1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ባግቦ በዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት

ሐሙስ፣ ጥር 19 2008

የኮት ዲቩዋር የቀድሞ ፕሬዝደንት ሎሮ ባግቦ በሀገራቸዉ ከምርጫ በኋላ በተፈጠረ ግርግር 3ሺህ ሰዎች ለመገደላቸዉ ተጠያቂ አይደለሁም አሉ።

https://p.dw.com/p/1HlQJ
Elfenbeinküste Präsident Laurent Gbagbo
ምስል picture-alliance/dpa/M. Kooren

[No title]

ዛሬ ዓለም አቀፉ የጦር ወንጀል ተመልካች ፍርድ ቤት የቀረቡት ባግቦ በፈረንሳይ ጣልቃ ገብነት ለዚህ በቅተዋል የሚሉት በመቶዎች የተገመቱ ደጋፊዎችም በበኩላቸዉ ከፍርድ ቤቱ ዉጭ በመሰባሰብ የ70 ዓመቱ የቀድሞዉ የኮት ዲቩዋር ፕሬዝደንት በነፃ እንዲለቀቁ ጠይቀዋል።

«ሚስተር ባግቦ ጥፋተኛ ነዎች ወይንስ አይደሉም።»

«አመሰግናለሁ የተከበሩ፤ ጥፋተኛ አይደለሁም።»

በሰብዓዊነት ላይ የተፈፀሙ አራት ክሶች የቀረቡባቸዉ የኮት ዲቩዋር የቀድሞ ፕሬዝደንት ሎሮዉ ባግቦ ለዓለም አቀፉ የጦር ወንጀል ተመልካች ፍርድ ቤት ዳኛ ኩኖ ራርፉሰር ጥፋተኛ እንዳይደሉ እንዲህ ነዉ ዛሬ የገለፁት። እሳቸዉ ብቻ ሳይሆኑ አብሯቸዉ የተከሰሰዉ በወገኖቹ ዘንድ «የጎዳና ላይ ጀነራል» በሚል ቅፅል የሚታወቀዉ የ44 ዓመቱ የወጣቶች ጉዳይ ባለስልጣን ቻርልስ ብለ ጉዲም እንዲሁ በጎርጎሪዮሳዊዉ 2011ዓ,ም ይሰነዝራቸዉ ከነበሩ አደገኛ ንግግሮቹ ጋር በተያያዘ ለቀረበበት የክስ ጭብጥ እዉቅና እንደማይሰጥ ለፍርድ ቤቱ ገልጿል። በወቅቱ ኮት ዲቩዋር ምርጫ ካካሄደች በኋላ በተፈጠረ ዉዝግብ አራት ወራት የዘለቀ የእርስ በርስ ጦርነት አተራምሷታል። ጦርነቱ ያበቃዉ የቀድሞ ቅኝ ገዢዋ ፈረንሳይ ባደረገችዉ ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት አላስን ዋታራን ወደስልጣን መንበር ካወጣች በኋላ ነዉ።

Deen Haag Ble Goude vor Weltstrafgerichtshof ICC
ብለ ጉዉደምስል Reuters/Peter Dejong

የባግቦ የክስ ሂደት በሀገራቸዉም ሆነ በዉጭ በትኩረት ሲጠበቅ ቆይቶ ተጀምሯል። የፍርድ ሂደቱ ከሚካሄድበት ችሎት ፊት ለፊት የተሰባሰቡት በመቶዎች የተገመቱት የባግቦ ደጋፊዎች የፈረንሳይ ጣልቃ ገብነት ሰለባ ናቸዉ ያሏቸዉ የቀድሞ ፕሬዝደንት በነፃ እንዲለቀቁ ጠይቀዋል። የፍርድ ቤቱ ጠቅላይ አቃቢተ ሕግ ፋቱ ቤንሱዳ በበኩላቸዉ ሁለቱም ተከሳሾች በተጠየቁባቸዉን ወንጀሎች የሚያስረዱ እጅግ በርካታ መረጃዎችን ጽሕፈት ቤታቸዉ እንደሰበሰበ ተናግረዋል። የኮት ዲቩዋር ህዝብ ግንባር ቃል አቀባይ ቦባከር ኮኔ ግን ምን ማስረጃ አስለማይገኝ ባግቦ በነፃ ይለቀቃሉ ባይ ናቸዉ።

«ለቀረቡት ክሶች መረጃዎች አይገኙም ብለን እናስባለን። በዚህም ምክንያት ፍትህ በመጨረሻ እንደሚገኝ እና ፕሬዝደንት ባግቦ ወደሀገራቸዉ በነፃ እንደሚመለሱ እንጠብቃለን። ይህንንም ትዕግስት በማጣት ነዉ የምንጠባበቀዉ።»

ለኮኔ ዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት የኢምፔሪያሊስቶች ችሎት ነዉ። ለዚህም ማሳያ የሚሉት በዴሞክራሲያዊ መንገድ በተካሄደ ምርጫ ባግቦ አሸንፈዉ በሌሎች ጣልቃ ገብነት ስልጣናቸዉን ተቀምተዉ ለእስር ተዳርገዋል ነዉ። በአንድ በኩል እሳቸዉ ለሚሉት ማጠናከሪያ የሚሆነዉ እስካሁን የባግቦ ታማኝ ወታደሮች ብቻ የፈፀሙት በደል እና ወንጀል ብቻ ነዉ ሲመረመር የታየዉ። አሁን ስልጣን ላይ የወጡት የዋታራ ወታደሮችም ጥይት ተኩሰዉ የሰዉ ህይወት ቀጥፈዋል። ይህንንም የባግቦ ወገን ያልሆኑ የዓይን ምስክሮች ያረጋግጣሉ። ያም ሆኖ ስልጣን ላይ የሚገኙትን ፕሬዝደንት ጉዳይ መመርመር አልተደፈረም። ይህ አካሄድ ብሄራዊ እርቀ ሰላም ማስፈን መቻሉን በግብርና ሥራ የተሰማሩት ኢቲኖ ሞሮ ይጠራጠራሉ።

Elfenbeinküste Unterstützung für Laurent Gbagbo in Haag Boubacar Kone
ቡባከር ኮኔምስል DW/K. Gänsler

«ወደእርቀ ሰላም ከመምጣት በፊት በአግባብ እና በሀቀኝነት መሥራት ያስፈልጋል። አለበለዚያ ዉጤት አያመጣም። ለዚህም ነዉ ከቤተሰብ መጀመር ያለበት። በዚያም ቢሆን ደግሞ ብዙ መነጋገር ያስፈልጋል። እዚያ እርቀ ሰላም ማምጣት ካልተቻለ፤ በየትም ቢሆን ሊሳካ አይችልም።»

እንዲያም ሆኖ ይህ የፍርድ ሂደት 23 ሚሊየን ህዝብ ላላት ሀገር ኮት ዲቩዋር አንድ ነገር ነዉ። የወቅቱ ቀዉስ ሰለባዎች የሆኑት 726 ሰዎች በአንድ ጠበቃ ተወክለዋል። ለአፍሪቃ ኅብረት ጉባኤ አዲስ አበባ የሚገኙት የሀገሪቱ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር አልበርት ቶይኩሴ ማብሪ የፍርድ ሂደቱ በከፍተኛ ደረጃ ሲጠበቅ የቆየ ነዉ ማለታቸዉ ተሰምቷል። የአፍሪቃ ኅብረት በተቃራኒዉ ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤቱን አፍሪቃዉያን ብቻ የሚዳኙበት ፍርድ ቤት ነዉ በሚል አጥብቆ ይተቻል። ለሁሉም የኮት ዲቩዋርን የምርጫ ወቅት ዉዝግብ በምን መልኩ መርምሮ ፍርድ እንደሚሰጥ ጉዳዩ ለዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት መፈተኛ ነዉ ተብሏል።

ሸዋዬ ለገሠ

አርያም ተክሌ