1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በጀርመን የሴቶች አኩል የሥራ እድል

ማክሰኞ፣ ኅዳር 17 2006

ጀርመን ውስጥ የሴቶች ደሞዝ በአመዛኙ ከወንዶቹ በአንድ አራተኛ እንደሚያንስ ስታስቲካዊ ጥናቶች ያስረዳሉ ። ሴቶች የሥራ እድል የማያገኙባቸው የሥራ መስኮችም በርካታ ናቸው ።

https://p.dw.com/p/1AP6P
ምስል imago/Sven Simon

የዛሬው አውሮፓና ጀርመን ዝግጅታችን በሁሉም የሥራ መስክ ሴቶች እኩል የሥራ እድል እንዲኖራቸው ለእኩል ሥራም እኩል ክፍያ እንዲሰጣቸው የሚደረጉ ጥረቶችን ይመለከታል ።

በጀርመን ህገ መንግሥት ሴቶችና ወንዶች እኩል መሆናቸው ተደንግጓል ። ይሁንና በአንዳንድ ሥራዎች የሴቶች ቁጥር አናሳ ሲሆን የሚያገኙት ደሞዝም ከወንዶቹ እንደሚያንስ ጥናቶች ያመለክታሉ ። በመካሄድ ላይ ባለው የአዲስ መንግሥት ምሥረታ ድርድር ላይ የሴቶች ቁጥር አናሳ በሆነባቸው የሃላፊነት ቦታዎች ቁጥራቸው እንዲያድግ ትኩረት ተሰጥቶት ስምምነት ላይ ተደርሶበታል ። ተጣምረው መንግሥት ለመመሥረት በድርድር ላይ ያሉት እህትማማቾቹ የክርስቲያን ዲምክራትና ሶሻል ህብረት ፓርቲዎች እንዲሁም ሶሻል ዲሞክራቶች ከዛሬ 3 ዓመት አንስቶ የትላልቅ ኩባንያዎች ተቆጣጣሪ ቦርድ ሴት አባላት ቁጥር ቢያንስ 30 በመቶ እንዲሆን ተስማምተዋል ። ከዚሁ ጋር ትላልቅ ኩባንያዎች በሥራ አስፈፃሚነት ና በከፍተኛ የአስተዳደር ሃላፊነት ቦታዎች የሴቶችን ቁጥር የሚያሳድጉባቸውን እቅዶች በ 2015 ማውጣት ይጠበቅባቸዋል ። እጎአ አቆጣጠር እስከ መስከረም 2013 ድረስ ባለው መረጃ መሠረት ጀርመን ውስጥ የትላልቅ ኩባንያዎች የቦርድ አባላት ሴቶች ቁጥር በመቶኛ ሲሰላ 11.7 በመቶ ብቻ ነው ። ጥናትን መሰረት አድርገው በቀረቡ አሃዛዊ መረጃዎች መሰረት የጀርመን ሴቶች ደሞዝ በተመሳሳይ ደረጃ ካሉ ወንድ ባልደረቦቻቸው ጋር ሲነፃፀር ወደ 22 በመቶ የቀነሰ ነው ።

Bundesfamilienministerin Kristina Schröder wartet vor Aufzug
ምስል dapd

በቅርብ ይፋ የሆነው ጀርመን ውስጥ የደሞዝ ልዩነት ያጤነው ይህ ጥናት ግራ የሚያጋባ መሆኑን ነው አንዳንድ አስተያየት ሰጭዎች የሚናገሩት ። ከወንድ ባልደረቦቻቸው ያነሰ ገቢ ያገኛሉ የሚባሉ ሴቶች ቁጥር በጥናቱ አንድ 4 ተኛ የሚጠጋ መሆኑ ቢገልፅም ይህ ቁጥር አሻሚ ሆኖ ተገኝቷል ። EQUAL PAY INITIATIVE ወይም እኩል የደሞዝ ክፍያ በሚል የሚንቀሳቀሰው ተቋም እንደሚለው ከሆነ ሴቶች ከሞላ ጎደል ወንዶች ከሚያገኙት በሩብ ዝቅ ያለ ደሞዝ ነው የሚከፈላቸው ። ከአሠሪዎች ጋር የቀረበ ግንኙነት እንዳለው የሚነገርለት የጀርመን የኤኮኖሚ ተቋም ደግሞ ልዩነቱ አንድ በመቶ ነው የሚለው ። የትኛው ቁጥር ትክክለኛ ተደርጎ ሊወሰድ እንደሚችል ዶቼቬለ የጠየቃቸው የሰራና ማህበራዊ ጉዳይ ባልደረባ ዩታ አልሜንዲንገ የትኛው ትክክል እንደሚመስል ሲያብራሩ

« እዚህ ላይ ብዙውን ጊዜ ሴቶች ያላቸው የሥራ ልምድ ከወንዶች የተለየ መሆኑን ግምት ውስጥ ማስገባት ይኖርብናል ። ብዙውን ጊዜ ልምዳቸው ከወንዶች ያነሰ ነው ። ብዙውን ጊዜ የሚሰሩትም በአነሰተኛ ኩብናያዎች ውስጥ ነው ። እነዚህ ሴቶችም በሌሎች ቡድኖች ውስጥ ነው የሚመደቡት ። እናም በርርግጥ እነዚህን ሁሉ አጠቃላይ ምክንያቶች መከታተል ያስፈልጋል ። ያ ማለት የምናነፃፅረውም በተመሳሳይ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ሴቶችና ወንዶች ነው ።ከዚያም በሰዓት የሚከፈለውን የደሞዝ መጠን ልዩነት ከሞላ ጎደል በ 2/3ተኛ ዝቅ ልናደርገው ወይንም ልንቀንሰው እንችላለን ። የሚቀረው ሲሶ ማለትም 7 ከመቶው ነው እዚህ ላይ የቤት ወጪ ይዞታን በማስመልከት ተጨማሪ ምክንያቶችንም ሆነ ማብራሪያዎችን ማቅረብ ይቻላል ። »

Frauenquoten-Konzepte in der Diskussion
ምስል Picture-Alliance/dpa

የሥራና የማህበራዊ ጉዳዮች ባለሞያዋ አልሜንዲ እንደሚሉት የተጠቀሰው 22 በመቶ ሴቶች የሚገኙበትን እውነታ ያንፀባርቃል ። አብዛኛዎቹ በትርፍ ሰዓት ሥራ እንደተሰማሩ ፣ በሙያቸው የሚያድጉበትን መንገድ ያልያዙ ፣ እድሜያቸው ሲገፋም እየደኽዩ እንደሚሄዱ ነው አልሜንዲንገ የሚናገሩት ። ይሁንና አሁን በጥምር መንግሥት ምሥረታው ድርድር ላይ ለሴቶችም የተወሰነ ቦታ እንዲሰጥ ስምምነት ላይ የተደረሰው በኩባንያዎች ቦርዶች ውስጥ ብቻ ነው ። በዚህ ስምምነት መሰረት ኩባንያዎች በቦርዶቻቸው ውስጥ የሴት አባላትን ቁጥር የማሳደግ ግዴታ ይገባሉ ። ካረን ሆይማን ቲንክ የተባለው የማስታወቂያ ድርጅት ብቸኛዋ ሴት የቦርድ አባል ናቸው ።

« ብዙ ወንዶች ባሉበት በአንድ ክፍል ውስጥ አንዲት ሴት ብቻ ማየት የተለመደ ነው ። ምናልባት ሌላ የተለየ ሁኔታ ሊኖር ይችላል ። ያማለት ይህ እንደ ቅንጦት ሊታይ ይችላል »

ሆይማን የሴቶች ቁጥር አናሳ በሆነባቸው የሥራ ዘርፎች ሴቶች በህግ በሚደገፍ አሠራር የተወሰኑ ቦታ እንዲያዝላቸው በመደረጉ አይስማሙም ነበር ።

« ቀደም ሲል ለሴቶች ተብሎ የተወሰነ ቁጥር እንዲያዝ መደረጉ አስፈላጊ አይደለም ብዮ ነበር የማስበው ። ምክንያቱም በኔ አስተሳሰብ ሴቶች በአመራር ደረጃ ቦታ መያዛቸው እየተለመደ መምጣት አለበት ብዮ ነበር የማምነው ።

ሆይማን በስራ ላይ ስለሚገጥማጠቸው ሁኔታ ተጠይቀው ሲመልሱ አሰራሩ ሁልጊዜም ፍትሃዊ ሆኖ እንደማያዩት ነው የተናገሩት ።

« እኔ እያወቅኩት ከወንዶች በተለየ አድልዎ ደርሶብኛል የሚል ስሜት የለኝም ። ሆኖም ከጊዜ በኋላ ያመለጠሽ ነገር እንዳለ ትደርሺበት ይሆናል ። »

Bundesrat zu Meldegesetz - 900. Sitzung Bundesrat
ምስል dapd

ጀርመን ውስጥ የሴቶች ቁጥር የሚያንስባቸው የስራ መስኮች የሃላፊነት ቦታዎች ብቻ አይደሉም ። ለምሳሌ ከእሳት አደጋ መከላከያ ባልደረቦች ውስጥ የሴቶች ቁጥር አነስተኛ ነው ። በዚህ ሙያ የተሰማሩ ሴቶች ቁጥር አንድ በመቶ ብቻ ነው ። ታንያ ዲትማር ከነዚህ ሴቶች አንዷናት

« እሳቱ ሁሉንም እኩል ነው የሚያቃጥለው ። በአደጋው የሚጠቁትም እንዲሁ ተመሳሳይ ጉዳት ነው የሚደርስባቸው ። ስለዚህ ሴቶችም ወንዶችም ተመሳሳይ ፈተና መውሰድ ይኖርባቸዋል ።»

ሆኖም ታንያ እንደምትለው በሴቶችና በወንዶች ደሞዝ መካከል ግን ልዩነት የለም ። ሁሉም የመንግሥት ሠራተኞች ናቸው ። አድልዎም አላጋጠማትም ። የምትሰራው ግን በወንዶች ዓለም ውስጥ ነው ። ሥራውም ጠንካራ ሰው ይፈልጋል ።

የሴት ሰራተኞችና ሃላፊዎች መጠን ከወንድ ባልደረቦቻቸው ቁጥርና በአንዳንድ ሥራዎች የሚሰጣቸው አነስተኛ ክፍያ እንዲስተካከል ወይም ተመጣጣኝ እንዲሆን የሚደረገው እንቅስቃሴ ጀርመናውያንን ማነጋገሩ እንደቀጠለ ነው ።

ኂሩት መለሰ

ተክሌ የኋላ

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ