1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ቬኑዙዌላ፥ የፕሬዝዳት ሑጎ ሻቬዝ ድልና ተቃዋሚዎቻቸዉ

ማክሰኞ፣ የካቲት 10 2001

ተቃዋሚዎቹ የተከፋፈሉ ናቸዉ።በዚያ ላይ የሕዝቡን አንገብጋቢ የምጣኔ-ሐብት፥ የጤና እና የማሕበራዊ ችግሮችን ከማንሳት ይልቅ ሥለሩቁ ዲሞክራሲና ፀጥታና ሙስና እያነሱ ሲጥሉ ሻቬዝ ቀደሙ-አሸነፏቸዉም

https://p.dw.com/p/GwAK
ሻቬዝምስል AP

የቪኑዙዌላ ሕዝብ ባለፈዉ እሁድ በተጠራዉ ሕዝበ-ዉሳኔ የሐገሪቱ ሕገ-መንግሥት እንዲሻሻል መወሰኑ ለፕሬዝዳት ሁጎ ሻቬዝና ለሚመሩት ፓርቲ ታላቅ ድል ነዉ።እስካሁን የነበረዉ ሕገ-መንግሥት ለሁለት ዘመነ-ሥልጣናት በፕሬዝዳትነት የሠራ ሰዉ ለተጨማሪ ዘመነ-ሥልጣን እንዲወዳደር አይፈቅድም ነበር።የግራ ፖለቲካ አቀንቃኙ ሻቬዥ ነባሩን ሕገ-መንግሥት ለማማሰቀየር ከዚሕ ቀደም ያደረጉት ሙከራ ከሽፎባቸዉ ነበር።አሁን ተሰካላቸዉ።ባዲሱ ሕግ መሠረት ሻቬዝ ለፕሬዝዳትነት ያለ-ገደብ መወዳደር ይችላሉ።አንዳድ የፖለቲካ ተንታኞች እንደሚሉት ፕሬዝዳንቱ ለዚሕ ድል የበቁት በሕዝብ በመፈቀር-ወይም የገቡትን ቃል በማክበራቸዉ ሳይሆን በተቃዋሚዎቻቸዉ ድክመት ነዉ።ነጋሽ መሐመድ ዝር ዝሩን አጠናቅሮታል።

ድምፅ

ጭፈራ ዳንሱ ገደብ አልነበረዉም።ማሻሻያዉ በ54.ነጥብ አራት ከመቶ ድምፅ መፅደቁ እንደተሰማ እየጨፈረ-እየደነሰ በመስሪያ ቤታቸዉ በኩል የሚያልፍ ደጋፊዎቻቸዉን ለማየት ከፅሕፈት ቤታቸዉ በረነዳ ወጡ-ሁጎ ሻቬዝ።ፈከሩም።

ድምፅ

«ቬኑዙዌላ ለዘላላም ትኑር።የቪኑዙዋላ አብዮት ለዘላላም ይኑር።ሾላዚም ለዘላላም ይኑር።»

የሐገራቸዉን ባንዲራ ያዉለበልባሉ፥ መፈክሩን ጋብ አደረጉ።እና ብሔራዊዉን መዝሙር ያንቆረቁሩት ገቡ።

ድምፅ

ሁጎ ሻቬዝ በርግጥ ድል አደረጉ።ከሰወስት አመት በሕዋላ በሚደረገዉ ፕሬዝዳታዊ ምርጫ ለመወዳደር ከእንግዲሕ የሚያግዳቸዉ የለም።እንደሚያሸነፉ የሚጠረጥርም ቢያንስ እስካሁን በጣም ጥቂት ነዉ።የሃያ-አንደኛዉ ክፍለ ዘመን ሾሻሊዝም የሚሉትን መርሕ ከግብ ለማድረስ እስካሁን በሥልጣን የቆዩበት አስራ-አራት አመታ አልበቃቸዉም።ይቀጥላሉ።

ድምፅ

«እኛ የታላቅ አባት ሐገራችን አርበኞች አንድ ፕሮጀክት አለን።ፕሮጄክቱ የቬኑዙዌላ መሠረታዊ ማንነት ጉዳይ ነዉ።ባለፉት አስር አመታት ይሕንን መልሰን ለማቆም በቅተናል።ፀረ-አብዮታዊ መንገድ አንከተልም።ጉዳዩ የመሆን ወይም አለመሆን ነዉ።»

የሕዝበ-ዉሳኔዉ ዉጤት ለሻቬዝና ለደጋፊዎቻቸዉ ጮቤ አስረጋጭ የመሆኑን ያክል ለተቃዋሚዎቻቸዉ አስደንጋጭ-አሳዛኝም ነዉ የሆነዉ።ተቃዋሚዎቹ ተስፋ እንደደሩት የሻቬዝ ዘመነ-ሥልጣን ባጭሩ የሚያበቃ አይነት አልሆነም።ከሻቬዝ ተቃዋሚዎች አንዳዶቹ ሰዉዬዉ የቪኑዙዌላ ካስትሮ ይሆናሉ ማለታቸዉም አልቀረም።

ያም ሆኖ ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ኖየቮ ቲምፖ የተሰኘዉ ፓርቲ መሪ ኦማር ባርቦሳ እንዳሉት የእሁዱን ሕዝበ-ዉሳኔ ዉጤት በፀጋ ይቀበሉታል።

ድምፅ

«እኛ ዲሞክራሲያዊ ነን።ዉጤቱን እንቀበለዋለን።እምነታችንን ለማስረፅ፥ለዲሞክራሲና የሕዝቡን መብት ለማስከበር የምናደርገዉን ትግል ግን ይበልጥ እናጠናክራለን።»

ሻቬዝ የእሁዱን ሕዝበ-ዉሳኔ ያሸነፉት የመንግሥትን ገንዘብ እና የአስተዳደር መዋቅር ተጠቀመዉ ነዉ ባይዮች አልጠፉም።በሮስቶክ ዩኒቨርስቲ የመንግሥት አወቃቀር ፕሮፌሰር ማኑኤል ጳዉሎስ እንደሚሉት ግን የሻቬዝ ጎራ ብዙ ጊዜ ለድል የሚበቃዉ ከጥረት፥ ብልጠት፥ ይልቅ በተቃዋሚዎቹ መከፋፈልና ድክመት ነዉ።በርግጥ ተቃዋሚዎቹ የተከፋፈሉ ናቸዉ።በዚያ ላይ የሕዝቡን አንገብጋቢ የምጣኔ-ሐብት፥ የጤና እና የማሕበራዊ ችግሮችን ከማንሳት ይልቅ ሥለሩቁ ዲሞክራሲና ፀጥታና ሙስና እያነሱ ሲጥሉ ሻቬዝ ቀደሙ-አሸነፏቸዉም።

Polansky,Martin/Romero,Evan,Ospina-Valencia,Josep

nm,aa

►◄