ነዋሪ ከፍተኛ ዋጋ ያስከፈለውን የደንጊ በሽታን ለመከላከል ፍሳሾችን ማፋሰስ እና ማዳረቅ እንደሚገባ ወይዘሮ ለምለም ጠቁመዋል።

የከተማዋ ነዋሪ የሆኑት አቶ ከበደ ካሳ በሽታው በወረረርሽኝ መልክ ይከሰት እንጂ ህብረተሰቡ ዘንድ እና በአንዳንድ አካባቢዎች ለወረርሽኙ መስፋፋት ምቹ ሁኔታዎችን በመከላከል በኩል ችግሮች መኖራቸውን በመጥቀስ የፅዳት ስራ በከፍተኛ ሁኔታ መከናወን አለበት ብለዋል፡።ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪም ህብረተሰቡ አፋጣኝ የመፍትሄ ስራ ካልሰራ ከፍተኛ ጉዳት ሊደርስ ይችላል ብለዋል፡፡

የመስተዳደሩ ጤና ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ለምለም በዋነኛነት በተመሳሳይ በትንኝ የሚተላለፈው የቺኩንጉንያ በሽታ መከሰቱ ባይረጋገጥም የበሽታውን ምልክቶች የሚያሳዩ ታማሚዎች ወደ ህክምና ተቋም አምርተው ህክምና እያገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል። የወባ በሽታንም ሙሉ በሙሉ ለማስቀረት የሚያስችል ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል።

ህብረተሰቡ ላይ የሚታየው መዘናጋት በሽታዎችን ለመከላከል እክል እየፈጠረ መሆኑን ኃላፊዋ ተናግረዋል። በርካታ ሰዎች በደንጊ እና መሰል በሽታዎች ምልክት እየታመሙ መሆናቸው ታውቋል።

መሳይ ተክሉ

እሸቴ በቀለ