1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ቢን ላድን

ሐሙስ፣ ነሐሴ 5 2003

የአልቃዳ መሪ ኦስማ ቢን ላደንን ለመያዝ የነበረዉ የማሳደድ ትግል ከባድ እንደነበር የቀድሞዉ የአሜሪካ ሰላይ ድርጅት CIA ምክትል ተጠሪ ጆን ሜክላፍሊን ለዶቸ ቬለ በሰጡት ቃለ ምልልስ አስታዉቀዋል። ጆን ሜክላፍሊን አሸባሪዎችን ማሳደድ የጀመሩት ከጎርጎረሳዉያኑ 1997 አ.ም ጀምሮ እንደነበር ተጠቅሶአል።

https://p.dw.com/p/RfGU
ምስል DW / AP

1-የመስከረም 1 ,1994 ዓ.ምህረቱን የኒውዮርኩን የአሸባሪዎች ጥቃት አስረኛ አመት በማስመልከት ዶይቸ ቬለ ለቀድሞዉ የአሜሪካ ሰላይ ድርጅት CIA ምክትል ተጠሪ ጆን ሜክላፍሊን ያቀረበላቸዉ የመጀመርያ ጥያቄ፣ በአሜሪካ የስለላ ድርጅት CIA ዉስጥ ከሰላሳ አመት በላይ አገልግለዋል። ለመጀመርያ ግዜ ስለ ኦሳማ ቢን ላደን የሰሙት መቼ ነበር? የሚል ነበር።

ጆን ሜክላፍሊን በመልሳቸዉ« በግሌ ስለ እሱ የሰማሁት በዘጠናዎቹ አመታት አጋማሽ ላይ ነዉ። በግምት እ.ጎ.አ 1996 አ.ም ዉስጥ ቢንላደን ለአልቃይዳ እና ለሌሎች አሸባሪ ቡድኖች ዋነኛ የገንዘብ ምንጭ መሆኑን አዉቀን ነበር። በዚሁ አመት ነበር ቢንላደን ከነበረበት ከሳዉዲ አረብያ ተነስቶ አፍጋኒስታን መኖር የጀመረዉ። እኔ ደግሞ በዚህ ወቅት ለዩኤስ አሜሪካ መንግስት ስለ አሸባሪዎች ሁኔታ ጥናት ላይ ነበርኩ። በጎርጎረሳዉያኑ 1997 አ.ም ኦሳማ ቢንላደን ለአሜሪካ ከባድ ጠላት መሆኑ ታዉቆ ስሙ በጥቁር መዝገብ ላይ ሰፈረ። ከዝያ ነዉ በመጀመርያ እ.ጎ.አ 1998 አ.ም በአሜሪካ ኤንባሲ ላይ ጥቃት የደረሰዉ፣ በመቀጠል እ.ጎ.አ 2000 አ.ም በአሜሪካ የጦር መርከብ ላይ እንዲሁ ጥቃት ተጣለ፥ በመጨረሻም መስከረም አንድ በአሜሪካ የደረሰዉ ከፍተኛዉ የአሸባሪዎች ጥቃት ነዉ»

USA John McLaughlin früherer Vize-Direktor des US-Geheimdienstes CIA
ጆን ሜክላፍሊንምስል AP
Pakistan Terror Haus von Osama bin Laden in Abbottabad
በአቦታባድ ኦሳማ ቢን ላደን የተደበቁበት ቤትምስል dapd

2- በዪናይትድ ስቴትስ ላይ እንዲህ አይነቶቹ ጥቃቶች ከደረሱ በኋላ በርካታ የአሸባሪ ቡድን መሪዎች እና ግለሰቦች በአፍጋኒስታን ቶራ ቦራ ተራራ ላይ ወጥተዉ በመሸሸጋቸዉ ምክንያት በዚሁ ተራራ ላይ ቢላደንን ለማግኘት ትልቅ ፍተሻ ተካሂዶ ነበር። ታድያ ቢንላደን የዝያን ግዜ እንዴት ከዪናይትድ ስቴትስ ወታደሮች ሊመልጥ ቻለ? እርሶስ ስለዚህ ጉዳይ ምን አሉ?

«በዝያን ግዜ ቶራ ቦራ ላይ ተከሶ ስለነበረዉ ነገር አሁንም ቢሆን የተለያዩ ሃሳቦች ናቸዉ የሚንሸራሸሩት» ይላሉ ጆን ሜክላፍሊን በመልሳቸዉ «አንዳንዶቹ የቅርብ ጓደኞቼ የዛን ግዜ ቢንላደንን መያዝ ነበረብን ይላሉ። ሌሎቹ ባንጻሩ መያዝ መቻሉን ይጠራጠራሉ። እንደኔ እንደኔ ደግሞ ቦታዉ በጣም ዉጣ ዉረድ የበዛበት በመሆኑ ቢላደንን ለመያዝ በጣም እንደሚከብደ ነዉ ባይነኝ፣ ካልሆነ ደግሞ እጅግ በርካታ ቁጥር ወታደር ቦታዉ ላይ ያስፈልገናል። በዝያን ግዜ በቦታዉ ላይ የነበሩት የጦር ሰራዊት መሪዎች ምን እንዳሰቡ ባላዉቅም፤ እኔና እና ሌሎች አንዳንዶች በዝያን ግዜ ቢንላደንን መያዝ አለብን ብለን አላሰብንም። ቶራ ቦራ ላይ ቢን ላደንን ለማግኘት በርካታ ወታደሮችን ብናሰማራ እንኳ ቦታዉ ጠመዝማዛ እና አስቸጋሪ በመሆኑ፣ እንዲሁም በዝያን ግዜ በነበረዉ የስለላ ድርጅት መረጃ ሁኔታ ነገሩ ከባድ ይሆን ነበር።»

3 ባለፈዉ አመት ቢንላደን ያለበት ታዉቆ ያለፈዉ ግንቦት ወር ከመገደሉ በፊት ዪናይትድ ስቴትስ በዝያን ግዜ ቶራ ቦራ ተራራ ላይ ቢንላደን ለመያዝ እንድል እንደነበራት አይነት ሁኔታ አለጋጠማትም ነበር? የቀድሞዉ የአሜሪካ ሰላይ ድርጅት CIA ተጠሪ ጆን ሜክላፍሊን በመልሳቸዉ «እንደማስበዉ ከሆነ አላጋጠማትም፣ እ.ጎ.አ ከ2001 እስከ 2011 አ.ም በተለያዩ ቦታዎች ቢንላደን ይኖራል እየተባለ፣ እንዴት እሱን መያዝ እንደሚቻል ይገለጽ ነበር። አንዳንድ ግዜ እንደዉም ከምናገኘዉ ጥቆማ ቢንላደን የሚኖርበትን አካባቢ ትክክለኛ መረጃ እንይዝና በትክክል ያለበትን ቦታ የማናዉቅበት ግዜም ነበር። በጠቆምነዉ አካባቢ ላይ ለብዙ ግዜ እንፈልጋለን እንፈልጋለን አናገኘዉም። በዚህም እሱን የምንፈልገበትን አንዳንድ ቦታዎች ሰረዝን እና ፍለጋዉ በሌላ አካባቢዎች ተጠናክሮ ቢቀጥልም በተለይ እኛ እሱን የሚረዱ የአልቃይዳ መረብ ሁሉ ለመበጣጠስ ትግላችንን አጠናክረን ቀጠልን። በሌላ አነጋገር ቢንላደንን ለማግኘት ፍለጋችንን መቀጠል እንዳለብን ብናዉቅም፣ ዳግመኛ የአሸባሪ ጥቃት እንዳይደርስ የአልቃይዳን መረብ ማዳከም፣ የግንኙነት መስመሩን መስበር የገንዘብ ምንጩን እና ለጋሹን ማጥፋት ነበር አላችን። በዚህ መንገድ ነበር ቢንላደንን ብቸኛ አድርገን ለመያዝ የፈለግነዉ። እናም እንደ እኔ ሁኔታዉ በከፍተኛ ደረጃ ተሳክቶልናል።»

4 በወታደራዊ ትጥቅ ከፍተኛ ቴክንኒክ ያሟላችዉ ዪናይትድ ስቴትስ በተለይም የተሟላ የስለላ መረጃ ምንጭ ያላት አገር እንዴት በአለም ላይ በቀንደኝነት የሚፈጉ አሸባሪዎችን መያዝ ያቅታታል?

«በእኔ በኩል የስለላ ድርጅቶች ተፈላጊን ለማግኘት ትልቅ ችግር አለባቸዉ» ይላሉ ጆን ሜክላፍሊን «እስቲ የቀዝቃዛዉን ጦርነት ግዜ መለስ ብለን እናጢን። በዝያን ግዜ በአለማችን አንድ ትልቅ ነገርን መፈለግ ነበረብን። ይኸዉም የሶቭየት ህብረትን የአቶም ሃይል ማብላልያ፣ የዉቅያኖስ ዉስጥ ለዉስጥ መርከብ እና ቦንብ ጣይ፣ በጀርመን ድንበር ላይ ያለዉን ተንቀሳቃሽ ጦር የመሳሰሉትን። ታድያ ይህ ፍለጋ ከመስከረም አንድ ጀምሮ የተጠናከረዉ አሸባሪን የማሳደድ ተግባር ጋር ሲነጻጸር ያኛዉ በጣም ኢምንት ነገር ነዉ። በሻንጣ ዉስጥ የተደበቀ ቦንብ ወይም በሚሊዮኖች የሚቆጠር ህዝብ በሚኖርበት ከተማ አንድ አሰቫሪን ማግኘት፣ በጣም ይከብዳል።»

5 በአሜሪካዉ ሰላይ ድርጅት CIA መስሪያ ቤት ዉስጥ በተለይ ቢላደንን በተመለከተ ሲሰሩ በርካታ ግዜዎትን አሳልፈዋል። እ.ጎ.አ 2004 አ.ም መጨረሻ መስሪያ ቤቱን ለቀዉ ሲወጡ ምን ተሰማዎት?

«አልቃይዳ በጣም ተዳክሞአል የሚል እምነት ስለነበረኝ ጥሩ ስሜት ነበረኝ» አሉ ጆን ሜክላፍሊን በመቀጠል «አላማችን ዩናይርድ ስቴትስን ከአሸባሪ ጥቃት መከላከል ነዉ፣ ከመስከረም አንድ ጥቃት በኋላም ሌላ አዲስ ጥቃት በአገሪቷ አልደረሰም። በዚህም ዋናዉን አላማችን አሳክተናል ብለን እናምናለን። በሌላ በኩል በኔ ስልጣን ቦታ ያለዉ ማንኛዉም ሰዉ አንድ በጣም የሚፈለግ አሸባሪን ባለመያዙ ይቆጫል።»

6- ባለፈዉ አመት ቢንላደን የሚኖርበትን ፈልጎ የማግኘቱ ጉዳይ ስኬታማ ሆንዋል። እርሶ በአሁኑ ወቅት የአሜሪካ ሰላይ ድርጅት CIA መስሪያ ቤት ባልደረባ ባይሆኑም ዮናይትድ ስቴትስ ቢላደንን ለማግኘት ያደረገችዉን እርምጃ ለመግለጽ የሚያስችል በቂ መረጃን ያገኛሉ?

ጆን ሜክላፍሊን -አጥጋቢ መልስ ለመስጠት ምንም በቂ መረጃ የለንም እኔም የማዉቀዉ ነገር የለም ብል ይሻላል። እዚህ ላይ ብዙ ሁኔታዎች ሚና ሳይጫወቱ አልቀሩም። አንዳንዶቹ ደግሞ በሚስጥር ተይዘዋል። ዋናዉ ለስኬቱ የአመታቶች መረጃ ሳይሆን አልቀረም።»

7 የቀድሞዉ የአሜሪካ ሰላይ ድርጅት CIA ተጠሪ ጆን ሜክላፍሊን በአሜሪካ የዛሪ አስር አመት መስከረም አንድ ቀን የደረሰዉን ጥቃት በሁለት ቃላት ይገልጹታል።

ይኸዉም ይላሉ «ቁጣ እና ቆራጥ ሃሳብ» ብለዉታል «ቁጣዉ የአልቃይዳን የጥቃት ኢላማ ለይተን ባለማወቃችን ነዉ። አልቃይዳ በዝያ አመት በጋ ወራት ዉስጥ አንድ አደጋ እንደሚጥል መረጃ ቢኖረንም ጥቃቱን የት እንደሚጥል አናዉቅም ነበር። ሌላዉ ቆራጥ ሃሳብ ያልኩት፣ እንዲህ አይነቱ ጥቃት እንዳይደገም እና ይህንን ጥቃት የፈጸመዉን ድርጅት ለማጥፋት ቆርጠን መነሳታችን ነዉ።»

ጆን ሜክላፍሊን እ.ጎ.አ ከ2000 አ.ም እስከ 2004 አ.ም የአሜሪካ ሰላይ ድርጅት CIA ምክትል ተጠሪ ሆነዉ አገልግለዋል። ጆን ሜክላፍሊን በአሁኑ ወቅት ዪናይትድ ስቴትስ በሜሪላንድ ክፍለ ግዛት ባልቲሞር ዉስጥ በሚገነዉ ጆንስ ሆፕኪንስ ዪንቨርስቲ በተጋባዥ ፕሮፊሰርነት በማገልገል ላይ ይገኛሉ።

ሚሻኤል ክኒገ

አዜብ ታደሰ