1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

-በጀርመን የተፈጥሮ ባህርዩ የተለወጠ በቆሎ እንዳይዘራና እንዳይሸጥ መከልከሉ

ረቡዕ፣ ሚያዝያ 7 2001

-መተንበይ የሚያስቸግረው የምድር ነውጥ፣ ጀርመን ፣ የተፈጥሮ ባህርዩ በሰው-ሠራሽ መንገድ የተለወጠ በቆሎ ወደፊት ላለመዝራትና ላለመሸጥ መወሰኗ ተገለጠ።

https://p.dw.com/p/HXkS
-በጀርመን የተፈጥሮ ባህርዩ የተለወጠ በቆሎ እንዳይዘራና እንዳይሸጥ መከልከሉ፣ -መተንበይ የሚያስቸግረው የምድር ነውጥ፣
የተፈጥሮ ባህርዩ በሰው ሠራሽ እርምጃ ስለተለወጠ በቆሎ፣ የማስጠንቀቂያ ምልክት፣ምስል picture-alliance/dpa

የግብርና ጉዳይ ሚንስትር ወ/ሮ ኢልዘ አይግነር ትናንት እንዳስታወቁት ፣ እገዳው የሚመለከተው የዩናይትድ ስቴትሱን የሥነ-ህይወትና ቴክኒክ ኩባንያ «ሞንሳንቶ» ያዘጋጀው የበቆሎ ዘር MON 810 በሚል መለያ የታወቀውን ነው።አይግነር በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ይኸው የበቆሎ ዘር ከእንግዲህ በጀርመን የእርሻ ማሳዎች አይዘራም።

O-Ton Aigner

«ማንኛውም ፣ ይህን «ሞንሳንቶ 810» የበቆሎ ዘር ማልማትና መሸጥ አይፈቀድለትም። የጀርመን ፌደራል ክፍላተ-ሀገር ስለዚህ እርምጃ ማብራሪያ የሚሰጣቸው ሲሆን እገዳው እንዲጸና መከታተል ግዴታቸው ይሆናል።

እ ጎ አ ከ 1998 ዓ ም አንስቶ ይኸው የተጠቀሰ የበቆሎ ዓይነት በአውሮፓው ኅብረት፣ ለንግድ እንዲሆን እየተባለ ሲመረት ቆይቷል። የአውሮፓው ኅብረት ይኸው በቆሎ እንዲታገድ ማድረግ የሚችልበት የህግ አንቀጽም ያለው መሆኑ ይታወቃል። ጀርመን የምትከለክለው ለተፈጥሮ አካባቢ ጠንቅ ነው በማለት ነው። (በሰው ጤንነት ላይ ውሎ -አድሮ የሚያስከትለው ሳንክ ይኖር ይሆን!? የሚለው ጥያቄ፣ በዓለም ዙሪያ ምላሽ ያልተገኘለት ሆኖም ፣ አከራካሪ ነጥብ ሆኖ እንደሚገኝ የታወቀ ነው። MON 810 የበቆሎ እሸትን የሚያበላሹ ቢራቢሮዎችን የሚገድል መርዝ የሚያመነጭ ሲሆን፣ የተፈጥሮ አካባቢ ጥበቃ ነክ ድርጅቶች ፣ የአረንጓዴና የግራ ፈለግ ተከታይ ፓርቲዎች «ቢራቢሮዎችን ብቻ ሳይሆን ሌሎች ነፍሳትንም ያጠፋል ፣ አፈሩንም ይበክላል በማለት እንዲታገድ ከጠየቁ፣ ጊዜው ረዘም ብሏል። የባየርን ፌደራል ክፍለ ሀገር የተፈጥሮ ጥበቃ ጉዳይ ሚንስትር ማርኩስ ዞደር፣ በበኩላቸው ባለፈወ ሳምንት ማለቂያ ላይ ፣ ጀረመን ፣ የተፈጥሮ ባህርያቸው የተለወጠ ጥራጥሬዎች የማይዘሩባት አገር ትሆን ዘንድ ማሳሰባቸው ይታወሳል። እገዳው አግባብ የለውም በማለት የሚቃወሙ ወገኖች፣ ምርምር የሚያካሂዱ ተቋማትን ተግባር መግታት ይሆናል ባዮች ናቸው።

በጀርመን ሀገር በያዝነው ወር 3ኛ ሳምንት ላይ ለሚጀመረው በቆሎ የመዝራት እርምጃ፣ 3,600 ሄክታር መሬት፣ በተለይ፣ በምሥራቅ ጀርመን ተዘጋጅቶ በመጠበቅ ላይ መሆኑ የተገለጠ ሲሆን ፤ በምትኩ ምን እንደሚዘራበት አልተጠቀሰም።

ባለፈው ሳምንት ፣ መጋቢት 27 ቀን (እሁድ ሌሊት ለ ሰኞ መጋቢት 28 አጥቢያ) በመሃል ኢጣልያ ፣ በአብሩዞ ክፍለ-ሀገር ያጋጠመው በ Richter መለኪያ 5,8 የደረሰ የምድር ነውጥ ፣ ቁጥራቸው ወደ 300 የሚጠጋ ሰዎች (294) መግደሉና ወደ 58,000 የሚገመቱትንም መጠጊያ አልባ ማስቀረቱ፣ ብዙ ንብረትም ማውደሙ አይዘነጋም። አደጋውን ካደረሰው ብርቱ ነውጥ በኋላ፤ መለስተኛ የሆነ ከ 10ሺ የማያንስ የምድር ንዝረት መመዝገቡን የኢጣልያ የሥነ-ምድር ፊዚክስና የእሳተ ገሞራ ጥናት ፣ ብሔራዊ ተቋም ኀላፊ ኤንዞ፣ ቦሺ አስታውቋል። በአርግጥ ፣ የምድር ነውጥን እንደአየር ጠባይ አስቀድሞ መተንበይ ይቻላል ወይ?በፖትሳዳም የተፈጥሮ አደጋም ሆነ የሥነ-ምድር ማርምር ማዕከል ባልደረባ ጀርመናዊው የምድር ነውጥ ጉዳይ ተመራማሪ፣ Birger-Gottfried Lühr አንዳንድ ምልክቶችን መታዘብ እንደሚቻል ሲያስረዱ፣ በከርሠ-ምድር የሚገኘው የውሃ- ልክ መዋዠቅ፣ የውሃው የሙቀት መጠን መለወጥ፣ የራደን ጋዝ መሠራጨት እነዚህ አንዳንድ ምልክቶች ሲሆኑ፣ በሳቴላይት አማካኝነት የቅርጽ ለውጥን ማወቅ እንደሚቻል ይተነትናሉ።

ተክሌ የኋላ፣

ሸዋዬ ለገሠ፣