1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ቦኮሃራም ያገታቸው ልጃገረዶች የመለቀቅ ተስፋ

ቅዳሜ፣ ጥቅምት 8 2007

የናይጄሪያ መንግሥት እና ቦኮ ሃራም ተኩስ ለማቆም መስማማታቸው ይፋ ከሆነ በኋላ ቡድኑ ለ6 ወራት አግቷቸው የቆዩ ልጃገረዶች በሚመጡት ቀናት ነፃ ይሆናሉ ተብሎ ይገመታል።

https://p.dw.com/p/1DYCR
Nigeria Boko Haram soll offenbar entführte Mädchen freilassen
ምስል Reuters/A. Sotunde

አክራሪው እስላማዊ ታጣቂ ኃይል ቦኮ ሃራም ለግማሽ ዓመት ያህል አግቶ ያቆያቸውን 200 በላይ ሴት ተማሪዎችን ሊፈታ እንደሚችል ተጠቀሰ። ተማሪዎቹ የሚፈቱት የፊታችን ማክሰኞ መሆኑንም አቡጃ የሚገኘው የናይጄሪያ ፕሬዚዳንት /ቤት አስታውቋል። ይህ የሆነው የናይጄሪያ መንግሥት እና ቦኮ ሃራም ተኩስ ለማቆም መስማማታቸው ከተነገረ አንድ ቀን በኋላ ነው ከስምምነቱ መካከል ተማሪዎቹን ከዕገታ ማስለቀቅ ዋነኛው እንደሆነ ተጠቅሷል። ቦኮሃራም ተማሪዎቹን ወደ ጎረቤት ሀገር ቻድ በመውሰድ ለቻድ ፕሬዚዳንት እንደሚያስረክብ ይፋ አድርጓል። የቻዱ ፕሬዚዳንት ጄኔራል ኢድሪስ ዴቢ የናይጄሪያ መንግሥት እና ቦኮሃራም የተኩስ አቁም ስምምነት እንዲያደርጉ ሚና ከተጫወቱ ባለሥልጣናት ዋነኛው እንደሆኑ ይጠቀሳል። ቦኮሃራም ተማሪዎቹን ለመልቀቅ የተስማማበት ነጥብ ግን ይፋ አልተደረገም። አክራሪው እስላማዊ ታጣቂ ኃይል ቦኮ ሃራም አግቶ ያቆያቸው ተማሪዎቹን ለመፍታት በምትኩ በናይጀሪያ መንግሥት የታሰሩበት ታጣቂዎቹ እንዲፈቱ በተደጋጋሚ ሲጠይቅ እንደነበር ይታወሳል። በቦኮሃራም የሽብር ጥቃት በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች መሞታቸው ይታወቃል።

ዘግይቶ በደረሰን ዜና መሠረት ደግሞ ተጠርጣሪ የቦኮሃራም ታጣቂዎች ዛሬ የናይጀሪያ መንደሮች ውስጥ ጥቃት አድርሰው በርካታ ሰዎች መግደላቸው ይፋ ሆኗል።

ልደት አበበ

ማንተጋፍቶት ስለሺ