1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ባግዳድ፤በአይሲስ የቦምብ ጥቃት 120 ሰዎች ተገደሉ

ቅዳሜ፣ ሐምሌ 11 2007

በምስራቃዊ ኢራቅ ራሱን እስላማዊ መንግስት ብሎ የሚጠራው ታጣቂ ቡድን በጣለው የቦምብ ጥቃት ቢያንስ 120 ሰዎች መገደላቸውንና 130 የሚሆኑ ደግሞ መቁሰላቸው ተገለፀ።

https://p.dw.com/p/1G14g
Irak Selbstmordanschlag nahe Bagdad
ምስል A. Al-Rubaye/AFP/Getty Images

ከኢራቅ ዋና ከተማ 35 ኪ.ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘውና የሺዓ እስልምና ተከታዮች በሚኖሩባት የካን ባኒ ሳድ ከተማ በመኪና ላይ የተጫነው ቦምብ የረመዳን ቅዱስ ወርን መጠናቀቅ በማስመልከት የተሰበሰቡ ሰዎችን ዒላማ ማድረጉን የአገሪቱ ፖሊስ አስታውቋል። ከሟቾች መካከል ሴት እና ህጻናት ይገኙበታል።
ራሱን እስላማዊ መንግስት በማለት የሚጠራው አክራሪ ቡድን ለጥቃቱ ሃላፊነቱን ወስዷል። የዒድ በዓልን ለማክበር ወደ ገበያ የወጡ ሰዎች በዘንቢሎቻቸው በፍንዳታው የተበታተኑ የህጻናት አካላትን ሲለቃቅሙ መታየታቸውን ሮይተርስ ዘግቧል። አደጋው ታጣቂ ቡድኑ በኢራቅ ከፈጸማቸው ሁሉ የከፋ ነው ተብሎለታል።ከጥቃቱ በኋላ የአገሪቱ ፖሊስ የጸጥታ ቁጥጥሩን አጥብቋል።
በተያያዘ ዜና አይሲስ የአካባቢውን ባለስልጣናትና የስራ ባልደረቦቹን ይሰልላል ያለውን አንድ ጋዜጠኛ በሞስል ከተማ መግደሉን አዣንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል። ጃላል አል አባዲ የተባለው ጋዜጠኛ ከቤቱ ተወስዶ በአክራሪ ቡድኑ ችሎት ሞት ከተበየነበት በኋላ ባለፈው ረቡዕ በጥይት ተደብድቦ ተገድሏል። በኢራቅና ሶርያ በእስልምና ህግጋት የሚተዳደር ግዛት መስርቻለሁ የሚለው አክራሪ ቡድን የሁለት ልጆች አባት የሆነውን ጃላል አል አባዲን ጨምሮ በርካታ ጋዜጠኞች መግደሉ ይነገራል።

Irak Selbstmordanschlag nahe Bagdad
ምስል APTN

እሸቴ በቀለ

ልደት አበበ